ራግው

ከውክፔዲያ
ራግው (በሠዓሊው ጊዮም ሩዊይ አስተያየት፣ 1545 ዓ.ም.)

ራግው (ዕብራይስጥ፦ רְעוּ /ርዑ/፤ ግሪክ፦ /ራጋው/) በመጽሐፍ ቅዱስ መሠረት የፋሌቅ ልጅና የሴሮሕ አባት ሲሆን የአብርሃም ቅድማያት ነበረ።

መጽሐፍ ቅዱስ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ኦሪት ዘፍጥረት 11፡20 ዘንድ፣ የራግው እድሜ 132 ሲሆን ሴሮሕ ተወለዱ፤ ራግውም ከዚያ 207 ዓመታት ኑሮ በጠቅላላ 339 ዓመታት ኖረ ማለት ነው። እነዚህ ቁጥሮች ከግሪኩ ትርጉም (70ው ሊቃውንት) እና ከሳምራዊው ትርጉም ጋራ ይስማማሉ። በመደበኛው ዕብራይስጥ ትርጉም ግን፣ ራግው ሴሮሕን የወለደው ዕድሜው 32 ዓመት ነበር፤ ስለዚህ በጠቅላላ 239 ዓመታት መኖሩ ነው።

መጽሐፈ ኩፋሌ ዘንድ፣ የራግው እናት ስም ሎምና (የሰናዖር ልጅ) ነበር፤ በ1580 ዓመተ ዓለም (ከዓለም ፍጥረት በኋላ) ተወለደ። ይህም የባቢሎን ግንብ የተጀመረበት ወቅት ነበር፤ በኩፋሌ አቆጣጠር ከማየ አይኅ 272 ዓመታት በኋላ ነው። የባቢሎን ግንብ የወደቅበት ዓመት ዕድሜው 59 ዓመታት ሲሆን ነው። በ1681 ዓመተ አለም ሚስቱን ኡራን (የኡር ከሰድ ልጅ) አገባት። በ1687 ዓ.ዓ. ሴሮሕ ተወለዱ፣ እንግዲህ የራግው እድሜ ያንጊዜ 107 ዓመታት ነበር። በዚያም አመት የከለዳውያን ዑር ተሠራና ከኖኅ የተወለዱት አሕዛብ መጀመርያ ጦርነት ሠሩ። የሞተበት ዓመት አይሠጠም።

ሌሎች ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አረብኛኪታብ አል-ማጋል (ከቄሌምንጦስ ሥነ ጽሑፍ መካከል) ዘንድ፣ ራግው ሴሮሕን ሲወልድ ዕድሜው 32 ነበር፤ የራግውም ዕድሜ 163 ሲሆን ናምሩድ ነገሠ። ከዕብራይስጡም ዘፍጥረት በመስማማት፣ እስከ 239 ዓመታት እድሜው ድረስ ኖረ፤ በሠራውም ከተማ በ«ዖዓናን» ተቀበረ። ከዚህ በኋላ በዝርዝሩ ስሙ «ያርዑ» ተብሎ ሚስቱ «ታናዓብ» (የዖቤድ (ኤቦር) ልጅ ትባላለች። ናኮርም የራግውን ሴት ልጅ «አአክሪስ» ያግባታል።

አራማያየመዝገቦች ዋሻ ዘንድ፤ ራግው በ32 ዓመት ሴሮሕን ወልዶ፣ እድሜው 130 ሲሆን ናምሩድ ነገሠ። እንደገና በመሞቱ እድሜው 239 ዓመታት ይሠጣል። በሌላ አንቀጽ እንደሚለን፣ የራግው ዕድሜ 50 ሲሆን ናምሩድ ኒሲቢስኤደሣንና ካራንን ከተሞች ሠራ።

ግዕዝ የአዳምና ሕይዋን ትግል ከሠይጣን ጋራ ዘንድ፣ ራግው በሙሉ 232 ዓመታት እንደ ኖረ ሲል በሌላ ቦታ ግን ለ289 ዓመታት ኖረ ይላል። ዕድሜው 130 ዓመታት ሲሆን ናምሩድ ነገሠ፤ 140 ዓመታትም ሲሆን «ያኑፍ» (ወይም ምጽራይም) በግብጽ ነገሠ።