አራም (የሴም ልጅ)
አራም ሴም (ዕብራይስጥ፦ אֲרָם) በመጽሐፍ ቅዱስ ኦሪት ዘፍጥረት (ምዕ. 10) መሠረት የኖህ ልጅ ሴም ከወለዱት ልጆች አንድ ሲሆን የዑፅ፣ ሁል፣ ጌቴርና ሞሶሕ አባት ይባላል።
በጥንቱ ታሪክ ጸሐፊዎች ዘንድ፣ ይህ አራም የስሜን ሜስጶጦምያና የሶርያ ሕዝብ የአራማውያን አባት ነበር። በኤብላ ጽላቶች ላይ (2300 ዓክልበ. ግድም) «አራሙ» እና «አርሚ» የሚሉ ስያሜዎች ይገኛሉ፤ «አርሚ» የሐላብ (አሌፖ) ስም ነበር። በ2250 ዓክልበ. ያሕል በአካድ ንጉሥ ናራም-ሲን በስሜን ተራሮች በተደረገው ዘመቻ «የአራም አለቃ ዱቡል» እንደማረከው ይመዘገባል።[1] የአራም ሕዝብ ወይም አገር ደግሞ በማሪ ጽላቶች (1900 ዓክልበ. ግድም) እና በኡጋሪት ጽላቶች (1300 ዓክልበ. ግድም) ታይተዋል። ሆኖም እነዚህ ስያሜዎች ትርጉሞች ለሊቃውንት ክርክር ሆነዋል፤ የአራም ሕዝብ መኖሩ ከ1100 ዓክልበ. ጀምሮ በእርግጥ ይታወቃል።
በመጽሐፈ ኩፋሌ (9፡19) መሠረት፣ የኖህ ልጆች ምድሪቱን ሲያከፋፈሉ የአራም ልጆች የወረሱት ርስት ከኤፍራጥስና ከጤግሮስ ወንዞች መካከል ያለው አገር ሁሉ ያጠቅልል ነበር። ይሁንና በታሪካዊው ዘመን አራማውያን ይህን አገር በሙሉ ሠፍረው አያውቁም።
በብሉይ ኪዳን የተጠቀሰው ካራንንም ከተማ የጠቀለለው ሀገር «አራም-ናሐራይን» (የሁለት ወንዞች አራም) እንዲሁም በአካባቢው የተገኙት አራም-ደማስቆና አራም-ረሆብ በአራም ልጆች እንደ ተመሰረቱ ይታመናል።
ደግሞ የሴም ልጅ አራም በማንዳያውያን ሃይማኖት እንደ ነቢይ ሆኖ ይከብራል።
|
|||||||||||