መንዳባ መድሃኒአለም
1. ማን እንደ አባ መድኃኒዓለም ገዳም
ገዳሙን (ቦታውን) የመሠረቱት አባት ጻድቁ አቡነ ያሳይ ይባላሉ፡፡ ትውልድ ሀገራቸውም በሸዋ ክፍለ ሀገር ተጉለት ነው፡፡ አባታቸውም የኢትዮጵያ ንጉሥ ቀዳማዊ ዓምደ ጽዮን ናቸው፡፡ ለአባታቸው ሦስተኛ ልጅ ናቸው፡፡ እናታቸው ግን የዐፄ ዓምደ ጽዮን ሚስቶች ሁለት ናቸውና የማንኛይቱ ልጅ እንደሆኑ አይታወቅም፡፡ እንደ ታሪከ ነገሥቱ ከሆነ የንጉሡ ሚስቶች ሁለት ነበሩ፡፡ አንደኛይቱ ታላቋ ዣን መንገሣ፣ ሁለተኛይቱ ብሌን ሳባ ይባላሉ፡፡ ንጉሡ ዓምደ ጽዮንም ከዕለታት አንድ ቀን ታመው ሳለ ጠላት በጦርነት ተነሳባቸው ያን ጊዜ በመኳንንቱ በመሳፍንቱ ፍርሃት ወደቀባቸው፡፡ የሕዝባቸውን መጨነቅ ያዩት ንጉሡ የሥጋ ደዌ አጥብቆ አሟቸው ሳለ ቁጭት ፀናባቸው ከሚስቶቼ ጋራ ከቤት ተኝቼ አልሞትም እየተዋጋሁ ከጦር ሜዳ ላይ እሞታለሁ ብለው በሽተኛው ሰውነታቸውን አበረታትተው ወደ ጦር ለመሄድ ሲነሡ ሁለቱ ሚስቶቻቸው እያለቀሱ ወደሰልፍ እንዳይሄዱ ለመኗቸው፡፡ ነገርግን ወደምክራቸው አልተመለሱም ከዚህ በኋላ ከታቦተ ማርያም ድንኳን ገብተው ድንግል ማርያም እንድታበረታቸውና በጦርነቱ እንድትረዳቸው አጥብቀው እያለቀሱ ለመኗት፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ ሰልፍ ሄዱና ጠላታቸውን አጥፍተው በዚያው ሌላ ሐገር እያቀኑ ቆዩ፡፡[1]
መዘግየታቸውን ያዩት ሚስቶቻቸው ዓምደ ጽዮን እኮ ሙቷል እያሉ አለቀሱ፡፡ ከሚስቶቻቸውም አንደኛይቱ ብሌን ሳባ የምትባለው ለትልቂቱ ለዣን መንገሣ ልጆቼን እንዴት ላድርጋቸው አለቻት እርሷም እመቤታችን ታውቃለችና ወደ እመቤታችን ድንኳን ወስደሽ አስገቢያቸው አለቻት፡፡ እሷም ወስዳ ከታቦተ ማርያም ፊት አኖረቻቸው፡፡ ያን ጊዜ እመቤታችን ባረከቻቸው ይላል፡፡ ከተባረኩት ልጆች አንደኛው አቡነ ያሳይ ሁለተኛው አቡነ መልከ ጼዴቅ ሳይሆኑ አይቀርም፡፡ በታሪከ ነገሥቱ እንደምንረዳው ከሆነ ታላቋ ዣን መንገሣ መካን ሁና ልጆቹ የብሌን ሳባ ይመስላሉ፡፡ ስለዚህ የአቡነ ያሳይ እናት ብሌን ሳባ ማለት ባያስደፍርም ሳትሆን አትቀርም፡፡ ከዚህ በኋላ ንጉሡ ዓምደ ጽዮን ጠላቶቹን አጥፍቶ ከዘመቻ ተመለሰ፡፡ ይህም ንጉሥ ከአፄ ይኩኖ አምላክ አንስቶ በሸዋ መንግሥት ስምተኛ ሁኖ ከ296 እስከ 1326 ዓ/ም ለ30 ዓመት የነገሠ ማለት ነው፡፡ ከዚህ በኋላ አባታችን አቡነ ያሳይን በጥበብና በፈሪሃ እግዚአብሔር አሳደጓቸው፡፡ አድገውም የቤተከርስቲያንን ትምህርት ብሉያትንና ሐዲሳትን እንዲሁም የቤተ መንግሥቱን ጥበብ ጠንቅቀው አወቁ፡፡ ከዚህ በኋላ የአልጋ ወራሽነት ማዕረግ ተቀበለው መንግሥት ይጠባበቁ ነበር፡፡[2]
ከዚህ በኋላ አቡነ ያሳይ ከእናት ከአባታቸው ቤት እያሉ ከንጉሡ ደጅ የሚፀኑ መነኮሳት ሁልጊዜ ወደ ቤተመንግሥቱ ይመጡ ነበር፡፡ እርሳቸው ግን መነኮሣቱን ተቀብለው እግራቸውን አጥበው የእግዚአብሔርን ሥራ የመለኮትን ነገር የምናኔን ሕይወት ይጠይቋቸው ነበር፡፡ እነርሱም የተቻላቸውን ያህል ያሥረዷቸው ነበር አባታችን አቡነ ያሳይም መጻሕፍትን የተማሩ ስለነበር መጽሐፍ ሲመለከቱ የመነኮሳትን ምክር እና ወንጌልን ቃል በማገናዘብ የእግዚአብሔር ፍቅር በልቦናቸው እንደ እሳት ነደደ፡፡[3]
