ኒኑስ

ከውክፔዲያ
ኒኑስ በሰዓሊው ጊዮም ሩዊ ዕይታ
(1545 ዓ.ም.)

ኒኑስ በጥንታዊ የግሪክ ታሪክ ጸሃፊዎች ዘንድ የነነዌ መስራችና የአሦር ንጉስ ነበረ። ለዘመናዊ ሥነ ቅርስ የታወቀ አንድ ግለሰብ አይመስልም፤ ዳሩ ግን የአያሌ ታሪካዊ ወይም አፈ ታሪካዊ ግለሰቦች ትዝታ በአንድ ስም በግሪኮች በኋለኛ ዘመን እንደ ተዘከረ አሁን ይታስባል።

የንጉሥ ኒኑስና ሚስቱ ንግሥት ሴሚራሚስ ስሞች በጽሁፍ መጀመርያ የተገኘው ክቴስያስ ዘክኒዱስ (400 ዓክልበ. ገዳማ) በጻፈው በፋርስ አገር ታሪክ ነው። ክቴስያስ ለ2 አርጤክስስ (2 አርታሕሻጽታ) የመንግሥት ሀኪም ሆኖ የፋርስ ነገሥታት ታሪካዊ መዝገቦች አንብቤያለሁ ብሎ አሳመነ።[1] ከዚህ በኋላ የግሪክ ታሪክ ጸሐፊ ዲዮዶሮስ ሲኩሉስ የክቴስያስን ወሬ አስፋፋ። የአለም ታሪክ ሊቃውንት እስከ 1880ዎቹ ድረስ የኒኑስ ታሪክ ዕውነት መሆኑን ይቈጠሩት ነበር። በዚያን ጊዜ የኩኔይፎርም ጽሕፈት ፍች ስለ ተፈታ፣ በሜስፖጦምያና በነነዌ ብዙ ቅርሶችም በመገኘታቸው፣ የአሦር ትክክለኛ ታሪክ ዕውቀት ተጨመረልን።

ኒኑስ የቤሉስ ወይም ቤል ልጅ ተባለ፤ ይህም ምናልባት በሴማዊ ቋንቋ ሥር «ባል» (ጌታ) የመሰለ ማዕረግ ሊሆን ይችላል። በካስቶር ዘሮድስ ዘንድ ኒኑስ ለ52 ዓመታት ነገሰ፤ ክቴስያስም እንዳለው መጀመርያው ዓመተ መንግሥቱ 2198 ዓክልበ. ነበረ። በ17 አመታት ውስጥ ኒኑስ በአረቢያ ንጉስ አርያዎስ እርዳታ ምዕራብ እስያን በሙሉ እንዳሸነፈ ተብሏል። ከዚህ ቀጥሎ የአርመን ንጉስ ባርዛኔስን (ይቅርታ የሰጠውን) እና የሜዶን ንጉስ ፋርኖስን (በስቅለት ይሙት በቃ የሰጠውን) ድል በማድረግ የአለም መጀመርያ ንጉሠ ነገስት እንደ ሆነ ተብሏል።

የኒኑስ መንግሥት ስፋት በዲዮዶሮስ ዘንድ

ግሪኮቹ እንደ ተረኩት፣ ይህ ኒኑስ በዙርያው ያሉትን እስያዊ አገሮች ከሕንድና ከባክትርያና በስተቀር በሙሉ አሸነፋቸው። ከዚያ ወዲያ ኒኑስ በ2 ሚሊዮን ወታደሮች ሠራዊት በባክትርያና ንጉሥ በኦክስያርቴስ ላይ ወረራ ጀመረ። አገሩ ሁሉ ቢወድቅም ዋና ከተማው ባክትራ ግን አልወደቀምና ሠራዊቱ ከበቡት። ባክትራን ሲከብቡት ኒኑስ የመኮነኑ ኦኔስ ሚስት ሴሜራሚስ አገኛትና ከባልዋ ነጥቆ እንደ ራሱ ሚስት ልትሆን ያዛት። ልጃቸው የኒኑስ ተከታይ ኒንያስ ሆነ።

ሮማዊ ታሪክ ጸሃፊ ኬፋልዮን (120 ዓ.ም. ገደማ) ጀምሮ፣ አንዳንድ ታሪክ ሊቅ የኒኑስ ተቃዋሚ ኦክስያርቴስ ሳይሆን፣ በዕውነት የባክትርያ ንጉሥ ዞራስተር እንደ ነበር ጽፈዋል።

ቅሌሜንጦስ ጽሁፎች በአንዱ ዕትም፣ የኒኑስ መታወቂያ ከናምሩድ ጋራ አንድላይ ነው በማለት ደራሲው ይኸው ሰው የእሳት አምልኮት ለፋርሶች ያስተማረ ነው ይነግረናል። በኦሪት ዘፍጥረት 10፡11-12 መሠረት የነነዌ መስራች የሴም ልጅ አሦር ቢባልም፣ በአንዳንድ ትርጉም ከእብራይስጥ መጽሐፍ ቅዱስ፣ የነነዌ መስራች ናምሩድ እንደ ነበር ይመስላል።

19ኛው ክፍለ ዘመን ሁለቱ ባቢሎኖች የጻፈው አሌክሳንድር ሂስሎፕ ሃልዮ፣ የናምሩድና የኒኑስ (እንዲሁም የዞራስተር) መታወቂያ አንድ መሆኑ ዋና ነጥብ ነው።

ክቴስያስና ዲዮዶሮስ እንዳወሩት፣ ከኒኑስ ሞት በኋላ ሴሜራሚስ እንደ ገደለችው ተከሰሰች። እርስዋ ግን ታላቅ መቅደስ ግንብ በባቢሎን ለማስታወሻው አሠራች። እርስዋ በተጨማሪ በእስያ መጨረሻው ነፃ ንጉሥ በሕንድ ንጉሥ ስትራቶባቴስ ላይ ዘመቻ እንዳደረገች አወሩ። ነገር ግን ድል ሆና ለልጅዋ ለኒንያስ ዙፋኗን ተወች ነበር።

ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ "Like a Bird in a Cage": The Invasion of Sennacherib, Lester L. Grabbe (2003), p. 121-122