ሥልጣኔና እንጉርጉሮው

ከውክፔዲያ


ሥልጣኔና እንጉርጉሮውስነ-ልቡና ተመራማሪው ሲግመንድ ፍሮይድ1929 እ.ኤ.አ. የተጻፈ እንዲሁም በ1930 እ.ኤ.አ.ጀርመንኛ የታተመ መጽሃፍ ነው። በጀርመንኛ አርእስቱ Das Unbehagen in der Kultur /ዳስ ኡንበሃግን ኢን ደር ኩልቱር/ ወይም «በባህሉ ያለው አለመመቸት» ተሰየመ። ከፍሮይድ ስራዎች ዋና ከሚባሉት ወገን ሲሆን በምዕራቡ አለም ከፍተኛ ተነባቢነት ያለው መጽሃፍ ነው።.[1]

ግለሰቦች በሥልጣኔ ላይ ያንጎራጉራሉ፡ የዚህ ምክንያቱ በአንድ ግለሰብና በስልጣኔ መካከል የማያባራ ቅራኔ በመኖሩ መሆኑን ፍሮይድ አሰፈረ። የዚህ ቅራኔ መሰረታዊ መንስኤ ግለሰቦች በደመነፍስ ነጻነትን ሲፈልጉ ስልጣኔ ግን ከያንዳንዱ ግለሰብ መታዘዝንና እራስን መግዛት ይጠይቃል። የሰው ልጅ በራሱ አረመኒያዊ የሆኑ የደመነፍስ ፍላጎቶች አሉት (ለምሳሌ የመግደል፣ የማያልቅ የፍትወተ ስጋ ፍላጎት ወዘተ...) ። ነገር ግን እኒህ ደመነፍስ ፍላጎቶች በማህበራዊ ኑሮ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳሉ። ስለሆነም በማናችውም የታሪክ ዘመናት የተፈጠሩ ስልጣኔዎች የሰውን ልጅ ደመነፍስ ፍላጎት ለማቀብ ህግ አውጥተዋል። አትግደል፣ አትድፈር፣ አታመንዝር፣ የሌላ ሰውን ሃብት አትውሰድ ወዘተ... የሚሉ ህጎች ወጥተው ህጎቹን የተላለፈ ከፍተኛ ቅጣት በዘመናትና በስልጣኔያት ሁሉ ሲቀበል ይታያል። ይህ እንግዲህ፣ በፍሮይድ አስተሳሰብ፣ በስልጣኔ ውስጥ የሚንሸራሽሩ ዜጎች በስልጣኔ ላይ የማያባራ ቅሬታ እንዲያበጁ አድርጓል።

ከላይ የተጻፈው የፍሮይድ መላምት መሰረቱ የሰው ልጅ አንድ አንድ በተፈጥሮ ያሉት ምንጊዜም የማይቀየሩ የደመነፍስ ባህርዮች ናቸው። ከነዚህ የሰው ልጅ መሰረታዊ ባህርዮች ፍሮይድ ዋና ያላቸው፦ ፍትወተ ስጋ የመፈለግ ባህርይና አንድ ግለሰብ ይህን ፍላጎት እንዳያሟላ ከላይ ሆነው የሚከለክሉትን የበላዮች (ባለ ስልጣናት፣ አለቆች፣ አዛዦች..ወዘተ..)ና በፍትወት ስጋ ተፎካካሪወች ላይ ጥል ለመፍጠር ያለ የደመነፍስ ባህርይ ናቸው።

መጽሃፉ ባጭሩ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ፍሮይድ መጽሃፉን የሚጀመረው የሃይማኖታዊነት ስሜት መነሻ ሊሆን ይችላል ያለውን የውቅያኖሳዊነት ስሜትን በመመርመር ነው። ውቅያኖሳዊነት ስሜት የሚለው ጽንሰ ሃሳብ አንድ ግለስብ በአንድ ወቅት ምሉዕነት፣ ወሰን አልባነትና ዘላለማዊነትን በጥልቅ ሲሰማው የሚመጣ ልዩ ስሜት ነው። ፍሮይድ ይህን "በአለም ውስጥ እንደጨው የመሟሟት" ስሜት በግሉ ሊሰማው ባይችልም ሌሎች ግለሰቦች በጤናማ እና በታወከ አዕምሮ ሊሰማቸው እንደሚችል አስተውሏል። ለምሳሌ ሰዎች ፍቅር ሲይዛቸው በእኔነትና በሚወደደው ውጫዊ ነገር መካከል ያለው ድንበር ወይ ይደበዝዛል ወይም ደግሞ ሟሙቶ ይጠፋል። ስለዚህም ለፍሮይድ የውቅያኖሳዊ ስሜት የሚመነጨው ቀደምት የሰዎች ንቃተ ህሊና እኔነቱን ከከባቢው አለም ሳይለይ በፊት ሁሉ በሁሉ በተደባለቀበት ኩነት ውስጥ ሟምቶ ሲጠፋ ነው። ይህም ከፍሮይድ አጠቃላይ እምነት ጋር የተያያዘ ነው፦ ማለት ፍሮይድ ከዚህ መጽሃፍ በፊት እንዳስረዳ የሃይማኖታዊነት ስሜት የሚመነጨው ጨቅላዎች ከሚሰማቸው ደካማነትና እራስን አለመቻል የተነሳ "የአባታቸውን እርዳታ ከመፈለግ" የሚመጣ ነው [2]፤ ስለሆነም በፍሮይድ አስተያየት "የውቅያኖሳዊ ስሜት በኋላ ከሃይማኖት ጋር የተያያዘ" በጨቅላነት የእኔነት መሟሟት የሚመነጭ ነው። በሌላ አባባል እውነተኛ የሃይማኖት ስሜት ሳይሆን ነገር ግን ይህን ሁኔታ የተሰማቸው ሰዎች እንደ እውነተኛ የሃይማኖት ስሜት የሚረዱት ስሜት ነው።



ማጣቀሻ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ Harv|Gay|1989|loc=p. 722
  2. ^ Strachey 2001, pg. 72