ደርግ

ከውክፔዲያ

°

የኢትዮጵያ ጊዜያዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ

ደርግ ከሰኔ 21፣ 1966 እስከ 1983ዓ.ም. በኢትዮጵያ ሰፍኖ የነበር የወታደራዊ አገዛዝ ስርዓት አይነት ነበር። ደርግ የሚለው ቃል ከግዕዝ የተወሰደ ሲሆን ትርጓሜውም ቡድን ወይንም ኮሚቴ ማለት ነው። ይህን ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ ለስርዓቱ መገለጫነት የተጠቀመው ግለሰብ ሻለቃ ናደው ዘካሪያስ ሲባል ይሄውም ሰኔ 21፣ 1966 ዓ.ም. ነበር[1]። በዚህ ወቅት፣ በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኘው የአራተኛ እግረኛ ክፍለ ጦር መምሪያ ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተውጣጡ መለዮ ለባሾች በየካቲት ወር ስለፈነዳው አብዮት ከሰኔ 19 ጀምሮ ውይይት የሚያካሂዱበት ጊዜ የነበር ሲሆን፤ ሻለቃ ናደው የዚህ ኮሚቴ ማስታወቂያ ጉዳይ ሠራተኛ ነበር። ደርግ በዚህ ሁኔታ በዝቅተኛ መኮንኖች (ከኮሎኔል ማዕረግ በታች) ከተመሰረተ በኋላ በዚያው ቀን ሻለቃ መንግስቱ ኃይለማርያም የደርግ ሊቀመንበር በመሆን ተመርጦ እስከ ስርዓቱ ማብቂያ (1979) ድረስ በዚያ ስልጣን አገልግሏል።

የአብዮቱ ዋዜማ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የታኅሣሥ ግርግር ተብሎ በሚታወቀውና በ1953 ዓ.ም. የተካሄደው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ከከሸፈ በኋላ የቀዳማዊ ዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘውዳዊ መንግስት የተለያዩ ማሻሻያ ለውጦችን ለስርዓቱ አስተዋወቀ። አብዛኛዎቹ ማሻሻያዎች መፈንቅለ መንግስቱን እንዲደግፉ ለሚጠረጠሩ የጦርና የፖሊስ ሃይሎች የመሬት ስጦታ በማድረግ ላይ ያተኮረ ነበር። ስለሆነም የአገሪቱ መሰረታዊ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ሁኔታ በቋሚ ሁኔታ ሊሻሻል አልቻለም።

በ1958ዓ.ም. የባለ ርስቱን መደብ ጉልበት ለመቀነስ በማሰብ የዘውዱ ሥርዓት አዲስ አይነት የመሬት ግብር ለማስተዋወቅ ሞከረ። ሆኖም ፓርላማው ሙሉ በሙሉ ውድቅ አደረገው። በምትኩ፣ በሚቀጥለው ዓመት የእርሻ ውጤቶች ግብር ለፓርላማ ቀርቦ ጸደቀ። ምንም እንኳ የጸደቀው ግብር መንግስት ካቀረበው በጣም የተለወጠ ቢሆንም፣ በባለርስቱ መደብ አመጽ ማስነሳቱ አልቀረም። በተለይ በጎጃም ባለርስቶች በተነሳ አመጽ ምክንያት የሁለት አመት ወታደራዊ ዘመቻ በጎጃም ተደርጎ አመጹን ለማሸነፍ ስላልተቻለ መንግስት ወታደሩን ከጎጃም በማውጣት ግብሩን ሙሉ በሙሉ መሰርዝ ግድ አለው። እንዲያውም ወደኋላ፣ እስከ 1932ዓ.ም. የነበር የግብር እዳ በሙሉ ተሰረዘ። የጎጃሙ ሽንፈት ሌሎች ለውጥን የሚቃወሙ ክፍሎች እንዲያምጹ ከማበረታቱም በላይ ስርዓቱን ለሌላ አጣብቂኝ ዳረገው።

ለውጥን እሚቃወሙ ኃይሎች በሚያምጹበት በዚያው ወቅት፣ በተቃራኒው ለውጥን የሚፈልጉ ተማሪዎች፣ ገበሬዎችና፣ የሰራተኞች ማህበራት ባንጻሩ የኑሮ ውድነትን፣ ጉቦንና፣ የመሬት ሥርዓቱን በመቃዎም ማደም ጀመሩ። ይህ የተወሳሰበ ሁኔታ በእድሜ እየገፉ የሄዱት ንጉሱ ፊታቸውን ወደ ውጭ ጉዳይ እንዲያዞሩና የአገሪቱን የውስጥ ጉዳይ በጠቅላይ ሚንስትራቸው አክሊሉ ሃብተወልድ ጫንቃ ላይ እንዲያስቀምጡ አደረጋቸው።

