ተዋህዶ

ከውክፔዲያ

ተዋውጦ (Monophysitism)[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በዚህ እምነት ኢየሱስ ክርስቶስምድር በነበረበት ጊዜ አንደ እና አንድ ብቻ ተፈጥሮ /ባሕርይ ነበረው ። ይህም ተፈጥሮ /ባሕርይ ሥጋ የሌለበት መለኮት ነበር የሚል ነው ። ሥጋ እንኳ ቢኖረው ፣ ባሕር ውስጥ ሟሙቶ እንደሚጠፋ አንድ ማንኪያ ጨው ፣ የክርስቶስ ሥጋም እንዲሁ በመለኮቱ ባሕር ሟሙቶ ጠፍቷል ይላሉ ።

ተዋሕዶ (Miaphysitism)[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 3:16 እግዚአብሔርንም የመምሰል ምሥጢር ያለ ጥርጥር ታላቅ ነው፤ በሥጋ የተገለጠ፥ በመንፈስ የጸደቀ፥ ለመላእክት የታየ፥ በአሕዛብ የተሰበከ፥ በዓለም የታመነ፥ በክብር ያረገ።

ስንዴ እና ባቄላ እንደሚቀላቀሉት - ያለመቀላቀል፣ ኦክስጅንና ሀይድሮጅን ሲዋሐዱ ጸባያቸው እንድሚቀያየር - ያለመቀያየር፣ የተጋቡ ሰዎች እንደሚለያዩ - ለአንዳች ቅፅበት እንኳን ያለመለያየት፣ መለኮታዊ እና ሥጋዊ ተፈጥሮ በኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ሆነ። ቅድስት ድንግል ማርያም ሰው ወይም አምላክ ወይም ደግሞ ኹለት ተፈጥሮ ያለው ሰው እና አምላክ ሳይሆን የወለደችው፣ የሰው እና የአምላክ ውሕደት፣ አንድ ተፈጥሮን፣ እየሱስ ክርስቶስን ነው።

በዕለት ተዕለት ኑሯችን ይህን ዓይነት ኹኔታ የምናየው የአእምሮ እና የአንጎልን ውሕደት ልብ ስንል ነው። በዚህ ንግግር አእምሮ ማለት የሐሳባችን ስብስብ ሲሆን የማይጨበጥ እና የማይዳሰስ ነው፤ አንጎል /ጭንቅላት ማለት ደግሞ ተጨባጩ የማሰቢያ ክፍል ማለት ነው። የኹለቱ ውሕደት እንግዲህ ያለመቀላቀል፣ያለመለዋወጥ እና ያለመለያየት የሚሉትን ሐሳቦች ያንጸባርቃል።


ተከፋፍሎ (Dyophysitism)[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በዚህ እምነት እየሱስ ክርስቶስ ሁለት ተፍጥሮ አለው ተብሎ ይነገራል ፦ ስጋው እና መለኮታዊ ። እነዚህ 2 ተፈጥሮወች በአንድ ተፈጥሮ (እየሱስ ክርስቶስ ) ይኑሩ እንጂ አልተዋሀዱም ተብሎ ይታመናል ።

የሰው ልጅ ፣ በጊዜና በቦታ የተወሰነ ሲሆን ፣ ስጋን ለመስዋእት ማቅረብ ከዘመን -ዘመን የሚሻገር የሐጥያት ስርየት አያመጣም ።

እየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሲሞት ፣ ተፈጥሮውን ከፋፍሎ ፣ ስጋው ብቻ ሞተ ማለት ፣ ዮሐንስ 3:16 እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና። የሚለውን ፉርሽ ያደርጋል ።

በመስቀል ላይ የሞተው እየሱስ ክርስቶስ ፣ ተዋህዶ ወይንም አንድ ተፈጥሮ ነው ። የመለኮት ተፈጥሮ እንግዲህ ሞትንና መንገላታትን ባያውቅም ከስውነት ጋር ባለው ውህደት ግን አብሮ ተንገላቷል ማለት ነው ።

ይህን ሀሳብ ለመረዳት የሚነድ ብረትን ያስታውሷል ። እሳት እና ብረት ያለመቀላቅል ሲዋሀዱ ፣ አንጥረኛ ብረትን በመዶሻ ሲመታ ፣ የመዶሻው ምት እሳት ላይ ምንም ሀይል ባይሆረውም ፣ እሳት እራሱ ከብረት ጋር ስለተዋሀደ ፣ ብረት ሲጣመም ፣ እንዲሁ እሳትም ይጣመማል ።

ሉቃስ በሐዋርያት ስራ 20:28 በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ሲል እዚህ ላይ መርዳት ያለብን መለኮት በራሱ ደም የለውም ። ነገር ግን የመለኮት ተፈጥሮ እና የስው ተፈጥሮ ውህደትን ለማመልከት ያንዱን ባህርይ በሌላው ስም መጥቀስ ተችሏል ።

እየሱስ ክርስቶስ በስጋ ከሞተ ፣ ለምን ወደዚህ አለም መምጣትስ አስፈለገው ። የስጋ መስዋእት ለዘላለም ስርእየት በቂ ከሆነ አንድ የተመረጠ ሰው ለዚህ ተግባር ማዋል ይቻል ነበር ፡ ስለማይቻል 'የእግዚአብሔር ልጅ ' 'ከሰው ልጅ ' ጋር ያለመቀላቀል ፣ ያለመለዋወጥ ፣ ያለመለያየት ተዋሐደ ። የዚህም ውህደት ውጤት ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ ፣ ከትውልድ እስከ ትውልድ የሚሸጋገር ድህነትን ለሰው ልጅ አተረፈ ። ዮሐንስ 3:16 እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።