ይልቁንም “ምንት ይብቁዖ ለሰብ እለእመ ኲሎ ዓለመ ረብሀ ወነፍሶ ሐጉለ" ሰው ዓለሙን ቢገዛ ቢያተርፍ በነፍሱ ከተጎዳ ምን ይጠቅመዋል፡፡ ማቴ 16-26" የሚለውን የፈጣሪን ቃል በማሰብ ያባታቸውን የአልጋ ወራሽነትንና የመንግሥትን ክብር ናቁት በመልክአ አቡነ ያሳይ መኑ ከማከእግዚኦ እንዘ ወልደ ንጉሥ ውእቱ ዘተናከሮ ለዓለም ዝንቱ" አቤቱ ማነው እንዳተ የንጉሥልጅ ሁኖ ይህን ዓለም የተለየው እንዲል፡፡ ዳግመኛም “እኔን መከተል የሚወድ ቢኖር እራሱን ይካድ መስቀሌን ተሸክሞ ይከተለኝ ማቴ6 24” የሚለውን መለኮታዊ ቃል በማሰብ በዚህ ዓለም ወጥመድ : ሳልገባ ብለው ወደሰልፍ እንደሚሄድ ወታደር በቆራጥነት የምነናን ጉዞ ጀመሩ፡፡ በእግዚአብሔር ስም እየዘመሩ” ፍኖተከ እግዚኦ አምረኒ ወአሠረ ዚአከ ምህረኒ አቤቱ መንገድህን አሳየኝ (አመላከተኝ የአንተን ፍለጋም አስተምረኝ መዝ24 4" ምህረትከ ይትልወኒ በኩሉ መዋዕለ ሕይወትየ” ይቅርታህና ምህረትህ እስከ ምኖርበት ዘመን ይከተለኝ መዝ 22-6” እያሉ ከቤተ መንግሥቱ ሸዋ ተነሥተው ወደ ትግራይ ክልል በአክሱም አካባቢ ከሚገኙት ገዳማት ደብረ በንኮል ከሚባለው ከአቡነ መድኃኒነ እግዚእ ገዳም ደረሱ፡፡ አቡነ መድኃኒነ እግዚእም ብዙ ፀጋ ያላቸው መሆናቸውን በመንፈስ ቅዱስ አውቀው ተቀብለው በረድእነት ከአኃው ቅዱሳን ጋር ጨምሯቸው፡፡[4]
ብዙ ጊዜም ካገለገሉ በኋላ አቡነ መድኃኒነ እግዚእ ሰባቱን ልጆቻቸውን በአንድ ቀን አመነኮሷቸው፡፡ ሲመነኩሱም መንፈስ ቅዱስ ፀጋቸውን ለመመስከር ስለወረደ ገዳሙ የተቃጠለ እስከ ሚመስል ድረስ በብርሃን ተዋጠ፡፡ በእያንዳንዳቸው ቆብም ቦግ ቦግ የሚል ብርሃን ታየ፡፡ ስለዚህ ከዚያን ቀን ጀምሮ እንደ ሮም ተስዓቱ (9) ቅዱሳን እንደተባሉት ሁሉ እነዚህም ሳባቱ ከዋክብት ተብለው ዝናቸው በሁሉ ተሰማ፡፡ “ከጻድቃንም ብዙዎች እንደ ከዋክብት ጥበበኞችም እንደ ሰማይ ፀዳል ለዘለዓለም ይበራሉ፡፡” ዳን 23፡3። እነዚህም አባታችን አቡነ ያሳይ በቆብ ትውልድ ከእንጦንስ አንስቶ ዘጠነኛ ናቸው፡፡[5]
አባ መድኃኒነ እግዚእ ያመነኮሷቸው 7ቱ ከዋክብት በመባል የሚታወቁት ቅዱሳንም እነዚህ ናቸው[6]
| ተ.ቁ | የቅዱሱ ስም | መካነ ገድል | የሚገኙበት ሀገር |
| 1 | አቡነ ያሳይ | ማን እንደ አባ | ደንቢያ |
| 2 | አቡነ ሳሙኤል | ዋልድባ | ጸለምት |
| 3 | አቡነ ሳሙኤል | ቆየጻ | ትግራይ |
| 4 | አቡነ ሳሙኤል | ጣሬጣ | ትግራይ |
| 5 | አቡነ አብሳዲ | ዞዝ አምባ | በለሳ |
| 6 | አቡነ ያፍቅረነ እግዚእ | ደብረ ጉጉቤን | ደራ |
| 7 | አቡነ ዮሐንስ | ግራናቔ | ትግራይ |
አሁን ያለነው መነኮሳት የምንኩስና ሐረጋችን ከመነኮሳት ሁሉ አባት ከአባ እንጦንስ ጀምሮ እንዲህ የሚታወቅ የተሰፈረ ነው።