Jump to content

ሶስና ሃይሌ

ከውክፔዲያ

ፕሮፌሰር ሶስና ሃይሌ (ግእዝ፡፣ በሐምሌ 21 1958 ዓ.ም ተወለደች) ኢትዮ-አሜሪካዊ ኬሚስት ስትሆን የመጀመሪያውን ጠንካራ አሲድ ነዳጅ ሴሎች በማበልጸግ ትታወቃለች።[1] በአሜሪካዋ ግዛት ኢሊኖይ ውስጥ በሚገኘው ሰሜን ምዕራብ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የቁሳቁስ ሳይንስ እና ምህንድስና ፕሮፌሰር ናት።[2]

በትውልድ ሀገሯ ኢትዮጵያ ውስጥ እምብዛም ባትታወቅም፤ በእርሷ የሕይወት ታሪክ ዙሪያ የተቃኘ ያልተወለደው ሌባ የሚል የአማርኛ የሣይንስ ልብወለድ መጽሐፍ መታተምን ተከትሎ ከፍተኛ እውቅናን አግኝታለች።

ሶስና የናሽናል ሳይንስ ፋውንዴሽን የብሔራዊ ወጣት ተመራማሪ ሽልማትን (National Young Investigator Award) (በ1986 ዓ.ም)፣ የሁምቦልድት ፌሎውሺፕን (Humboldt Fellowship) (ከ1984-1985 ዓ.ም)፣ ፉልብራይት ፌሎውሺፕን (Fulbright Fellowship) (ከ1983-1984 ዓ.ም)፣ እንዲሁም የአሜሪካን ቴሌፎን እና ቴሌግራም ካምፓኒ(AT&T) ትብብር ሪሰርች ፌሎውሺፕን AT&T Cooperative Research Fellowship (ከ1978-1984 ዓ.ም) ተቀብላለች። የሁምቦልድት ፌሎውሺፕ እና የፉልብራይት ፌሎውሺፖች ሶስና ከ1983ዓ.ም እስከ 1985 ዓ.ም በጀርመን ሀገር ማክስ ፕላንክ ኢንስቲትዩት ውስጥ ስታካሂድ የነበረውን ምርምሯን ደግፈዋል።

በ1993 ዓ.ም ሶስና በጄቢ ዋግነር ሥም የተሰየመውን የኤሌክትሮኬሚካላዊ ማህበረሰብ (Electrochemical Society) ከፍተኛ ሙቀት ቁሳቁሶች ክፍል ሽልማትን፣ በ1992 ዓ.ም በኤሜሪካዊው እውቅ ሣይንቲስት ሮበርት ኮብል(Robert L. Coble) ሥም የተሰየመውን የኮብል ሽልማት ከአሜሪካ ሴራሚክ ሶሳይቲ እንዲሁም በ1989ዓ.ም በሮበርት ላንሲንግ ሃርዲ(Robert Lansing Hardy) ሥም የተሰየመውን የማእድን፣ ብረታብረት እና ቁስ አካላት ማሕብረሰብ (TMS: The Minerals, Metals & Materials Society) ሽልማትን አግኝታለች።[3]

በ2002 ዓ.ም ሶስና በኢንዲያና ዩኒቨርሲቲ ውስጥ “በሳይንስ የላቁ ሴቶች” በሚል ርእስ ንግግር እንድታደርግ ተጋብዛ ነበር።[4] በ2010 ዓ.ም ሶስና የቁስአካለት ምርምር ማህበር አባል ሆና ተመርጣለች።[5] ሶስና በ2013 ዓ.ም የቁስአካላት ምርምር ማሕበረሰብ ግኝታቸውን ለሰፊው ማሕበረሰብ ላስተማሩና ላስረዱ ሣይንቲስቶች የሚሰጠውን የኤምአርኤስ ኮሙኒኬሽን ሌክቸር ሽልማትን (MRS Communications Lecture Award) አግኝታለች።[6]

