መናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን
| መረጃ | አካል |
|---|---|
| ስም | መናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን |
| ቦታ | ፒያሳ እየተባለ በሚጠራው ከዳግማዊ ምኒልክ አደባባይ ፊት ለፊት፣ ገዳም ሰፈር፤ ውቤ በረሀ፣ ጣልያን ሰፈር |
| ከተማ | አዲስ አበባ |
| ሀገር | ኢትዮጵያ |
| ዓይነት | ኦርቶዶክስ ተዋህዶ |
| አስተዳዳሪ | |
| የሕንፃ መነሻ ዓመት | |
| የሕንፃ መጨረሻ ዓመት | |
| የተከፈተበት ዓመት | 1886 ዓ.ም |
| የአርክቴክቸር ዓይነት | |
| የአርክቴክቸር ቅርንጫፍ | |
| ድህረ ገፅ | https://aradagiorgis.org/ |
መናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን Big text
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ስር በተለምዶ ፒያሳ እየተባለ በሚጠራው ከዳግማዊ ምኒልክ አደባባይ ፊት ለፊት፣ ገዳም ሰፈር፤ ውቤ በረሀ፣ ጣልያን ሰፈር በመባል በሚታወቁት አካባቢዎች የተከበበ ቤተክርስቲያን ሲሆን ደብሩ በስተመሀል ሰሜን አቅጣጫ የሚገኝ ነዉ። ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽፈት ቤት በ1.7 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል። መናገሻ የተባለዉ ንግሥት ዘውዲቱ እና ዐፄ ኃይለ ሥላሴ የንግሥ ዘውድ የደፉት በዚህ ቤተ ክርስቲያን ስለሆነና ለሥርዓተ ንግሡም ተጨማሪ ታሪካዊ ክብር ስላስገኘለት መናገሻ የሚለው ሥያሜም የተሰጠው በዚህ ምክንያት ነው ::
ገነተ ጽጌ ተብሎ የተሰየመው ደግሞ ጽጌ ማለት አበባ ልምላሜ ቆጽል ማለት ሲሆን ‹‹የአበባ ልምላሜ ደብር ለማለት ነው›› በገነት ቆጽል ልምላሜ አበባ አለና ቤተክርስቲያኑ ዕጅግ ዕድሜ ጠገብ በሆኑ በተለያዩ ዕጸዋት የተከበበ በመሆኑ ነዉ፤ የተተከለበትም ቦታ ‹‹አባ ያዕቆብ›› ወይም አባ” ሞንሲኞር ታውሪን” በተባለ ፈረንሳዊ ሚሲዮን የተያዘ ነበር፤ የገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በታነጸበት ቦታ ላይ በ400 ዓመት ገደማ ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶበት እንደነበረና ግራኝ አህመድ በተነሣበት ወቅት እንዳቃጠለው ኢሚል ፋውቸር የተባለ የውጭ ሀገር ታሪክ ጸሐፊ ገልጿል፤
