ኢንጋይዎን
ኢንጋይዎን (ወይም ኢንግዋዮን፣ ኢንጌዎን) በጥንታዊ ጀርመናውያን ነገዶች መካከል አንዱ ዋና ክፍል ነበር። ስሙ በሮማውያን ታሪክ ጸሐፍት እንደ ታኪቱስና ፕሊኒ ዘንድ ይታወቃል።
ታኪቱስ (90 ዓ.ም.) እንደሚለን፣ በጀርመናውያን «ጥንታዊ ዘፈኖች» መሠረት በጥንት ማኑስ ሶስት ልጆች ነበሩት። እነኚህም 3 ልጆች ሦስት ንዑስ-ብሔሮች ወለዱ፦
ፕሊኒ (70 ዓ.ም. ግድም) እንደ ጻፈው፣ ጀመናውያን በ5 ንዑስ-ብሔሮች ተከፋፈሉ፤ አራቱም ኢንግዋዮን፣ ኢስትዋዮን፣ ሄርሚዮን፣ ዋንዲሊ ናቸው (የ5ኛውን ነገድ ስም አይገልጽም)። በኢንግዋዮን ነገዶች መካከል ኪምብሪ፣ ቻውኪና ቴውቶን የተባሉ ጎሣዎች እንደ ኖሩ ይለናል።
አኒዩስ ዴ ቪቴርቦ በ1490 ዓ.ም. ባሳተመው ጽሑፍ ዘንድ፣ ቤሮሶስ ብዙ መዝገቦች አቅርቦ ነበር። በዚህ በኩል፣ የማኑስ ልጅ ኢንጋይዎን የሳርማትያ እና የጀርመን አገሮች ሦስተኛው ንጉሥ ነበር። ኢስታይዎን ባይጠቀስም ሄርሚኖን ከኢንጋይዎን በኋላ እንደ ነገሠ ይጨምራል።
በ1513 ግድም ጀርመናዊው መምህር ዮሐንስ አቬንቲኑስ የጀርመን አገር ዜና መዋዕል አሳተመ፤ በዚህም ውስጥ እንዳለው፣ በጥንት ጀርመኖች በ5 ብሔሮች ተከፋፈሉ፤ እነርሱም ዋንዳሊ፣ ኢንጌዎን፣ ኢስቴዎን፣ ሄርሚኖን፣ እና ባስተርናይ ናቸው። የኢንጌዎን ነገዶች ከማኑስ ልጅና ተከታይ ንጉሥ ኢንጌዎን ተወለዱ፤ እነዚህም በስሜን ባሕር ላይ የተገኙ ሕዝቦች ቻውኪ፣ ኪምብሪ፣ ቴውቶኖች፣ ፍሪዚ፣ ሳክሶኖችና ዳኖች ነበሩ።
አቬንቲኑስ እንደሚዘግበው፣ በኢንጌዎን ዘመን፣ የጥራክያ ንጉሥ ሊኩርጉስ ሁለት አለቆች ሞፕሱስንና ሲፒሉስን ከሳቫ ወንዝ ዙሪያ ወደ ኢንጌዎን ግዛት አባረራቸው። ከዚህ በኋላ የሊብያ አማዞኖች ንግሥት ሚሪና ሶርያንና ትንሹን እስያ ይዛ በአውሮጳ ገባችና እስከ ዳኑብ ወንዝ ድረስ ዘመተች። ጀርመንን ከሠራዊቷ ጋር ለመውረር ስትል ግን፣ ኢንጌዎን 2ቱን አለቆች ሞሱስንና ሲፒሉስን ልኮ በሳቫ ወንዝ ላይ በትልቅ ውጊያ አሸነፉአትና ተገደለች። ተመሳሳይ አፈ ታሪክ በግሪኩ ዲዮዶሮስ ሲኩሉስ መጽሐፍ (III. 55) ይገኛል።
ኢንጌዎን ለ45 ዓመት (2185-2140 ዓክልበ. ግድም) ከነገሠ በኋላ ሞተና ልጁ (ወይም እንደ ታኪቱስ፣ ወንድሙ) ኢስቴዎን በጀርመን ዙፋን ላይ ተከተለው ይላል።