ሥልጣኔና እንጉርጉሮው
ሥልጣኔና እንጉርጉሮው በስነ-ልቡና ተመራርማሪው ሲግመንድ ፍሩድ በ1929 ዓ.ም. የተጻፍ እንዲሁም በ1930 ዓ.ም በጀርመንኛ የታተመ መጽሃፍ ነው። ከፍሩድ ስራወች ዋና ከሚባሉት ወገን ሲሆን በምዕራቡ አለም ከፍተኛ ተነባቢነት ያለው መጽሃፍ ነው።.[1]
ግለሰቦች በስልጣኔ ላይ ያንጎራጉራሉ የዚህ ምክንያቱ በአንድ ግለሰብና በስልጣኔ መካከል የማያባራ ቅራኔ በመኖሩ መሆኑን ፍሩድ አሰፈረ። የዚህ ቅራኔ መሰረታዊ መንሴ ግለሰቦች በደመነፍስ ነጻነትን ሲፈልጉ ስልጣኔ ግን ከያንዳንዱ ግለሰብ መታዘዝንና እራስን መግዛት ይጠይቃል። የሰው ልጅ በራሱ አረመኒያዊ የሆኑ የደመነፍስ ፍላጎቶች አሉት (ለምሳሌ የመግደል፣ የማያልቅ የፍትወተ ስጋ ፍላጎት ወዘተ...) ። ነገር ግን እኒህ ደመነፍስ ፍላጎቶች በማህበራዊ ኑሮ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳሉ። ስለሆነም በማናችውም የታሪክ ዘመናት የተፈጠሩ ስልጣኔወች የሰውን ልጅ ደመነፍስ ፍላጎት ለማቀብ ህግ አውጥተዋል። አትግደል፣ አትድፈር፣ አታመንዝር፣ የሌላ ሰውን ሃብት አትውሰድ ወዘተ... የሚሉ ህጎች ወጥተው ህጎቹን የተላለፈ ከፍተኛ ቅጣት በዘመናትና በስልጣኔያት ሁሉ ሲቀበል ይታያል። ይህ እንግዲህ፣ በፍሩድ አስተሳሰብ፣ በስልጣኔ ውስጥ የሚንሸራሽሩ ዜጎች በስልጣኔ ላይ የማያባራ ቅሬታ እንዲያበጁ አድርጓል።
ከላይ የተጻፈው የፍሩድ ርዕዮተ አለም መሰረቱ የሰው ልጅ አንድ አንድ በተፈጥሮ ያሉት ምንጊዜም የማይቀየሩ የደመነፍስ ባህርዮች ናቸው። ከነዚህ የሰው ልጅ መሰረታዊ ባህርዮች ፍሩድ ዋና ያላቸው፦ ፍትወተ ስጋ የመፈለግ ባህርይና አንድ ግለሰብ ይህን ፍላጎት እንዳያሟላ ከላይ ሆነው የሚከለክሉትን የበላዮች (ባለ ስልጣናት፣ አለቆች፣ አዛዦች..ወዘተ..)ና በፍትወት ስጋ ተፎካካሪወች ላይ ጥል ለመፍጠር ያለ የደመነፍስ ባህርይ ናቸው።
መጽሃፉ ባጭሩ [ለማስተካከል]
ፍሩድ መጽሃፉን የሚጀመረው የሃይማኖታዊነት ስሜት መነሻ ሊሆን ይችላል ያለውን የውቅያኖሳዊነት ስሜትን በመመርመር ነው። ውቅያኖሳዊነት ስሜት የሚለው ጽንሰ ሃሳብ አንድ ግለስብ በአንድ ወቅት ምሉዕነት፣ ወሰን አልባነትና ዘላለማዊነትን በጥልቅ ሲሰማው የሚመጣ ልዩ ስሜት ነው። ፍሩድ ይህን "በአለም ውስጥ እንደጨው የመሟሟት" ስሜት በግሉ ሊሰማው ባይችልም ሌሎች ግለሰቦች በጤናማ እና በታወከ አይምሮ ሊሰማቸው እንደሚችል አስተውሏል። ለምሳሌ ሰወች ፍቅር ሲይዛቸው በእኔነትና በሚወደደው ውጫዊ ነገር መካከል ያለው ድንበር ወይ ይደበዝዛል ወይም ደግሞ ሟሙቶ ይጠፋል። ስለዚህም ለፍሩድ የውቅያኖሳዊ ስሜት የሚመነጨው ቀደምት የሰወች ንቃተ ህሊና እኔነቱን ከከባቢው አለም ሳይለይ በፊት ሁሉ በሁሉ በተደባለቀበት ኩነት ውስጥ ሟምቶ ሲጠፋ ነው። ይህም ከፍሩድ አጠቃላይ እምነት ጋር የተያያዘ ነው፦ ማለት ፍሩድ ከዚህ መጽሃፍ በፊት እንዳስረዳ የሃይማኖታዊነት ስሜት የሚመነጨው ጨቅላወች ከሚሰማቸው ደካማነትና እራስን አለመቻል የተነሳ "የአባታቸውን እርዳታ ከመፈለግ" የሚመጣ ነው [2]፤ ስለሆነም በፍሩድ አስተያየት "የውቅያኖሳዊ ስሜት በኋላ ከሃይማኖት ጋር የተያያዘ" በጨቅላነት የእኔነት መሟሟት የሚመነጭ ነው። በሌላ አባባል እውነተኛ የሃይማኖት ስሜት ሳይሆን ነገር ግን ይህን ሁኔታ የተሰማቸው ሰወች እንደ እውነተኛ የሃይማኖት ስሜት የሚረዱት ስሜት ነው።
| ጅምር! (ይህ አጭር ጽሑፍ መሠረት ወይም መዋቅር ነው። እርስዎ ሊያስፋፉት ይችላሉ!) |