ናምሩድ

ከውክፔዲያ
ናምሩድ በስኮትላንድ ሰዓሊ ደይቪድ ስኮት አስተያየት (1824 ዓም ተሳለ)

መጽሐፍ ቅዱስ እንዲሁም በአፈ ታሪክናምሩድ (ዕብራይስጥ נִמְרוֹד /ኒምሮድ/) የኩሽ ልጅ፣ የካም ልጅ ልጅ እና የኖህ ልጅ-ልጅ-ልጅ ሲሆን የሰናዖር ንጉሥና 'በእግዚአብሔር ፊት ኃያል አዳኝ' ይባላል። በመጽሐፍ ቅዱስ ስሙ የሚገኘው በኦሪት ዘፍጥረት 10፣ በዜና መዋዕልና በትንቢተ ሚክያስ ብቻ ነው። እነዚህ መጻሕፍት ስለ ናምሩድ ብዙ ባይነገሩንም፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጭ ስለሱ ያሉት ትውፊቶች ግን በርካታ ናቸው። ከነዚህም ትውፊቶች መካከል ከሁሉ የታወቀው የባቢሎን ግንብ እንዲገነባ ያዘዘ መሆኑ ነው።

በመጽሐፍ ቅዱስ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  • ኦሪት ዘፍጥረት 10፡8-10፦
«ኩሽም ናምሩድን ወለደ፤ እርሱም በምድር ላይ ኃያል መሆንን ጀመረ። እርሱም በእግዚአብሔር ፊት ኃያል አዳኝ ነበረ፤ ስለዚህም፦ በእግዚአብሔር ፊት ኃያል አዳኝ እንደ ናምሩድ ተባለ። የግዛቱም መጀመሪያ በሰናዖር አገር ባቢሎንኦሬክአርካድካልኔ ናቸው።»

መጽሐፈ ዜና መዋዕል ቀዳማዊ 1፡10 ከዚህ በላይ ምንም አይጨምርም። ትንቢተ ሚክያስም 5፡6፦ «የአሦርንም አገር በሰይፍ፥ የናምሩድንም አገር በመግቢያው ውስጥ ያፈርሳሉ» ያለው ነው።

በእብራይስጥ ትርጉም ኦሪት ዘፍጥረት 10፡11-12 ዘንድ ነነዌንና በነነዌ ዙሪያ ሌሎች ከተሞች የሠራው የሴም ልጅ አሦር ወይም ናምሩድ መሆኑ ግልጽ አይደለም። ስለዚህ በአንዳንድ ትርጉም ዘንድ በአሦር አገር ያሉትን ከተሞች የሠራው ደግሞ ናምሩድ ነበረ።

መጽሐፈ ኩፋሌ 8፡39 የኤቦር ሚስት አዙራድ «የአብሮድ ልጅ ናት» ሲል በግሪኩ ደግሞ በ«አብሮድ» ፈንታ «ነብሮድ» አለው፤ ይህም በግሪክ መጽሐፍ ቅዱስ «ናምሩድ» ማለት ነው። ናምሩድ የኤቦር አማትና የፋሌክ ቅድማያት ከሆነ፣ እንግዲህ አብርሃምና አይሁዶች ሁሉ ኢየሱስ ቢሆንም ከናምሩድ ከኩሽና ከካም ትንሽ ተወላጅነት አለባቸው ማለት ነው።

ዘፍጥረት በብዙ ጥንታዊ ግዕዝ ቅጂዎች የናምሩድ ስም ኑቤርድ ወይም ኑቤር ተጽፎ ይታያል፤ ይህም ከግሪኩ አጻጻፍ ነብሮድ የደረሰ ይሆናል። አንድ ግዕዝ ቅጂ ግን «ናምሩድ» አለው፤ ይህም ከአረብኛው አጻጻፍ ታረመ።

በአፈ ታሪክና በትውፊቶች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በአይሁድ ልማዶች ዘንድ በተለይ በታልሙድ እንደሚገኘው ናምሩድ የባቢሎን ግንብ እንዲሠራ ያዘዘው ነው። በአንዳንድም የአይሁዶች ምንጭ ዘንድ፣ ከአብርሃም ጋር የታገለው የባቢሎን ንጉስ አምራፌል (ዘፍ. 14፡1) እና ናምሩድ አንድ ናቸው። ፕሲውዶ-ፊሎ የሚባል የአይሁድ መጽሐፍ (70 ዓ.ም. ያህል ተጽፎ) እንደሚለው፣ ናምሩድ የነገደ ካም አለቃ ሲሆን፣ እንዲሁ ዮቅጣንነገደ ሴም አለቃ፣ የያዋንም ልጅ ዶዳኒም (ሮድኢ) ልጅ ፌኔክነገደ ያፌት አለቃ ሆኑ።

