ራስ ዳርጌ

ከውክፔዲያ
ራስ ዳርጌ ሣሕለ ሥላሴ

ራስ ዳርጌ ሣህለ ሥላሴ የሸዋው ንጉሥ ሣህለ ሥላሴ ልጅና የንጉሥ ኃይለ መለኮት ግማሽ ወንድም እንዲሁም ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ አጎት ነበሩ። ራስ ዳርጌ በ፲፰፻፳፪ ዓመተ ምሕረት ሲወለዱ ከአድዋ ጦርነት በኃላ በበተወለዱ በ ፸ ዓመታቸው ፲፰፻፺፪ ዓ/ም በሰላሌ የአስተዳደር ርዕሰ ከተማ በነበረችው ፍቼ ላይ አልፈዋል።

ዓፄ ቴዎድሮስ ወደ ሸዋጥቅምት ወር ፲፰፻፵፰ ዓ/ም ላይ በዘመቱ ጊዜ አቤቶ ዳርጌ (የወደፊቱ ራስ) እና የወንድማቸው ልጅ አቤቶ ምኒልክ (የወደፊቱ ዳግማዊ ዓፄ ምንሊክ) ኅዳር ፴ ቀን በረከት ላይ በተደረገው ጦርነት፣ እራሳቸውን ለመከላከል ሞክረዋል። ዳሩ ግን በጦርነቱ ድል ስለሆኑ አቤቶ ዳርጌና አቤቶ ምንሊክ በምርኮ፣ መጀመሪያ ወደጎንደር ከዚያ ወደደብረ ታቦር እና በስተመጨረሻ ወደ መቅደላ ተወሰዱ። በዚህ ወቅት አቤቶ ዳርጌ የጦርነት ድፍረትን ስላሳዩ በዓፄ ቴዎድሮስ ፊት ከፍተኛ ባለሟልነትን አገኙ፣ እንዲሁም የፊታውራሪነት ማዕረግ ተሰጥቷቸው በክብር ይኖሩ ነበር። ቆይቶም ሰኔ ፳፬ ቀን ፲፰፻፶፯ ዓ/ም ደጃዝማች ምንሊክ ከመቅደላ ሲያመልጡ እርዳታ ቢሰጡም እራሳቸው ግን በምሽጉ ውስጥ ቀርተው ነበር። ዓፄ ቴዎድሮስም ለፊታውራሪ ዳርጌ ከነበራቸው ፍቅር የተነሳ ቅጣት አልበየኑባቸውም ነበር።

ዓፄ ቴዎድሮስ ሞት በኋላ ፊታውራሪ ዳርጌ ወደ ሸዋ ተጉዘው በራስ ማዕረግ የሰላሌ አስተዳዳሪ ሆኑ። ቀጥሎም የአሩሲ አስተዳዳሪ በመሾም አሩሲ ሲካሄድ የነበረውን ዘመቻ አጠናቀቁ። ከዚህ በኋላ ራስ ዳርጌ የዳግማዊ ምኒልክ ዋና አማካሪ በመሆን ንጉሡን ይረዱ ነበር። ከአስተዋይነታቸውና አርቆ አሳቢነታቸው የተነሳ በአጼ ዮሐንስ ዘንድ ሳይቀር ከፍተኛ ግምት ያገኙ መሪ ነበሩ። የአድዋ ጦርነት ወቅት በዳግማዊ ምኒልክ ፈንታ በእንደራሴነት አገሪቱን ይመሩ ነበር። በዚህ ወቅት ጣሊያኖች ልጃቸውን ጉግሳ ዳርጌን የወደፊቱ የኢትዮጵያ ንጉሥ ነህ በማለት ከሚማርበት ስዊዘርላንድ እንዳመጡት ሲሰሙ በንዴት ስሙን ከቤተሰባቸው ስም ዝርዝር እንዳሰረዙ ታሪክ ጸሐፊው ሃሮልድ ማርከስ ዘግቦት ይገኛል[1]

ራስ ዳርጌ መጋቢት ፲፭ ቀን ፲፰፻፺፪ ዓ/ም በተወለዱ በ ፸ ዓመታቸው ፍቼ ላይ አርፈው በደብረ ሊባኖስ ገዳም ተቀበሩ።

የራስ ዳርጌ ከተማ፣ ፲፰፻፸፰ዓ.ም. ፣ ቦሮማጨርጨር፣ አሁን ምዕራብ ሐረርጌ


ዋቢ ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ Marcus, Menelik II, p. 215

2. የራስ ዳርጌ ዘር ሐረግ (እንግሊዝኛ) http://freepages.genealogy.rootsweb.ancestry.com/~royalty/ethiopia/i159.html