1ቆሮ 2:8 አውቀውስ ቢሆኑ የክብርን ጌታ ባልሰቀሉትም ነበር፤ ቅዱስ ጳውሎስ እዚህ ላይ «የእየሱስ ክርስቶስን ስጋ» አላለም ፣ የልቁኑ «የክብር ጌታ» በማለት ውሕደቱን በግልጽ አስቀምጧል ።

ቅዱስ ጴጥሮስ በሐዋርያት ስራ 3:14-15 እናንተ ግን ቅዱሱን ጻድቁንም ክዳችሁ ነፍሰ ገዳዩን ሰው ይሰጣችሁ ዘንድ ለመናችሁ፥ የሕይወትንም ራስ ገደላችሁት፤ «የሕይወት እራስ» እንግዲህ የመለኮትነትን ባህርይ የሚያሳይ ሐረግ ነው ።

እብራውያን 2:10 ብዙ ልጆችን ወደ ክብር ሲያመጣ የመዳናቸውን ራስ በመከራ ይፈጽም ዘንድ፥ ከእርሱ የተነሣ ሁሉ በእርሱም ሁሉ ለሆነ፥ ለእርሱ ተገብቶታልና። በመከራ ላይ እያለ እንኳን መለኮታዊ ባህርዩን (በእርሱ ሁሉ የሆነ ) አልረሳም ።

ራእይ 1:17-18 ባየሁትም ጊዜ እንደ ሞተ ሰው ሆኜ ከእግሩ በታች ወደቅሁ። ቀኝ እጁንም ጫነብኝ እንዲህም አለኝ። አትፍራ፤ ፊተኛውና መጨረሻው ሕያውም እኔ ነኝ፥

ሞቼም ነበርሁ እነሆም፥ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ሕያው ነኝ፥ የሞትና የሲኦልም መክፈቻ አለኝ።

እዚህ ላይ ፣ እየሱስ ክርስቶስ እራሱ ፣ ስለስቅለቱ ሲናገር እራሱን በመከፋፈል በስጋ ሞትኩ አላለም ፣ ይልቁኑ ፊተኛውና መጨረሻው ሲሆን ፣ ለዘላለምም ሕያው ሲሆን ሳለ ፣ በመስቀል ላይ መሞቱን ያለክፍፍል ፣ በተዋህዶ አስረድቷል ።

እንግዲህ አዲስ ኪዳን እንደሚያስረዳው ፣ በመስቀል ላይ የሞተው ፣ በሞቱም ከዘላለም እስከ ዘላለም የድህነት ጥላን የዘረጋልን «ስጋ» ብቻ ሳይሆን ፣ የ«ክብር ጌታ»፣ የ«ሕይወት እራስ»፣ «በእርሱ ሁሉ የሆነ»፣ 'ፊተኛው እና ሁዋለኛው ' የተባለው «ተዋህዶው» እየሱስ ክርስቶስ ነው ።

የዮሐንስ ወንጌል 20:19 ያም ቀን እርሱም ከሳምንቱ ፊተኛው በመሸ ጊዜ፥ ደቀ መዛሙርቱ ተሰብስበው በነበሩበት፥ አይሁድን ስለ ፈሩ ደጆቹ ተዘግተው ሳሉ፥ ኢየሱስ መጣ፤ በመካከላቸውም ቆሞ። ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው። ይህንም ብሎ እጆቹንም ጎኑንም አሳያቸው። ደቀ መዛሙርቱም ጌታን ባዩ ጊዜ ደስ አላቸው። ክርስቶስ በስጋው ነው በተዘጋ በር ያለፈው ወይንስ በመለኮት ነው ያለፈው ። በመለኮት ካለፈ እንዴት በስጋ ታያቸው ? በስጋስ እንዴት በተዘጋ በር አለፈ ?

ይልቁኑ ፣ ከሞት የተነሳው ፣ ወልድ ዋህድ በተዘጋ በር አለፈ በአይንም ታየ ፡ ተገለጠም ። የቅዳሴ መጽሐፍ ስለእየሱስ ክርስቶስ ሞት እና መነሳት የሚናገረውን ጠቅሰን እንደምድም ፦

ነፍስና ስጋው ቢላቀቁም ፣ መለኮቱ ግን ከስጋውም ከነፍሱም ጋር ነበረች ። ነፍሱም ከመለኮቱ ጋር ሆና ለስብከትወደ ገሀነም ወረደች ፣ በእምነት ለሞቱትም የገነትን በር ከፈተች ። ነገር ግን ከመለኮት ጋር የተዋሀደው ስጋው በመቃብር ነበር ።

በሶስተኛው ቀን ጌታ ሞትን ድል ነሳ ፣ ነፍሱም ከስጋው ጋር ተመልሳ ተዋሀደች ፣ መለኮት ግን ምንጊዜም አልተለየም ፣ ስለዚህም የዘላለም ድነት ሆነ ።

አሜን ለዘለአለም።