በ1ኛ ክፍለ-ዘመን የአይሁድ ታሪክ ጸሐፊ ፍላቪዩስ ዮሴፉስ ስለ ናምሩድ እንዲህ ብሎ ጻፈ፦

«እግዚአብሔርን ለመናቅና ለማቃለል ያበረታታቸው ናምሩድ ነበረ። እሱ የካም ልጅ ልጅ፣ ደፋር ሰው ነበረ፤ ታላቅ የእጅ ብርታትም ነበረው። ደስታቸው በእግዚአብሔር አማካይነት የደረሠ ሳይሆን ከገዛ ድፍረታቸው የተነሣ እንዲደሰቱ አሳመናቸው። ከዚህ በላይ ቀስ በቀስ መንግሥቱን ወደ አምባገነንነት ቀየረ፤ ሰዎችን ከአምላክ ፍርሃት ለማዛወርና ለራሱ ስልጣን ምንጊዜ ጥገኛ እንዲሆኑ ከማድረግ በቀር ሌላ ዘዴ አላወቀም ነበርና…

ብዙዎቹም የናምሩድን ውሳኔ እንዲከተሉ፣ ለእግዚአብሔርም መገዛት እንደ ቦቅቧቃነት እንዲቆጠሩ በጣም ተዘጋጁ። ግንብም ሠሩ፤ ምንም ጣር አላስቀሩም ወይም በምንም ረገድ ስራቸውን ቸል አላሉም። በስራው ላይ በተደረጉ እጆች ብዛት ምክንያት፣ ማንም ሳይጠብቀው ቶሎ ቶሎ እጅግ ከፍ ከፍ አለ፤ ሆኖም ውፍረቱ በጣም ግዙፍ በመሆኑ፣ ታላቅ ከፍታው ከርቀት ሲታይ ከእውኑ ያነሰው ይመስል ነበር። ውኃ እንዳይዘልቀው የተሠራው በዝፍት ከተመረገ ከተቃጠለ ጡብ ነበር። እግዚአብሔርም እንዲህ ያለ አእምሮ እንደ አደረጉ ባየ ጊዜ፣ በሙሉ እንዲያጠፋቸው አላሰበም፤ በቀድሞ ሐጢአተኞች ጥፋት ጥበበኛ አልሆኑምና፤ ነገር ግን ትርምስ አደረገባቸው፣ የተለያዩም ልሣናት አስገኘባቸው፣ በቋንቋዎች ብዛት ሳቢያ እርስ በርስ እንዳይግባቡ። ግንቡን ያገነቡበት ሥፍራ አሁን ባቢሎን ይባላል፤ ምክንያቱም አስቀድሞ በቀላል የገባቸው ቋንቋ ተደናገረና፤ አይሁዶች 'ባቤል' በሚለው ቃል 'ድብልቅ' ማለታቸው ነውና…»

ኪታብ አል-ማጋል የተባለው ጥንታዊ አረብኛ መጽሐፍ (ከ'ቄሌምንጦስ መጻሕፍት' መሃል) እንደሚለው፤ ናምሩድ ሐዳኒዩንን፣ እላሳርን፣ ሴለውቅያን፣ ክቴሲፎን፣ ሩሂን፣ አትራፓተነን፣ ተላሎንንና ሌሎችን ከተሞች ሠራ። የፋሌቅ ዕድሜ 50 አመት ሲሆን ናምሩድ ኒሲቢስን፣ ራሃን (ኤደሣ) እና ካራንን ሠርቶ ከዚህ በላይ የራግው ዕድሜ 163 አመት በሆነበት ወቅት ናምሩድ የዓለም ንጉስ ሆኖ ለ69 አመታት ነገሠ። በተጨማሪ ናምሩድ 'ጥቁር ጨርቅና ዘወድ በሰማይ አይቶ ሸማኔውን ሳሳንን ጠርቶ እሱ በእንቁ ሠሮቶት በራሱ ላይ ጫነው። እሱ መጀመርያ ዘውድ የጫነው ንጉስ ነበረ። ስለዚህ ነገር ምንም የማያውቁ ሰዎች ዘውድ ከሰማይ ወረደለት አሉ።' በኋላ መጽሐፉ ናምሩድ የእሳትና የጣኦት አምልኮት መሠርቶ ለ3 አመት የአስማት ትምህርት ከኖህ 4ኛ ልጅ ከ'ቡኒተር' እንደ ተቀበለ ይላል[1]

