አብርሀም ሊንከን
ከWikipedia
አብርሀም ሊንከን (እንግሊዝኛ፦ Abraham Lincoln፣ የካቲት 6 ቀን 1801 ዓ.ም. - ሚያዝያ 8 ቀን 1857 የኖሩ) ከ1853 እስከ 1857 ዓ.ም. ድረስ 16ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ነበሩ። በ1857 አ.ም. ከብሔራዊው ጦርነት ቀጥሎ ገና ፕሬዚዳንት እየሆኑ ተተኩሰው ተገደሉ።
የአብርሀም አባት ማሀይም ገበሬ ቢሆንም፣ አብርሀም ከልጅነት ጀምሮ እራሱን በጥጋት ያስተምር ነበር። በ1826 ለኢሊኖይ ክፍላገር ምክር ቤት መቀመጫ ተመረጡ። የሕግ ትምህርት በጉልበት አጥነው የሕግ አዋቂ ሆኑ። ከ1829 ዓ.ም. ጀምሮ የባርነት ተቃዋሚ ሆነ። ከአፍሪካ የተወሰዱት ጥቁር ሕዝቦች በግብርና መሥራት እንዲገደዱ ትክክለኛ ወይም ጥሩ ሀሣብ አይደለም ብለው አመኑ። ዳሩ ግን በ1834 ብዙ ባርያዎች ባገለገሉበት ቤተሠብ ውስጥ ያደገችውን ሚስታቸውን ሜሪ ቶድን አገቡ። ሜሪ ያለ ባርያዎች ከባልዋ ጋር በመኖር ትንሽ ተቸግራ ሩቅ ባልሆነ ግዜ ውስጥ ግን ተለመደችና በተከተሉት አመታት ላይ 4 ወንድ ልጆችን ወለዱ።
በ1838 ዓ.ም. የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጄምስ ፖልክ በሜክሲኮ ላይ ጦርነት ባደረገ ጊዜ አብርሀም ሊንከን የዚህን ጦርነት ተቃዋሚ ነበሩ። በ1846 ዓ.ም. የባርነት ተቃዋሚዎች ወገን ሪፐብሊካን ፓርቲ መሠርተው አብርሀም ከፍተኛ ሚና አጫወቱ። በ1852 ፕሬዚዳንት ምርጫ ዘመቻ፣ እሳቸው የሪፐብሊካን ዕጩ ሆኑ። ምርጫው በተደረገበት ቀን በጥቅምት 28 ቀን 1853 ዓ.ም.፣ ሊንከን አሸነፉ።
ይህም የሆነ የሕዝቡ ብዛት በአገሩ ስሜን እየኖረ የሬፑብሊካን ደጋፊዎች ነበሩ። በስሜኑ ክፍላገሮች ደግሞ፣ ባርነት ከዚህ በፊት ተክለክሎ ነበር። በአሜሪካ ደቡብ በተገኙ ክፍላገሮች ግን ባርነት ገና የተለመደ ከመሆኑ በላይ በጥጥ የተመሠረተው የምጣኔ ሀብታቸው አስፈላጊነት መሰላቸው። ስለዚህ የባርነት ተቃዋሚ ሊንከን ፕሬዚዳንት መሆኑ በደቡብ ያሉት ክፍላገሮች ከአሜሪካ መገንጠላቸው ማለት ነበር። እንዲሁም ከምርጫው ቶሎ ተቀጥሎ ማዕረጉንም እንኳን ገና ሳይይዙ፣ ሳውስ ካሮላይና በታኅሣሥ 12 ቀን 1853 ዓ.ም. መገንጠሏን አዋጀች። በጥቂት ግዜ ውስጥ ሌሎች የደቡብ ክፍላገሮች እንዲህ አዋጁና በጥር 25 ቀን ቴክሳስ 7ኛው ሆነ። ከዚያ ቀጥሎ እነዚህ 7 ክፍላገሮች በሞንትጎመሪ፣ አላባማ ተባብረው አዲሱ መንግሥት የአሜሪካ ኮንፌዴራት ክፍላገሮች (CSA) ተባሉ። በየካቲት 26 ሊንከን የፕሬዚዳንትነቱን ማዕረግ በተቀበሉበት ቀን አገሩ በተግባር በ2 ተከፋፍሎ ነበር። የደቡብ ፕሬዚዳንት ጄፈርሰን ዴቭስ ሆኑ። የደቡብ ክፍላገሮች ለጦርነት ተዘጋጁና ምሽጎች ከUSA ሠራዊት ሊይዙ ጀመር። በሚያዝያ 5 ቀን ፎርት ሰምተር ምሽግ በሳውስ ካሮላይና በግፍ ስለ ተያዘ ጦርነቱ ጀመረ። ስለዚህ ሊንከን ከስሜኑ 75,000 ሰዎች ለዘመቻ ጠሩ። ከዚህ በኋላ ሌላ 4 ደቡብ ክፍላገሮች ተገንጥለው ለCSA ተጨመሩ። የደቡብ ዋና ከተማ ለዋሺንግተን ዲሲ ቅርብ ወደ ሆነው ወደ ሪችሞንድ፣ ቪርጂንያ ተዛወረ።
በጦርነቱ የስሜን ሠራዊት ከብዛታቸው የተነሣ በ4 አመት ውስጥ አሸነፉ። በዚህ ጊዜ ላይ ሊንከን ለአመጸኖቹ ባርዮች ነጻነት አዋጁ። ያላመጹ ዜጎች ባርያዎች ግን በዚያን ግዜ ነጻ አልወጡም። በ1856 ሊንከን በቀላል ለ2ኛ ዘመን ለፕሬዚዳንትነት ተመረጡ። በሚያዝያ 2 ቀን 1857 ዓ.ም. የኮንፌደራት ሠራዊት እጁን ሰጠ። ነገር ግን ከ6 ቀን በኋላ በነፍሰ ገዳዩ በጆን ዊልክስ ቡስ እጅ ተተኲሰው ሞቱ። ከዚህም ትንሽ በኋላ ባርነት በሕግ በሙሉ ተክለክሎ የተረፉት ባርያዎች ነጻነት አገኙ።