ተፈራ ወልደሰማዕት

ከውክፔዲያ


ተፈራ ወልደሰማዕት
፱ኛው የኢትዮጵያ የገንዘብ ሚኒስትር
ቀዳሚ ነጋሽ ደስታ
ተከታይ ተስፋዬ ዲንካ
ዜግነት ኢትዮጵያዊ
ትምህርት የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ
ሀይማኖት የኢትዮጵያ ፡ ኦርቶዶክስ ፡ ክርስትና

የክቡር አቶ ተፈራ ወልደሰማዕት (1938 - 2013), (English: Teferra Wolde-Semait) የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣን ነበሩ። ከ1976 ዓ/ም አንስተው እስከ 1982 ድረስ በኢትዮጵያ ገንዘብ ሚኒስትር ሥልጣንና በኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ በከፍተኛው የአመራር ቦታ ላይ ነበሩ።

የህይወት ታሪካቸው[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ክቡር አቶ ተፈራ ወልደሰማዕት ከአባታቸው ከአቶ ወልደሰማዕት ማረሚ እና ከእናታቸው ከወይዘሮ ጀማነሽ በዳኔ በሰሜን ሸዋ ቅምቢብት ወረዳ እ. ኤ. አ. መስከረም 1 ቀን 1938 ዓ.ም ተወለዱ። አቶ ወልደሰማዕት እና ወይዘሮ ጀማነሽ ሶስት ወንድ ልጆችን ተገኝ፥ በቀለ ፥እና ተፈራን እና ሁለት ሴቶችን ጥሩነሽ ፥ እና ዘነበችን ያፈሩ ሲሆን ተፈራ የመጨረሻ ልጅ ናቸው። ክቡር አቶ ተፈራ የተወለዱበት ወቅት ግፈኛው ፋሺሽት ኢጣልያ ኢትዮጵያን የወረረበት እና ሕዝብዋን በመርዝ ጋዝ የፈጀበት ስለነበረ አቶ ወልደሰማዕት ዘምተው በጦር ሜዳ ግዳጃቸውን ከተወጡ በኋላ ወደ መኖሪያ አካባቢያቸው ተመልሰው ብዙም ሳይቆዩ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። እንዳካባቢው ህዝብ ሁሉ ወ/ሮ ጃማነሽም ልጆቻቸውን ይዘው ከመኖሪያ ስፍራቸው ተሰደዋል። ክቡር አቶ ተፈራም አዲስ አበባ ተወስደው የአገራቸውን የቤተክህነት ትምህርት በመከታተል ዳዊት እስከመድገም ድረስ ደርሰዋል። ከዚያም ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ካክብ ፅባህ ትምህርት ቤት ገብተው ከአንደኛ አስከ አስራ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርትን አጠናቀዋል። ቀጥለውም ለአንድ ዓመት በመምህርነት ከአገለገሉ በኋላ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ገብተው በኢኮኖሚክስ የባችለር ዲግሪ በማዕረግ (with distinction) በማግኘት እ.ኤ.አ. በ1964 ዓ.ም. ተመርቀዋል። ከኮሌጅ እንደተመረቁም በሕዝባዊ ኑሮ ዕድገት ሚኒስቴር ተቀጥረዋል። በዚህም መስሪያ ቤት ለተወሰነ ጊዜ ከሰሩ በኋላ ወደ ሔግ ኔዘርላንድ ለከፍተኛ ትምህርት ተልከው እ. ኤ. አ. በ 1967 ዓ.ም. በልማት ኢኮኖሚክስ የማስተርስ ዲግሪ አግኝተዋል።

በሙያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ከዚያም ወደ ሕዝባዊ ኑሮ ዕድገት ተመልሰው የፕላን ዩኒቲን በማቋቋምና የዩኒቲ ሃላፊ በመሆን የረጅም ጊዜ የልማት ፕላን እና ዓመታዊ የካፒታል ፕሮግራም እና በጀት በማዘጋጀት እ. ኤ. አ ከ1967 እስከ 1971 አገልግለዋል፡፡ ከዚያም ወደ ገንዘብ ሚኒስቴር በማዛወር በዋሺንግተን በኢትዮጵያ ኤምባሲ የኢኮኖሚ እና ፋይናንስ አማካሪ ሆነው እ. ኤ. አ. 1972-1974 ዓ.ም. ሰርተዋል በዚህም ሓላፊነታቸውን ከአለም ባንክ ከአይ. ኤም. ኤፍ ከአሜሪካ የኢንተርናሽናል የልማት ድርጅት ማለትም ከዩ. ኤስ. ኤይድ እና ከሌሎችም ድርጅቶች ጋር ለኢትዮጵያ የሚሰጠውን ዕርዳታ እያደገ አንዲሄድ ክትትል አድርገዋል።

ከዚያም ወደ አዲስ አበባ ተመልሰው እ. ኤ. አ. ከ 1974-1975 ዓ.ም. በገንዘብ ሚኒስቴር የብድር አና ኢንቨስትመንት መምርያ ሃላፊ በመሆን የውጪ ብድር አና እርዳታን አንዲሁም በተለያዩ የፐብሊክ ኢንተርፕራይዞች የመንግስት ኢንቨስትመንተ ይዞታ ተከታትለዋል። ቀጥሎም እ. ኤ. አ ለ 1977-1982 በዚሁ መ/ቤት በምክትልነትና በተጠባባቂነት ከዚያም እ. ኤ. አ. ከ 1977-1982 ዓ.ም. በገንዘብ ሚንስቴር ከፍተኛ አገልግሎት አበርክተዋል። በዚህም ሓላፊነታቸው የሚኒስቴርነት ከፍተኛ አገልግሎት አበርክተዋል። በዚህም ሐላፊነታቸው የሚነስቴሩን ልዩ ልዩ የስራ ክፍሎች በአዲስ መልክ በማደራጀት ለአገሪቷ የልማትና ቋሚ ወጪዎች የሚውሉ ገቢዎችን በማሳደግ እና ሌሎች ሚኒስቴሮችም የቀለጠፈ የበጀት አሰጣጥ አገልግሎት እንዲያገኙ አንዲሁም በፋይናንስ ቁጥጥር እና በጥናት እና ምርምር ሚኒስቴሩ እንዲጠናከር እና የሚጠበቅበትን ወቅታዊ እና የተሟላ አገልግሎት እንዲያበረክት ከማንኛውም ጊዜ ይበልጥ ከኢንተርናሽናል እና ከአህጉራዊ ድርጅቶች በተለይም ከዓለም ባንክ አና ከአፍሪካ ልማት ባንክ ከተለያዩ አገሮች ለኢትዮጵያ ልማት ዕርዳታ እና ብድር ለማስገኘት ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል።

እንደሚታወቀው ጊዜው አጅግ ፈታኝ የለውጥ እና የሽግግር ወቅት ስለነበር የአገሪትዋ የፋይናንስ ሁኔታ እንዳይናጋ በብልህነት በጥንቁቅነት በማስተዳደር የበጀት ዲሲፕሊን እንደተጠበቀ እንዲቆይ በለውጡም ምክንያት ለኢትዮጵያ ከምዕራብ አገሮች እና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች የሚሰጠው የወጪ ዕርዳታ እንዳይቀንስ ከፍተኛ ተጋኢደሎ አድርገዋል። በወቅቱ አዲስ የኢትዮጵያ ወዳጅ ከሆኑት አንፃር ለፖለቲካ ተቀጋይነት ሳይሆን የአገሪቱን ጥቅም ለማስጠበቅ የሚያስችል የኢኮኖሚ ግንኙነት እንዲጠበቅ ተዋግተዋል። በዚህም የተነሳ በአፍሪካም ሆነ በኢንተርናሽናል ደረጃ ብዙ አድናቆት እና አክብሮት አትርፈዋል። አብሮዋቸው የነበሩ የስራ ጓደኞቻቸውም ለዚሁ ሁሉ ምስክር ናቸው።