ጽርዕ የተጻፈው በዓተ መዛግብት (350 ዓ.ም.) ስለ ናምሩድ ተመሳሳይ ታሪክ አለው፤ ነገር ግን ናምሩድ ኒሲቢስን፣ ኤደሣንና ካራንን የሠራው የራግው ዕድሜ 50 አመት ሲሆን ነው፤ የናምሩድም ዘመን የጀመረው የራግው ዕድሜ 130 በሆነበት ወቅት ይባላል። በዚህ መጽሐፍ ደግሞ የሸማኔው ስም 'ሲሳን'፣ የኖህም አራተኛ ልጅ ስም 'ዮንቶን' ይባላል።

ቅዱስ ሄሮኒሙስ 380 ዓ.ም. ገዳማ በጻፉት ጽሕፈት እብራይስጥ ጥያቄዎች ስለ ኦሪት ዘፍጥረት እንደሚሉ፣ ናምሩድ በባቤል ከነገሠ በኋላ «ደግሞ የነገሠባቸው በኦሬክ እሱም ኤደሣ፤ በአርካድ እሱም አሁን ኒሲቢስ፣ በሐላኔ [ካልኔ] እሱም ስሙ ከተቀየረ በኋላ ስለ ንጉስ ሴሌውቆስ 'ሴሌውቅያ' አሁንም እንዲያውም 'ክተሲፎን' የሚባሉ ከተሞች ናቸው» ነገር ግን ይህ ልማዳዊ መታወቂያ በዘመናዊ ሊቃውንት አይቀበለም፤ የናምሩድ ከተሞች በሶርያ ሳይሆኑ ሁላቸው በሱመር ይገኛሉ ባዮች ናቸውና።

ግዕዝ የተጻፈው መጽሐፈ አዳምና ሕይዋን (ምናልባት ከ5ኛ ክፍለዘመን የታወቀ) ደግሞ ለበዓተ መዛግብት ተመሳሳይ ታሪክ አለው፤ በዚህ ግን የዘውዱ ሠሪ ስም 'ሳንጣል'፤ ናምሩድንም ያስተማረው የኖህ 4ኛ ልጅ ስም 'ባርውን' ይባላል።

በአይሁድ መጽሐፍ ፒርኬ ዴ-ረቢ ኤልኤዘር (826 ዓ.ም. ያህል) ዘንድ፣ ናምሩድ ከአባቱ ከኩሽ የአዳምና የሕይዋን ልብሶች ወረሰ። እኚህም ልብሶች የማይሸነፍ አደረጉት ይላል። ከዚያ የናምሩድ ወገን ነገደ ያፌትን ድል በማድረግ ላዕላይ ገዚነት ተቀበለ። በኋላ ዔሳው (የአብርሃም ልጅ-ልጅ) ናምሩድን ገደለው። ይህ ተረት እንደገና ከ1618 ዓ.ም. በሚታወቀው «ያሻር መጽሐፍ» በሚባለው ሚድራሽ ይገኛል። ከዚህ በላይ የናምሩድ ልጅ ማርዶን በክፋት ከአባቱ እንደበለጠ ይጨምራል።[2]

በ9ኛ መቶ ዘመን 'የነቢያትና የነገሥታት ታሪክ' የጻፉት የእስላም ጸሓፊ ሙሐመድ እብን ጃሪር አል-ታባሪ ይህን የመሰለ ተረት ያቀርባል ። በዚህ መሠረት ናምሩድ ግንቡን በባቢል (ባቢሎን) አስገንቦ አላህ አጠፋውና የሰው ልጅ ቋንቋ ከዚያ ቀድሞ የሶርያ (አራማያ) ሲሆን የዛኔ ወደ 72 ልሣናት ይደባለቃል። ከዚያ በላይ ደግሞ በ13ኛ መቶ ዘመን የጻፉት ሌላ የእስላም ታሪከኛ አቡ አል-ፊዳ ይህን መሰል ታሪክ ሲያወራ የአብርሃም ቅድመ-አያት ዔቦር ግንቡን ለመሥራት እምቢ ስላለ የፊተኛው ቋንቋ ዕብራይስጥ እንዲቀርለት ተፈቀደ ብሎ ይጽፋል።

