ሚሪና

ከውክፔዲያ

ሚሪና (ግሪክኛ፦ Μύρινα /ሚውሪና/) በግሪክ አፈ ታሪክ ውስጥ በሊብያ የተገኙት የአማዞኖች ንግሥት ነበረች።

ዲዮዶሮስ ሲኩሉስ (በ51 ዓክልበ. ጽፎ) እንደሚተርከው፣ ሚሪና መጀመርያ በትሪቶኒስ ሀይቅ ዙሪያ ዘምታ ቄሮኔሶስ («ልሳነ ምድር») የተባለች ከተማ መሠረተች። ከ፴ ሺህ ሴት ወታደሮችና ፫ ሺህ ሴት ፈረሰኞች ጋራ ወደ አትላንቲስ ተጉዘው ወረረችና ከተማቸውን ኬርኔ አጠፋች። አታላንቲስን ካሸነፈች በኋላ በአትላንቲስ ጎረቤት በጎርጎኖች ላይ ስትዘምት ከጎርጎኖቹ ፫ ሺህ ማረከች፣ ነገር ግን የቀሩት ጎርጎኖች ወደ ጫካ አምልጠው ጫካውን ለማቃጠል ስትሞክር አልቻለችምና ወደ አገሯ ተመለሰች።

ከዚህ በኋላ ሚሪና ከሥራዊቷ ጋር ወደ ምሥራቅ ዘመተች። ከግብጽ ፈርዖን ጋራ ስምምነት ስለነበራት በአገሩ መካከል በነጻ አለፈችና ዓረቢያንና ሶርያን ያዘች። ከዚያም ኪልቅያን ወረረችና ከኪልቅያ ሰዎች በፈቃድ ዕጅ የሠጡት ሁሉ በነጻ እንዲኖሩ ተወቻቸው። ፍርግያንና ትንሹ እስያን እስከ ካይኮስ ወንዝ ድረስ ያዘች። በዚያ አገር ሚሪና የተባለ ከተማ በሚስያ ሠራች፣ በአለቆቿም ስሞች ሌሎች ከተሞች ኩሜፒታኔ እና ፕሪዬኔ ተሠሩ።

እንዲሁም በኤጊያን ባህር ውስጥ አንዳንድ ደሴት ያዘች። በእርሷ ስም ሌላ ሚሪና ከተማ በሌምኖስ ደሴት፣ በእኅቷም ስም ደግሞ ሚቲሌኔ የተባለው ከተማ በለስቦስ ደሴት ተሠሩ። ከዚህ በኋላ በባህሩ ስትዘምት አውሎ ነፋስ ተነሥቶ ሳሞትራቄ በተባለ ደሴት ላይ ጣላት፣ እዚህም ለአረመኔ ጣኦታቷ ቤተ መቅደስ መሠረተች።

በመጨረሻ ግን የጥራክያ ሰው የሞፕሶስና የእስኩቴስ ሰው የሲፑሉስ ሃያላት በታላቅ ውጊያ አሸነፉአት። የቀሩትም አማዞኖች ወደ ሊብያ ሸሽተው ተመለሱ።