ዲዮኒሶስ

ከውክፔዲያ
ዲዮኒሶስ ጠጅ ሲያጠጣ

ዲዮኒሶስ (ግሪክ፦ Διόνυσος /ዲዮኑሶስ/) ወይም ባኩስ በጥንታዊ ግሪክ እና ሮማውያን አረመኔ ሃይማኖቶች ውስጥ የወይንና የስካር አምላክ ነበረ። የዚውስ ልጅ ይባላል። የእናቱ ስም በምንጮቹ ይለያያል፤ ወይም ሴት አምላክ ፐርሰፎኔ፣ ወይም መዋቲ ሴት ሴሜሌ ነበረች። ኒሳ በሚባል ደሴት ወይም ተራራ እንደ ታደገ ይታመን ነበር። በስሙ «ዲዮ-» የሚለው ክፍል ማለት «የዚውስ» እና «-ኒሶስ» ማለት «ከኒሳ» እንደሆነ ይመስላል።

በአንዱ ተውፊት ዘንድ ዚውስ ዲዮኒሶስን ከጸነሰ በሕዋላ የዚውስ ሚስት ሄራ በእናቱ ላይ እጅግ ቀናተኛ ሆነችና ልትገደለው አሰበች። ቲታኖቹን ልካ ሕጻኑን በሉት፣ ዳሩ ግን ዚውስ አጠፋቸውና ልጁን እንደገና በጭኑ ውስጥ አኖረው፤ ሁለተኛም ተወለደ። ስለዚህ ዲዮኒሶስ «ሁለት ጊዜ የተወለደው» ይባል ነበር። ዚውስ ልጁን ለሄርሜስ (ወይም ለሌሎች) ጥብቅና ሰጠውና በሥውር በኒሳ ታደገ። በዚያ የወይን ጠጅ አሠራር አገኘና የወይን ጥቅም በማስተማር ዓለሙን ዞረ። በፍርግያሕንድ፤ ግሪክ አገርና ጥራክያ ተጓዘ።

ጸሐፊው ዲዮዶሮስ ሲኩሉስሊቢያን ትውፊት ሲጠቅስ፣ ዲዮኒሶስ የዚውስ ሃሞን ልጅ ሲሆን የአባቱን ቂም በቅሎ ክሮኖስንና ሬያን ያሸንፋል፤ ከዚያ የክሮኖስን ልጅ ዚውስ ኦሊምፖስን የግብጽ ገዥ እንዲሆን ያደርገዋል።

አኒዮ ዳ ቪተርቦ ያሳተመው ዜና መዋዕል እንዳለው፣ ዲዮኒስዮስ የሊቢያ ንጉሥ ሃሞንና የቁባቱ አልማንጤያ ልጅ ነው፤ የሃሞንም ሚስት ሬያ ተቆጥታ ልጁ ወደ ኒሳ በሥውር እንዲታደግ ተላከ። በኋላ ወደ ሊቢያ ተመልሶ ሬያንና ወንድምዋን ካሜሴኑስን (የኖኅ ልጅ ካም) አባረራቸው። ልጃቸውን ዩፒተር ኦሲሪስ የግብጽ ገዥ አደረገው። ያንጊዜ ደግሞ ዲዮኒስዮስ አንዲት ሴት ልጅ ፓላስን በትሪቶኒስ ሀይቅ አገኝቶ ለራሱ ልጅ ትሆን ዘንድ አሳደጋት።