ሀንጋሪ አፈ ታሪክ ደግሞ የሀንጋሪ ሰዎች አባቶች ወንድማማች 'ሁኖር' እና 'ማጎር' ሲሆኑ እነኚህ የታና ልጅ መንሮጥ እና የሚስቱ የኤነሕ መንታዎች ይባላሉ። በአንዳንድ ትውፊት ይህ መንሮጥ የኩሽ ልጅ ናምሩድ እንደ ነበር ይባላል። ጥቂት ደራሲዎች የ'ታና' እና የ'ኩሽ' ስሞች ከታሪካዊ ሱመራዊ የኪሽ ንጉሥ ኤታና ጋር እንዲሁም ከኩሻን መንግሥት (እስኩቴስ) አባት 'ኩሽ-ታና' ጋር ያለውን ተመሳሳይነት አጠቁመዋል። ሆኖም በአንድ መጽሐፍ ዘንድ የሁኖርና የማጎር አባት የኤነሕም ባል ናምሩድ ሳይሆን የኖህ ልጅ ያፌት ነበረ።

አርሜኒያ አፈ ታሪክ ዘንድ፣ የአርሜኒያ ሕዝብ መስራች ሐይክ ናምሩድን በቫን ሐይቅ አጠገብ በተካሔደ ፍልሚያ አሸንፎት ነበር።

ዩናይትድ ስቴትስ በሚገኘው በሞርሞን ሃይማኖት መጻሕፍት ዘንድ፣ ልሣናት በተደባለቁበት ጊዜ የ'ያሬድ' ወገኖች መጀመርያውን ቋንቋ ጠብቀው በስሜን ቅርብ ወደ ሆነ፣ ስለ አዳኙም 'ናምሩድ' ወደ ተባለ ሸለቆ እንዲጓዙ ታዘዘ።

ክፉ ናምሩድና ጻድቁ አብርሃም[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በመጽሐፍ ቅዱስ ስለ ናምሩድና አብርሃም ምንም ግንኙነት የለም። እንዲያውም ከሁለቱ መካከል 7 ትውልዶች አሉ። ይሁንና በሐሣዊ ፊሎ ጽሕፈት[3]; በተልሙድም፣ በመካከለኛው ዘመን ረቢዎች ጽሕፈቶች[4] እና በዛሬም አይሁዶች ልማድ ዘንድ፤ ናምሩድና አብርሃም በአንድ ጊዜ የኖሩ ጠላቶች ያደርጋቸዋል። በዚሁ ትውፊት፣ አብርሃም ናምሩድን ስለ ጣኦት አምልኮት ይገሥጸዋል። በቤተ እሥራኤል ጽሕፈት ትዕዛዘ ሰንበት ተመሳሳይ እምነት ይተረካል። እዚህ ግን ናምሩድ የከነዓን ንጉሥ ይባላል።

በኢብራሂም (አብርሃም) እና ባልተሰየመ ንጉሥ መሃል ያለው ተመሳሳይ ክርክር ደግሞ በእስልምና ቁርዓን ይገኛል። በአይሁድ ምንጮች መሠረት፣ የእስላም ሊቃውንት ይህ ንጉሥ ናምሩድ ነበር ይላሉ። ናምሩድ የፈላጭ ቁራጭና የክፋት አራያ ሆኖ በእብራይስጥ 'ናምሩድ ክፉው' (נמרוד הרשע) በአረብኛም 'ናምሩድ አል-ጃባር' (አምባገነን) ይሠየማል።

ሌሎች አስተያየቶች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የታሪክም ሆነ የአፈታሪክ ሊቃውንት ለረጅም ዘመን የናምሩድን መታወቂያ ለመገመት ሙከራዎች አድርገዋል።

