ደብረ ብርሃን

ከውክፔዲያ
ዘልለው ለመሔድ፦ የማውጫ ቁልፎች, ፍለጋ
ደብረ ብርሃን
ከፍታ ፪ሺ፰፻፵ ሜትር (፱ሺ፫፻፲፰ ጫማ)
አገር ኢትዮጵያ
ክፍለ ሐገር ሰሜን ሸዋ
የሕዝብ ቁጥር ፶፯ ሺህ ፯፻፹
ደብረ ብርሃን is located in ኢትዮጵያ
{{{alt}}}
ደብረ ብርሃን
ደብረ ብርሃን፣ ኢትዮጵያ

ኬክሮስና ኬንትሮስ
9°41′ ሰሜን ኬክሮስ እና 39°32′ ምሥራቅ ኬንትሮስ

ደብረ ብርሃንኢትዮጵያአማራ ክልል ከተማ ስትሆን በሰሜን ሸዋእና በደብረ ብርሃን ዙሪያ ወረዳ ውስጥ ትገኛለች። ከተማዋ የሰሜን ሸዋ ዞን (አውራጃ) አስተዳደር ርዕሰ ከተማ ከመሆኗ ባሻገር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስም ዋና ጽሕፈት ቤት እዚሁ ይገኛል።

፲፱፻፺፰ ዓ/ም ማዕከላዊ የስታትስቲክስ ባለስልጣን እንደተመነው ደብረ ብርሃን ከተማ የ፷፯ ሺህ ፪፻፵፫ ሰው መኖሪያ ስትሆን ከነሱም ፴፬ ሺህ ፶፭ ወንዶችና ፴፫ ሺህ ፻፹፰ ሴቶች ይገኙባታል ይላል።[1]

በሌላ ገለልተኛ የግምት ትመና ደግሞ ከተማዋ የ፶፯ ሺህ ፯፻፹ ሕዝብ መኖሪያ እንደሆነች ተገምቷል። የከተማዋ አቀማመጥ በ9°41′ ሰሜን ኬክሮስ እና 39°32′ ምሥራቅ ኬንትሮስ ላይ ነው።[2]

የሰሜን ሸዋ ዞን ዋና ከተማ የሆነችው ደብረ ብርሃንአዲስ አበባ ፻፴ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በደሴ መስመር ላይ የተመሠረተች ስትሆን ፱ የአስተዳደር ቀበሌዎች አሏት። የአየር ንብረቷ ቀዝቃዛ ነው፡፡ የተቆረቆረችውና ስያሜዋን ያገኘችው ደግሞ በ፲፬፻፵፮ ዓ/ም አካባቢ በዓፄ ዘርአ ያዕቆብ ነበር፡፡ ከተማዋ ድሮ የንጉሡ የግራ በአልቴሃት (ግራ በአልቴሃት ከንጉሡ ሦሥት ሚስቶች የአንደኛዋ የክብር ስም ነው) ርስት ነበረች፡፡ በ፲፬፻፵ዎቹ መጀመሪያ ንጉሡ ጐብኝተዋት ደስ ስለተሰኙባት ተጉለት የነበረውን መናገሻ ወደዚያ አዙረው የድንኳን ከተማቸውን ከተሙባት፡፡ በኋላም ቤተመንግሥት አሳንፀውና ባለወርቅ ጉልላት የነበረውን የሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አሰርተው ቆረቆሯት፡፡

"ተአምረ ማርያም" የተሰኘ የጥንት ድርሳን የከተማዋን ስያሜ ከአንድ ተአምራዊ ሁነት ጋር አያይዞ ይገልፀዋል፡፡ በ፲፬፻፵፮ ዓ/ም በክርስትና ሃይማኖት ካህናትና በጥቂት የሃይማኖቱ ተከራካሪዎች መካከል ክርክር ይነሳል፡፡ ንጉሡና የካህናቱ አለቆች በተገኙበት አንድ ዕለት በጉባዔ ክርክሩ ተካሄደ፡፡ በመጨረሻም "እስጢፋኖሳውያን" በሚል መጠሪያ የሚታወቁት ተከራካሪዎች አቋማቸውን እንዲያስተካክሉ ተጠይቀው አሻፈረን በማለታቸው ከፍተኛ ቅጣት ይደርስባቸዋል፡፡ ይህ በሆነ በ፴፰ኛው ቀን መጋቢት ፲ ቀን በ፲፬፻፵፮ ዓ/ም ረዘም ላለ ጊዜ / ምናልባትም ለቀናት/ የቆየ ቦግ ያለ ብርሃን ከሰማይ ይወርዳል፡፡ የብርሃኑ መውረድ ለእስጢፋኖሳውያን ስህተተኛነት ለካህናቱ ደግሞ ትክክለኛነት ምስክር ነው በሚል ተተርጉሟል፡፡ ስለዚህ ብርሃን መውረድ የንጉሡ ዜና መዋዕልም ያትታል። በዚህ ሳቢያ ንጉሡ የሥፍራውን ስም ደብረ ብርሃን /የብርሃን አምባ/ በማለት ሰይመውታል። [3]

ዓፄ ዘርአ ያዕቆብ ከንግሥና ዘመናቸው ፲፬ ዓመታት የሚሆነውን በደብረ ብርሃን ከተማ እንዳሳለፉና አብዛኛዎቹን የሃይማኖትና የፍልስፍና ድርሰቶቻቸውን የፃፉት በዚሁ ከተማ መሆኑ ይነገራል። በዘመኑም ደብረ ብርሃን ከፍተኛ የትምህርት ማዕከል የነበረች ሲሆን በንጉሡ ትእዛዝ በርካታ የሃይማኖት መፃሕፍት የትርጉም ሥራ ተከናውኖባታል።

ማጣቀሻዎች [ለማስተካከል]

  1. ^ ማዕከላዊ የስታትስቲክስ ባለስልጣን, population.pdf
  2. ^ Butler, Rhett A., 2005 population estimates for cities in Ethiopia
  3. ^ የአማራ ብሔራዊ ክልል፤ ባህል፣ ቱሪዝምና ማስታወቂያ ቢሮ፤ “የአማራ ክልል የቱሪስት መስህብ ሃብቶች (አጭር ቅኝት)”፤ አርቲስቲክ ማተሚያ ድርጅት (፲፱፻፺፩ ዓ/ም)፤ ገጽ ፯

ምንጭ [ለማስተካከል]

  • የአማራ ብሔራዊ ክልል፤ ባህል፣ ቱሪዝምና ማስታወቂያ ቢሮ፤ “የአማራ ክልል የቱሪስት መስህብ ሃብቶች (አጭር ቅኝት)”፤ አርቲስቲክ ማተሚያ ድርጅት (፲፱፻፺፩ ዓ/ም)