ክቡር አቶ ተፈራ የገንዘብ ሚኒስትር በነበሩበት አመታት ሁሉ የብሔራው ባንክ የቦርድ ሊቀመንበር ስለነበሩ የአገሪቷን አጠቃላይ የሞንተሪ እና የፋይናንስ የበላይ ሓላፊ በመሆን የሚጠበቅባቸውን አመራር በብቃት ሰጥተዋል። ከላይ ከተዘረዘሩት ቋሚ የስራ ሓላፊነታቸው በተጨማሪ የብሔራዊ ፕላን ኮሚሽን ፥የካቢኔው የኢኮኖሚ አና ሕግ ኮሚቴዎች የቴሌኮሚኒኬሽን፥ የብሔራዊ ቡና ፥የከብት እርባታ እና የስጋ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦርዶች አባልም ሆነው አገልግለዋል።

ክቡር አቶ ተፈራ በትዕግስት፥ በብልህነት እና በቅንነት እጅግ ከባድ የሆነውን ሓላፊነታቸውን በመወጣት ለብዙ ዓመታት ከአገለገሉ በኋላ የአገሪቷ ሁኔታ ከመሻሻል ይልቅ ወደባሰ አቅጣጫ እያመራ መሄዱን በመገንዘባቸው እ.ኤ.አ 1982 ዓ.ም. ቤተሰባቸውን ይዘው ወደ አሜሪካ በመምጣት ከስራቸው በገዛ ፈቃዳቸው ተሰናብተዋል። በረጅም ጊዜ የአገልግሎት ዘመን የቀሰሙትን ሰፊ የስራ ልምድ በተለይ በፋይናንስ አና ባንክኒግ በበጀት በጥናት እና ምርምር ከፍተኛ ፖሊስ ነክ የምክር አገልግሎት ለ 10 ዓመታት ያህል ለልዩ ልዩ አገሮች እና ድርጅቶች አበርክተዋል። ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህል።

  • በዋሽንግተን ለሚገኘው ኦቨር. ሲይስ. ዲቨሎፕመንት ካወንስል (Overseas Development Council) እ.ኤ.አ. ከ1982-1983 ዓ.ም. በመመደብ ከሰሓራ በታች ያሉት የአፍሪካ አገሮች (Sub-Saharan Africa) የልማት ዕድገት በሚመለከት ጥናት አካሂደዋል።
  • በአይ. ኤም. ኤፍ ተመድበው ለስወዚላንድ መንግስት ብሄራዊ ባንክ እ.ኤ.አ. ከ 1984-1987 ዓ.ም. የጥናት እና ምርምር አቅሙ የጥናት እና ምርምር አቅሙ ስለሚዳብርበት በማማከር ሰርተዋል።
  • በዓለም ባንከ አማካሪ በመሆን ስለአፍሪካ ፐብሊክ ኢንተርፕራይዞች ( African Public Enterprises) የስራ ክንውን እና የማሻሻያ ጥናት እ. ኤ. አ. በ1988 አካሂደዋል።
  • በአይ. ኤም. ኤፍ ተመድበው ለሌሴቶ ማዕከላዊ ባንክ በፖሊሲ እና ኦፕሬሽን በጥናት እና ምርምር የባንኩ አቅም ስለሚጠናከርበት አማክረዋል።
  • አይ. ኤም. ኤፍ እና የተባበሩት መንግስታት የልማት ድርጅት ለናሚቢያ መንግስተ የሚሰጡትን የቴክኒክ ዕርዳታ በማስተባበር እና ለናሚቢያ የገንዘብ ሚኒስቴር ከፍተኛ አማካሪ በመሆን አገልግለዋል።