የከለዳውያን ጸሐፊ ቤሮስስ በ3ኛው ክፍለ ዘመን ዓክልበ. እንደ ጻፉ፣ ከማየ አይኅ በኋላ መጀመርያው ንጉሥ የከላውዴዎን ንጉሥ «ኤወኮዮስ» እንደ ነበር መሠከረ። ስለዚህ በ4ኛው ክፍለ ዘመን ዓ.ም. በክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ አውሳብዮስ አስተያየት ይህ ኤወኮዮስና ናምሩድ አንድ ነበሩ። ከዚህም ጋር በ200 ዓ.ም. ግድም የጻፉት ክላውዲዩስ አይሊያኑስ እንዳለው፣ «ኤወኮሮስ» የባቢሎን ንጉሥና የ«ጊልጋሞስ» አያት ይባላል። የዛሬው ሊቃውንት እምደሚያስቡ፣ የዚህ «ኤወኮሮስ / ኤወኮዮስ» መታወቂያ በተጨማሪ ከኩኔይፎርም ሰነዶች ከታወቀው ከኡሩክ (ኦሬክ) ጥንታዊ መስራች ከኤንመርካር ጋር አንድ ላይ ነው።[5] በጥንታዊ ጽሑፍ ኤንመርካርና የአራታ ንጉሥ ዘንድ፣ ኤንመርካር የግንብ መቅደስ በኡሩክ (ኦሬክ) እና በኤሪዱ (ባቢሎን እንደመሰለው) ሠርተው ነበር። «ባቢሎን» ማለት የኤሪዱ መጠሪያ እንደ ነበር የሚል ማስረጃ በሌሎችም ጥናቶች አለ።[6]

ሌሎች ሊቃውንት ለናምሩድ የተለያዩ መታወቂያዎች አቅርበዋል። የ4ኛው ሮማ ፓፓ ቅሌምንጦስ በጻፉት ደብዳቤ መሠረት፣ ናምሩድ የፋርስ ሃይማኖት ሰባኪ ዞራስተር (ዛራጡሽትራ) ነበረ [7]። ደግሞ የባቢሎን አምላክ ሜሮዳክ አፈ ታሪክ ከናምሩድ ሕይወት እንደ ተወሰደ ተብሎአል። ሌሎች ሃሣብ ናምሩድ በዕውኑ የአሦር ንጉሥ 1ኛ ቱኩልቲ-ኒኑርታ [8] ነበር ይላል። አሌክሳንድር ሂስሎፕ በ19ኛ ክፍለ ዘመን የጻፈው በግሪክ አፈ ታሪክ ዘንድ የመስጴጦምያ ንጉስና የሴሚራሚስ ባል ኒኑስ ተመሳሳይነት አየ።

በሱመራውያን ነገሥታት ዝርዝር የአካድ መስራች ታላቁ ሳርጎን ስለሆነ እንዲሁም በባቢሎን ዜና መዋእል ስነድ (ABC 19:51) ሳርጎን የባቤል መስራች ስለ ሆነ፣ አንድ ሃልዮ ሳርጎንንና ናምሩድን አንድ ያደርጋቸዋል። ነገር ግን ሌሎች ጽሕፈቶች አካድ ከሳርጎን አስቀድሞ በኤንሻኩሻና እና በሉጋልዛገሢ ዘመናት እንደ ነበር ስለሚመሰክር ይህ ሃሳብ ተጠይቋል። በተጨማሪ ሌላ ሰነድ (ABC 20:18-19) ሳርጎን ባቢሎንን ወደ አካድ ዙሪያ እንዳዛወረው ይላል።

ዋቢ ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  • The Legacy of Mesopotamia; Stephanie Dalley et al. (Oxford, Oxford University Press, 1998)
  • Noah's Curse: The Biblical Justification of American Slavery; Stephen R. Haynes (NY, Oxford University Press, 2002)
  • "Nimrod before and after the Bible" K. van der Toorn; P. W. van der Horst, The Harvard Theological Review, Vol. 83, No. 1. (Jan., 1990), pp. 1-29
  1. ^ ኪታብ አል-ማጋል (በእንግሊዝኛ ትርጉም)
  2. ^ See Louis Ginsberg Legends of the Jews Vol I, and the footnotes volume.
  3. ^ van der Toorn and van der Horst 1990, p. 19
  4. ^ [1]
  5. ^ Wouter F. M. Henkelman, "The Birth of Gilgamesh", in Altertum und Mittelmeerraum: die antike Welt diesseits und jenseits der Levante, p. 819.
  6. ^ "Babylon as a Name for Other Cities..." Archived ጁላይ 30, 2012 at the Wayback Machine p. 25-33. (እንግሊዝኛ)
  7. ^ Homily IX
  8. ^ Dalley et al., 1998, p. 67

የውጭ መያያዣዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]