ሥርዓቱ በሁለት ተጻራሪ አጣብቂኞች ውስጥ ገብቶ ባለበት በዚህ ወቅት በተፈጠረ የርሃብ፣ የኑሮ ውድነት፣ ሙስናና አጠቃላይ ቅሬታ የ1966ቱ አብዮት እንዲፈነዳ ግድ ሆነ። አብዮቱን ሀ ብሎ የጀመረው የወታደሩ መደብ ሲሆን፣ ጥር፣1966 ዓ.ም. ነገሌሲዳሞ ላይ ሰፍሮ የነበረው የምድር ጦር ሠራዊት አዛዥ መኮንኖቻቸውን ሲያግቱ ይጀምራል። ጉዳዩ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች በሚኖሩ የሰራዊቱ ክፍሎች ድጋፍን በማግኘቱ በወታደሩ መደብ ከመዛመቱም ባሻገር ወደ ተቀረው ዜጋም በመዝለል በመጋባቱ በብዙ ከተማዎች አመጽ መነሳት ጀመረ።

የዘውዱ መንግስት ለዚህ መልስ ይሆናል ብሎ ያስበውን ብዙ ጥቃቅን ለውጦችን አድርጓል፤ ለምሳሌ አክሊሉ ሃብተወልድን አንስቶ እንዳልካቸው መኮንንን ጠቅላይ ሚኒስትር አድርጓል፣ ለወታደሩ ልዩ ደመዎዝ ጭማሪ አድርጓል፣ ሊተገበር የነበር የትምህርት ስርዓት ማሻሻያ ለውጥን በተነሳበት ተቃውሞ ምክንያት አስቁሟል፣ የካቲት ወር ላይ እንዲሁ የመልስቱን ሕገ መንግስት ለማሻሻል ሞክሯል። ምንም እንኳ እኒህ ለውጦች ውጥረቱን ቢያረግቡም፣ በኋላ ላይ በኮሎኔል አለም ዘውድ የሚመራ የዘውዱ ተቆርቋሪ ቡድን የእንዳልካቸውን አስተዳደር ለመጥቀም በማሰብ ብዙ የአየር ኃይል መኮንኖችን ለእስር ዳረገ። በዚህ ሁኔታ የተበሳጨውና ተከፋፍሎ የነበረው የጦር ሠራዊቱ ክፍል፣ ኮ/ል አለም ዘውድ ከሚመራው ቡድን በማፈንገጥ በአንድ ልብ አመጽ ጀመረ። ሻለቃና ከሻለቃ በታች የሆኑት እነዚህ መኮንኖች በተለያዩ ስፍራዎች የሚገኙ የአገሪቱ ሰራዊት ሶስት ሶስት ተወካዮች ወደ አዲስ አበባ እንዲልኩ በማድረግ፣እርስ በርሳቸው በመሰባሰብ፣ ደርግን መሰረቱ።

የደርግ አመሰራረት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የአብዮቱ ዋዜማ መሪዎች፣ ሻለቃ መንግስቱ ኃይለ ማርያም፣ ብ/ር ጀኔራል ተፈሪ በንቲ፣ ሊ/ት ኮሎኔል አጥናፉ አባተ

ኮ/ል አለም ዘውድ የዘውዱ ተቆርቋሪ እንደሆነ ከታመነበት በኋላ በኮ/ል አጥናፉ አባተ የሚመራ፣ ባብዛኛው ከሆለታ ጦር ማሰልጠኛ የተመረቀ ቡድንና ጥቂት የሐረር መኮንኖች ማስለጠኛ ምሩቆች ሁነው አክራሪ አብዮተኛ ቡድን መስርተው ከአለም ዘውድ ቡድን ተገንጥለው ወጡ። ይህ ቡድን በኮሚቴ በመዋቀር በአገሪቱ ከሚገኙ 42 የጦር ክፍሎች ሦስት ሦስት ወኪሎች ወደ አዲስ አበባ እንዲመጡ ካደረገ በኋላ ከሰኔ '66 ጀምሮ መደበኛ ስብስባ በማድረግ ደርግ' እንዲቋቋም አደረገ። በአነጋገር ጥንካሬው፣ ውሳኔ ለመወሰን ባለምፍራቱና ባለማመንታቱ ታዋቂነት ያተረፈው መንግስቱ ኃይለማርያም ኢትዮጵያ ትቅደም የሚለውን መፈክር ካስተዋወቀ በኋላ በጣም ተቀባይነትን በማግኘቱ የዚሁ ኮሚቴ ሊቀመንበር ሆኖ ተመረጠ። ኢትዮጵያ ትቅደም የሚለውን መፈክር ባስተዋወቀበት ንግግሩ ኮሚቴው ኢትዮጵያን ከመበታተን አደጋ ለማዳን የቆመ ኃይል አድርጎ በማቅረብ ለተዘበራረቀው አብዮት አቅጣጫ ከመስጠቱም በተጨማሪ የአገሪቱን አንድነት ለማስጠበቅ የሚችል ሃይል ይሄው ኮሚቴ እንደሆነ በማሳየት ለኮሚቴው የሃገር ጠባቂነትን አላማ ለማሰጠት ችሎ ነበር።