አባ ያዕቆብ በጥንቱ የቤተክርስቲያን ፍራሽ ላይ ቤተክርስቲያን መስራት አለብኝ ብሎ ሲያስብ ነበር ንጉሥ ምኒልክም ቦታውን የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ለመስራት አሰቡ አባ ያዕቆብም ነገሩን ተቀብሎ በአትክልት የተሞላውን ግቢውንና ቤቱን ለቅቆ ሄደ። በዚሁ መሰረት እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1886 ዓ.ም የቅዱስ ጊዮርጊስ ጽላት በአንድ አነስተኛ ሕንፃ ውስጥ እንዲቀመጥ ተደረገ በዚያው ዓመት ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ (ምንይልክ) ባሰሩት ትልቅ የሣር ክዳን ሕንፃ ውስጥ ተቀመጠ። ሐምሌ 23 ቀን 1877 ዓ.ም ታቦተ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አባ ያዕቆብ ቤት /በመቃኞነት/ ገባ ዐፄ ምኒልክ ለታቦቱ የሚሆን ሌላ መቃኞ አሠሩ ሥራውም ከአድዋ ጦርነት በፊት ተጠናቆ መስከረም 23 ቀን 1888 ዓ.ም ታቦቱን ወደ አዲሱ መቃኞ አስገቡ። ታቦተ ቅዱስ ጊዮርጊስ በብዙ ጦርነቶች አብሮ ዘምቷል፤ በ1888 ዓ.ም ወደ አድዋ ዘምቷል በዚሁ ጦርነት ጊዜ የተማረኩ የፋሽሽት ኢጣልያ ወታደሮች “ቅዱስ ጊዮርጊስን በፈረስ ሆኖ ሲዋጋ አይተነዋል” ብለው ተናግረዋል ይባላል፤ በጥቅምት 1909 ዓ.ም ከራስ ተፈሪ ጋር ወደ ሰገሌ ዘምቷል በ1928 አመተ ምህረት ደግሞ ወደ ማይጨው ተጉዟል። ዐፄ ምንይልክ ወደ አድዋ ሲዘምቱ መጀመሪያ ወደዚህ ቤተክርስቲያን መጥተው ጸሎት አድርሰው በድል ቢመለሱ ዋናውን ሕንፃ ቤተክርስቲያን ሊያሠሩ ስዕለት ተስለው ነበር። ከአድዋ መልስ አንድ ዓመት ቆይታ በኋላ በየካቲት 23 ቀን 1899 ዓ.ም ዐፄ ምኒልክ መኳንንቱና ሕዝቡ በተሰበሰቡበት በአቡነ ማቴዎስ መሠረቱ ተጣለ፡፡ ሥራውን ለማፋጠን ዐፄ ምንይልክ የጢስ ባቡር ከአውሮፓ አስመጥተው ነበር። የደብሩ መገንቢያ ድንጋይ የተመላለሰው የሰርኪስ ባቡር በሚባለው ለኢትዮጵያ የመጀመሪያው በሆነው በዚህ መኪና ነው። ከዳግማዊ ምኒልክ ቤተመንግስት እስከ ቤተክርስቲያኑ የሚደርስ መንገድም ተሰርቶ ነበር። በመሀሉ ዐፄ ምኒልክ ቢታመሙም በተወካይ ሥራው ቀጠለ የቤተክርስቲያኑ አርክቴክት ‹‹አርፋኒዲስ›› የተባለ ግሪካዊ ሲሆን መሀንዲሱ ደግሞ ሙሴ ካስታኛ የተባለው ጣልያናዊ ነበር። የግንባታዉ ወጪ በአብዛኛው የተሸፈነው በመንግስት ነው። አፄ ምንይልክ 40,000 ብር አውጥተዋል ጉልላቱ /ዶሙ/ የተሰራበት ብረት ከፈረንሳይ በመጣ ብረት ነው ድንጋዩ ደግሞ ከተለያዩ ቦታዎች በአህያ እና በበቅሎ በሚጎተት ጋሪ ተጭኖ ቀርቧል:: የመጀመሪያውን ስዕል የሳሉት አለቃ ኀሩይ ናቸው። የአድዋ ድል በብሔራዊ ደረጃ መከበር የጀመረው እዚሁ ደብር ነበር፡፡ እንደ መርሥኤ ኃዘን ወልደ ቂርቆስ ከሆነ የቤተክርስቲያኑ ቅዳሴ ቤት የካቲት 23 ቀን 1904ዓ.ም ሲከበር ሕንፃው ተፈጽሞ ነበር:: ይሁን እንጂ የፍጻሜ ሥራው የቀረው ይመስላል በዓሉ የተከበረው በሚከተለው ሁኔታ ነበር። በመካኒሳ ሜዳ ድንኳን ተተክሎ በሚያዝያ 22 ቀን ታቦቱ ከመቃኞ ወርዶ አደረ ካህናተም እዚያው ማኅሌት ቆመው አደሩ። የበዓሉ ዕለት ልጅ ኢያሱ እና መኳንንቱ መጡ።ረፋዱ ላይ ነጋሪት በበቅሎ ተጭኖ እየተጎሰመ ጉዞ ወደ አራዳ ጊዮርጊስ ሆነ፤ዑደት ሆኖ አቡነ ማቴዎስ ካሳረጉ በኋላ 23 ጊዜ መድፍ ተተኮሰ። በ1894 ዓ.