ክቡር አቶ ተፈራ ከአበረከትዋቸው ጽሁፎች መካከል

  • በልማት ኋላቀር ( LDC’s ) ከሆኑ አገሮች መካከል ስለጋምቢያ ሌሴቶ ማላዊ እና ሱዳን ኢኮኖሚ ጥናት (እ. ኤ. አ. 1981)
  • ከሰሓራ በታች ስላሉት አፍሪካ አገሮች (Sub-Saharan Africa ) የልማት ፖሊሲ ( እ. ኤ. አ 1983)
  • በኢትዮጵያ ልምድ ላይ የተመሰረተ ስለ አንዳንደ የአፍሪካ አገሮች አጀስትመንት (Adjustment) ፖሲሲ
  • ከሌሎች ጋር በመተባበር የአፍሪካ ፐብሊክ ኢንተርፕራይዞች ስለሚሻሻሉበት ጥናት (እ. ኤ. አ. 1989)
  • ስለ ሳዴግ ( SADCC ) አባል አገሮች የሞኒተር ውህደት/ ህብረት
  • ስለ ናሚቢያ ፊዚካል ፖሊሲ (እ. ኤ. አ 1995)። ይህ ጥናት በናሚቢያ ካቢኔ ጸድቆ ተግባር ላይ ውሏል።

ክቡር አቶ ተፈራ ከአፍሪካ አገልግሎታቸውን አጠናቀው ዋሺንግተን ወደ አይ.ኤም. ኤፍ ዋና መስሪያ ቤት በመመለስ በልዩ ልዩ ክፍላተ በመጨረሻም በጡረታ እስከተገለሉ ድረስ የፕላን እና የበጀተ ከፍተኛ በላሙያ በመሆን ሰርተዋል።

ክቡር አቶ ተፈራ የ42 ዓመት የትዳር ጓደኛቸው ከሆኑት ከውድ ባላቤታቸው ከወ/ሮ ንግስተ ጌታቸው ሁለት ወንዶቸን ዶ/ር ሄኖክ ተፈራ፥ አቶ ዮሴፍ ተፈራንና እና አንድ ሴት ወይዘሪት ነፃነት ተፈራን አፍርተዋል። ሶስት የልጅ ልጆችንም ለማየት ታድለዋል።

ክቡር አቶ ተፈራ ወልደሰማዕት በተመደቡባቸው የስራ ኃላፊነቶች ሁሉ ቅንነት ታማኝነት ጥንቁቅነት እና ለአገር እና ለወገን ተቆርቋሪነትን የሚያንጸባርቅ ጠባይ ነበራቸው። አቶ ተፈራ በዚህች ዓለም አኗኗራቸው እና አረማመዳቸው ሁሉ ኃላፊነት የሚሰማቸው እና ለቤተሰባቸው ፍጹም ፍቅርና እንክብካቤ የሚያደርጉ ለወዳጆቻቸውም በሚፈለጉበት ጊዜ ፈጥኖ ደራሽ ነበሩ።

ህልፈት ህይወት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ክቡር አቶ ተፈራ ወደሚወድዋት አገራቸው ኢትዮጵያ ዘመዶቻቸውን እና ወዳጆቻቸውን ለማየት ሄደው ባለፈው መጋቢት ወር ወደ ዋሺንግተን እንደተመሉ የጤና መታወክ ገጥሟቸው በምርመራ ላይ እንዳሉ በድንገት እ. ኤ. አ. June 25 ቀን 2013 ከእኩለ ሌሊት በኋላ በተወለዱ በሰባ አራት ዓመታቸው በቦልቲሞር ከተማ ባለው በጆነስ ሆፕኪንስ ሆስፒታል ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። ሕመም ላይ በቆዩበት ጊዜ የውድ ባላቤታቸው እና የልጆቻቸው እንክብካቤ አንድም ቀን አልተለያቸውም፡፡

ዋቢ ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]