መንግስቱ፣ ምንም እንኳ በወታደሩ ዘንድ ተቀባይነት ቢያገኝም፣ በመላው ሃገሪቱ ዘንድ ሙሉ ተቀባይነትን ማግኘት እንደማይችል ስለተረዳ ለዚህ ተግባር እንዲረዳው ጄኔራል አማን አንዶምን የስርዓቱ መሪ እንዲሆን በመጋበዝ የጊዜያዊው አስተዳደር ደርግ መሪ እንዲሆን አደረገ። ቀጥሎም ለዓፄ ኃይለሥላሴ 5 ጥያቄዎችን በማቅረብ ንጉሱ አምስቱንም ስለፈቀዱ የደርግ ሃይል በቅጽበት እንዲያድግ አደረገ።

በመቀጠል፣ በሃይል የጎለበተው ደርግ ጠቅላይ ሚንስትር እንዳልካቸው ከስልጣን እንዲነሱ አድርጎ ሚካኤል እምሩን ተካ። አማን አንዶም መከላከያ ሚንስትር ሆነው ከተሾሙ በኋላ እንዳልካቸውና የርሳቸው ደጋፊዎች እንዲታሰሩ ተደረገ። በዚህ መልኩ ቀስ ብሎ ይካሄድ የነበረው ለውጥ ፍጥነት ጨመረ። መንግስቱ፣ ንጉሱ እራሳቸውን በቀጥታ መጋፈጥ ስላልፈለገ ቀስ በቀስ የኃይላቻውን መዋቅር በማፈራረስ፣ የክብር ዘበኛን መሪ በማሳሰር፣ በኋላም የጆናታን ዲምብሊየወሎ ረሃብ ቪዲዮ በቴሌቪዥን በማቅረብ ንጉሱ ተጠያቂ መሆናቸውን በማሳየት፣ ሙሉው ስራ ከተሰራ በኋላ ያለምንም ችግር ንጉሱን ከስልጣን ማስወገድ ቻለ።

የጊዚያዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ንጉሱ ከስልጣን ከተነሱ በኋላ ጄኔራል አማን አንዶም የጊዚያዊ ወታደራዊ ደርግ ዋና ሊቀመንበር ሆኖ በመሾም፣ አዲሱ ስርዓት መስከረም፣ 1967 ተጀመረ። ደርግ በዚህ አኳሃን ስልጣን ላይ እንደወጣ አዲስ ረቆ የነብረውን ሕገ መንግሥት እና የነበረውን ፓርላማ ወዲያው ሰረዘ። የአማን ተግባር በተለይ ለአለም ፈገግ የሚል መልክ ማሳየትና እጅ መጨበጥ ነበርና ከሁለት ወር በኋላ መንግስቱ አስገድሎት ሌላ አሻንጉሊት መሪ ተፈሪ በንቲ በሥፍራው አስቆመ።


አመሠራረት እና ዕድገት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የመንግስቱ አመራር[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

መረሳ በ1982[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የ1977 ረሃብ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ዕርዳታና ውዝግቡ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የደርግ ማብቂያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የተመሰረተው በጥቂት ዝቅተኛ ወታደራዊ መኮንኖች ሲሆን ደርግ የአጼ ኃይለ ስላሴ መንግስትን ገርሦ በምትኩ ወታደራዊ ጁንታ በመመስረት ስሙን በመቀያየር አገዛዙ ለ17 ዓመታት ኢትዮጵያን አስተዳድሮአል። የተመሠረተበትም ቀን ሰኔ 20 1966 ነው

ደግሞ ይዩ፦

ማጣቀሻ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  1. ^ ኮ/ል መንግስቱ ኃይለማርያም፣ ትግላችን፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ የትግል ታሪክ፣ ፀሐይ አሳታሚና አከፋፋይ ድርጅት፣ ታህሳስ 2004 ዓ.ም. (ገጽ 152)