አጋታርከስ

ከውክፔዲያ

አጋታርከስ (Ἀγάθαρχος) ወይንም (Ἀγαθαρχίδης) ከክርስቶስ ልደት በፊት በሁለተኛው ክፍለ ዘመን (200-130 ዓ.ዓ.) ይኖር የነበር የግሪክ መልክዓ ምድር ተመራማሪ ነበር። ግሪክ ውስጥ ናይደስ እምትባል ቦታ የተወለደው አጋርታከስ በኋላ ወደ አሌክሳንድሪያ ሄዶ ግብጽ ውስጥ እንደኖረ ታሪኩ ይገልጻል። በግብጽ ህይወቱ ውስጥ መጀመሪያ አስተማሪነት ቢቀጠርም በኋላ ግን የሄራክሊደስ ጸሐፊ ለመሆን በቃ። ሄራክሊደስ እንግዲይ የቶሎሚ 6ኛ ወዳጅ የነበረና በኋላ ከአንጾክዮስ ጋር በተደረገው ጦርነት ወደ ሶሪያ አምባሳደር ሆኖ የተሾመ ነው። በሁለቱ ጦረኞች መካከል የሰላም ድርድር ሲደረግ ሄራክሊደስ ተካፋይ ስለነበር የአጋርታከስ የጠለቀ ዕውቀት በዚህ ጊዘ ከነበረው መረጃዎችን የመፈተን ዕድል ይመነጫል። ሆኖም በኋላ ቶሎሚ 8ኛ ሲነግስ ማናቸውም በቶሎሚ 6ኛ ጥቅም ያገኙ ጠቢባን እንዲሰደዱ እንጂ እንዳይጠቀሙ አዋጅ ወጣ። ስለሆነም አጋርታከስ እና ሌሎች ተማሪዎች ለብዙ ዘመን ከኖሩባት አሌክሳንድሪያ እንዲሰደዱ ሆነ።

ስራዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

አጋርታከስ ብዙ ሰፊና ትላልቅ ጽሑፎችን አቅርቧል። ለዚህ መሰረቱ በሄራክሊደስ አማካይነት የንጉሱን መዝገብ ቤት ፋይሎች ለመመርመር ስለቻለ እንደሆነ ግምት አለ። ከስራዎቹ ውስጥ የእስያ ታሪክ (10 መጻሕፍት)፣ የአውሮጳ ታሪክ (49 መጻሕፍት)፣ እና ስለ ቀይ ባሕር (5 መጻሕፍት) የተሰኙት ተጠቃሽ ናቸው። ከስራዎቹ ስፋትና ጥልቀት አንጻር በኋላ ለተነሱ ብዙ የመልክዓ ምድር እና ታሪክ ጸሐፍት መሰረት በመሆን አገልግሏል። ምንም እንኳ በአሁኑ ዘመን አብዛኛወቹ የአጋርታከስ ስራዎች የጠፉ ቢሆንም በጥንቱ ዘመን ጽሑፎቹ በብዛት የተሰራጩ እንደነበር ይገመታል። ከድዮዶረስ ሴኩለስ እስከ ፖዚዶኒዮስ ድረስ የአጋርታከስ ስራቸው በሰፊው ይገኙባቸዋል። ታሪክንና ፍልስፍናን አቀናጅቶ ለማቅረብ የሞከረበት ስራውም በፖይዚዶኒዮስ ዘንድ ተቀባይነትንና ቀጣይነትን ያገኘ ነበር።