ም የአድዋ ድል ሰባተኛ ዓመት በዚህ ቤተ ክርስቲያን ሲከበር 60000 ሰዎች የተጋበዙ ሲሆን 8000 ከብት ታርዷል፡፡ ይሁን እንጂ በ1906 ዓመተ ምህረት ዐፄ ምኒልክ ሲያርፉ ግንባታው ገና አልተጠናቀቀም ነበር፤በ1909ዓ.ም ያስፈጸሙት ልጃቸው ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ናቸው። በዚሁ ደብር በ1909 ዓ.ም ንግሥተ ነገሥታት ዘዉዲቱ፣ በ1923 ዓ.ም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘውድ ጭነውበታል ፡፡ በአምስት ዓመቱ የጣልያን ወረራ ወቅት በአድዋ ጦርነት ቂም የያዘዉ ጣልያን ቤተ ክርስቲያኑን የሚያፈርስበትን ምክንያት ይፈልግ ነበር፡፡ በ1930 ዓ.ም የካቲት 12 ቀን በግራዝያኒ ላይ ቦንብ መወርወሩን ምክንያት አድርጎ የአርበኞች መደበቂያ ነዉ በማለት ቤተ ክርስቲያኑን ጋዝ አፍስሶ አቃጠለዉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ ከዉጫዊዉ ይልቅ ዉስጣዊዉ ክፍሉ ተጎድቷል፡፡ ግምጃ ቤቱ ሲቃጠል ብዙ መጻሕፍት እና ፋይሎች ተቃጠሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያኑ ሥዕሎችም ተቃጠሉ፡፡ ይህ አልበቃዉ ብሎ ጣልያን የመቅደሱን ግድግዳ ጥቁር ቀለም ቀብቶት ነበር፡፡ ቀለሙ ሙሉ በሙሉ የለቀቀዉ የዐፄ ኃይለ ሥላሴ 25ኛ የዘዉድ በዓል ሲከበር በተደረገዉ እድሳት ነዉ፡፡ ከፊሉ ካህናት ሲታረዱ ከፊሎቹ ታሥረዉ ወደሞቃዲሾ ተወሰዱ። ሌሎቹ ደግሞ ተሰደዱ፡፡ ታቦቱ ግን መምህር በየነ ወልደ ዮሐንስ በተባሉ ካህን አማካኝነት ራስ አበበ ወልደ አረጋይ ወደነበሩበት ሰሜን ሸዋ ጎሽ ባዶ ዐፄ ዋሻ ማርያም በድብቅ ስለወሰዱትአልተገኘም። የተመለሰዉ ከድል በኋላ ግንቦት 23 ቀን 1934 ዓ.ም ነዉ፡፡ አሁን ያለዉን ሥዕሎች የተሣሉት በአቶ እምአእላፍ ህሩይ፣ በተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌና በአለቃ መዝሙር ነዉ፡፡ መጋቢት 27 ቀን 1941ዓ.ም ከፍተኛ የክርስትናና እስልምና ሃይማኖት መሪዎች፣ መሳፍንት፣ ንጉሣውያን ቤተ ሰቦች፣ መኳንንትና ታላላቅ ሰዎች በዚሁ ቤተ ክርስቲያን ቅጽር ግቢ ውስጥ ተሰብስበው ስለዓለም ሰላምና ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር ስለምትቀላቀልበት ሁኔታ ውይይት፣ ንግግርና ጸሎት አድርገዋል። ደብሩ በ1963ዓ.ም ቤተ ክርስቲያኑ አራት መቶ ሥልሳ ሰባት (467) ጋሻ መሬት መተዳደሪያ መሬት ነበረው አብዛኛው በዐፄ ምኒልክ የተሰጠ ሲሆን ቀሪው በንግሥት ዘውዲቱና በቀዳማዊ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ የተሰጠ ነው ። ደብሩ በመምህር ይተዳደራል የማዕረግ ሥሙም ‹‹መልአከ-ገነት››፡፡ ወስብሀት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