ዒዛና

ከውክፔዲያ
ንጉሥ ዒዛና
በዒዛና አስተዳደር ዘመን የንግድ ልውውጥ ይደረግባቸው የነበሩ ገንዘቦች
የአክሱም ንጉሥ
የሚቀድመው አላ አሚዳ(አባቱ)
የሚከተሉት አብርሃወ አፅበሐ (ልጆቹ)
የኢትዮጵያ ነገሥታት


ዒዛና (በግሪክኤይዛናስ) ፣ (ወደ ፬ኛው ክ/ዘ አጋማሽ ዓ.ም.) ፣ ከአክሱም ነገስታት ሁሉ ገናና የሆነ የመጀመሪያው ክርስትያን ንጉሥ ነበር ። ምናልባት ለአባቱ ለንጉሥ ኢላ-አሚዳ ፡ የበኩር ልጁ ሳይሆን አይቀርም ። ስለ እናቱ ሥም የሚናገር ታዓማኒ የጽሑፍ መረጃ እስካሁን ድረስ አልተገኘም ። ከሁለተኛ ደረጃ ምንጮች መሠረት ግን የእናቱ ሥም ሶፍያ ይባላል ።

ሁለቱ ወንድሞቹ ሣይዛና እና ኃደፋ በአስተዳደር እና በውትድርና ሥራዎች ይረዱት ነበር ። በተለያዩ ጊዜያት ባደረጋቸው ተከታታይ የግዛት ማስፋፍያ ዘመቻዎች ፡ ንጉሥ ዒዛና ግዛቱን በስሜን ቤጃዎች፣ ካሡኖባ በተባሉ የተከዘ ቀበሌዎች ፣ በአትባራ እና በአባይ ወንዞች ፣ በምስራቅ በኩል በአግወዛት ፣ በደቡብ ስራኔ በተባለ የአፋን ምድሮች ላይ ወረራ እንደፈጸመ በግዕዝ ፣ በጥንታዊ ዐረብኛ ፣ እና በግሪክ ተጽፈው በአክሱም የተገኙ የጽሑፍ መረጃዎች ያመለክታሉ ። የግዛት ማስፋፍያ ዘመቻዎቹ ቅደም ተከተል ግን እስካሁን አከራካሪ ናቸው ።

የዒዛና የጦር ስልት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ንጉሥ ዒዛና ከሚጠቀሱለት የአስተዳደር ባሕርያት ውስጥ፤ የተቀናቃኞችን እና የአመፀኞችን ግዛቶች ካስገበረ በኋላ በምሕረትና በበጎ አስተዳደር ሥርዓት መተካቱ ፣ የአመፀኞችን ኃይል ለመስበር የሚያደርጋቸው የርስት ነቀላና የተለዋጭ ሠፈራ እርምጃዎች ተጠቃሽ ናቸው ። የዙፋኑ ሥያሜም ፦ ዒዛና የአክሱም፣ ሕምያርራይዳንሳባሳልሄንሲያሞቤጋ (ቤጃ) እና ካሡ ንጉሥ ነበር ።

የግዛቱ ክልል[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የደቡብ ዓረብያ ግዛቶች ሥም በዙፋኑ ሥያሜ መካተታቸው ከንጉሣዊ ራዕይ ወይም ምኞት የመነጩ እንጂ በእርግጥም በግዛቱ የተጠቃለሉ የባሕር ማዶ አውራጃዎች ናቸው ለማለት የሚያበቃ በቂ መረጃ የለም ። ከወርቅ፣ ከብር እና ከነሓስ በተቀረጹት ገንዘቦቹ ላይ «ዒዛና ዘሐለን ፣ የአክሱሞች ንጉስ» የሚል ጽሑፍ ይነበባል።

ንግድን በሚመለከት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በንጉሥ ዒዛና ዘመን ፡ አክሱማውያን በዓለም-ዓቀፍ ንግድ ረገድ እንደ ዝሆን ጥርስ፣ ወርቅ፣ የዔሊ ክዳን ፣ ቆዳ፣ ቅመማ ቅመም ወዘተ ወደ ውጭ ይልኩ እንደነበር፤ እንዲሁም ከወደ ሕንድ የሚመጡ ሽቀጦችን በመጨመር ከግሪኮችና ከሮማዊያን ጋር የአዱሊስ ወደብን በመጠቀም የንግድ ልውውጥ ያካሂዱ እንደነበር፣ በመዲናዋም የውጪ ዜጎችን ጨምሮ፣ ነጋዴዎች እና በልዩ ልዩ የሙያ መስኮች የተስማሩ በርካታ ነዋሪዎች ይኖሩባት እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ ።

ሃይማኖትን በሚመለከት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በንጉሥ ዒዛና ዘመን ዋንኛው ተጠቃሽ ክስተት ክርስትናን ከፍሬምናጦስ አምኖ መቀበሉ ነው ። ሆኖም የክርስትና እምነት ወደ ኢትዮጵያ በ 4ኛው ክ/ዘ የመጀመሪያ ዓስርተ ዓመታት ውስጥ ቀደም ብሎ መግባት ጀምሮ ነበር ። በቅድመ ክርስትና ዘመኑ ፡ ንጉሥ ዒዛና አስቴርመድርቤኄርሜኅረምአረስ በተባሉ አማልክት ያምን እንደነበረና እራሱንም የነዚህ አማልክት ልጅ አድርጎ ይቆጥር እንደነበር በጽሑፍ የተገኙ መረጃዎች ያሳያሉ ። በኋለኛ ዘመኖቹ ደግሞ የአሃዳዊ መለኮታዊ አምላክ አማኝ ስለመሆኑ የሚመስክሩ ጽሑፎች ተገኝተዋል ። በ 1969 በተገኘ የመረጃ ሰነድ ላይ ፡ ንጉሥ ዒዛና በግልፅ ክርስትያን ስለመሆኑ ሳያሻማ ይናገራል ። በዘመኑ የተቀረፁት ሳንቲሞቹ ላይ የጨረቃና-ኮከብ የቅድመ ክርስትና ምልክቶች ቀስ በቀስ ፡ የመስቀል ምልክቶች ባላቸው ሳንቲሞች እየተተኩ ሄደዋል ። እንዲሁም የአርያኖች ንጉሥ ቆንስጣንጢኖስ (፫፻፳፱-፫፻፶፫) የላከው «ለተወደዱት ሁለት ወንድሞቼ ዒዛና እና ሳይዛና ፡ የአክሱም ነገስታት» በማለት የሚጀምረው ታሪካዊ ደብዳቤ ስለ ፍሬምናጦስ ጵጵስና እና ዕውቅና ጉዳይ በሚመለከት ግለስቡን ወደ እስክንድርያ ፓትርያርክ አትናቴዎስ ዘንድ እንዲልኩት የሚጠይቀው ይህ ደብዳቤ እንደ ተጨማሪ መረጃ የሚያገለግል ስነድ ነው ። ፍሬምናጦስን ከዚሁ ደብዳቤ መላክ ሃያ አምስት ዓመት ቀደም ብሎ በኢትዮጵያ ጳጳስ አድርጎ ሾሞ የላከው ይኸው ንጉስ አትናቴዎስ ነበር ።

መታወቂያው[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በነገስታት ዝርዝር ላይ የንጉሥ ዒዛና ሥም አለመታወቁ ያስገርማል ። ሆኖም በሳንቲሞቹ ላይ ያለው ሥምይኸው «ዒዛና» የሚለው ነው ያለው ። በዘልማድ እንደሚነገረው ግን ፡ ንጉሥ አብርሃ(አበራ,ብርሃን አመጣ) እና ወንድሙ አጽብሃ(አነጋ,ጨለማን አባረረ) ክርስትና ወደ ኢትዮጵያ በገባበት ዘመን ኢትዮጵያን የሚገዙ ወንድማማች ንጉሦች ነበሩ ። ምናልባት ክርስትናን በተቀበሉበት ጊዜ የወስዱት የክርስትና ሥማቸው ሊሆን ይችላል ።

ስለ ንጉሥ ዒዛና ዘመነ ንግስ ፍፃሜ ወይም ስለ አሟሟቱ የሚዘረዝር ተጨባጭ መረጃ እስካሁን አልተገኘም ። በአፈ-ታሪክ መረጃዎች መሠረት ግን ንጉሡ በምዕራብ ኢትዮጵያ አካባቢ በተደረገ ጦርነት በጀብድ ወድቆ እንደሞተ እና አስከሬኑም ወደ ምስራቅ ትግሬ መጥቶ እንደተቀበረ ይነገራል ።

ምንጭ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  • ዲክሽነሪ ኦፍ ኢትዮጵያን ባዮግራፊ፣ ቮልዩም 1፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ ጥናት ማዕከል፣ 1975 (በእንግሊዘኛ የታተመ)
  • Compiled by Ayele Addis