የልጅነት ሕይወት

[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሶስና በ1958 ዓ.ም ሐምሌ 21 ቀን በአዲስ አበባ ኢትዮጵያ ውስጥ ተወለደች። በ1966ዓ.ም በአጼ ኃይለ ሥላሴ ላይ በተደረገው መፈንቅለ መንግስት ወቅት የመኳንንት ዘር የሆነው ቤተሰቧ ከኢትዮጵያ ተነስተው ወደ አሜሪካ ለመሰደድ በቅተዋል። አባቷ ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ የቋንቋ እና ታሪክ ተመራማሪ ሲሆኑ ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያ ኦርቶደክስ ቤተ-ክርስቲያን የተመለከቱ በግእዝና አማርኛ እነዲሁም በእንግሊዝኛ ከ18 በላይ መጻሕፍትን አሳትመዋል፡፡ ሶስና በ10 ዓመቷ ከኢትዮጵያ በመሰደድ ከእናቷ ጋር በሚኒሶታ ገጠራማ አካባቢ ኖራለች፤ ሶስና ትምህርቷን በሴንት ጆንስ መሰናዶ ትምህርት ቤት (ኮሌጅቪል ኤም ኤን) የተከታተለች ሲሆን በ1975ዓ.ም ተመርቃለች።[7]

ትምሕርት እና ሙያ

[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሶስና የመጀመሪያ ዲግሪዋን በተፈጥሮ ሣይንስ ከማሳቹሴትስ የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት (Massachusetts Institute of Technology) ተቀብላለች። በኋላም በርከለይ ከተማ በመሄድ ከካሊፎርኒያ ዩኒቨርስቲ የማስተርስ ዲግሪዋን ሠርታለች። ሶስና እንደገና ወደ ካምብሪጅ በመመለስ ከማሳቹሴትስ የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የዶክትሬት ዲግሪዋን ተቀብላለች፤ የፒኤችዲ ጥናቷም "Synthesis, crystal structure and ionic conductivity of some alkali rare earth silicate" የሚል ርዕስ ያለው ሲሆን በብርቅዬ ማእድናት ባህርይ ላይ ያተኮረ ጥናት ነው።[8]

ሶስና በሲያተትል ከተማ በሚገኘው ዋሽንግተን ዩኒቨርስቲ ውስጥ ለሶስት ዓመታት በረዳት ፕሮፌሰርነት አገልግላለች። በኋላም በ1988 ዓ.ም ወደ ካሊፎርኒያ የቴክኖሎጂ ኢኒስቲትዩት በመግባት ለ18 ዓመታት በምርምር ሥራ ውስጥ አገልግላለች። ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ በ2003ዓ.ም ባደረጉት የስቴት ኦፍ ዘዩኒየን ስብሰባ ሶስና በካሊፎርኒያ ቴክኖሎጂ ኢኒስቲትዩት ውስጥ የሠራችውን የምርምር ውጤት ለአሜሪካ ሕዝብ በይፋ ተናግረውላታል።

በ2007 ዓ.ም ወደ ኢሊኒዮስ ግዛዛ በማቅናት እስካሁን ድረስ በኖርዝዌሰተርን ዩኒቨርስቲ ውስጥ የቁስ አካላት ሣይንስና ኢንጂነሪንግ እንዲሁም የተግባራዊ ፊዚክስ ፕሮፌሰር በመሆን እያገለገለች ትገኛለች።[9]

ያልተወለደው ሌባ

[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ፕሮፌሰር ሶስና ያልተወለደው ሌባ በሚል ርዕስ ዶ/ር በኃይሉ ደመቀ በጻፉት የአማርኛ የሣይንስ እና የፍቅር ልብወለድ ውስጥ “ሕይወት” በሚል ገጸ-ባሕርይ በመወከል ዋና ገጸ-ባሕርይ ናት። ያልተወለደው ሌባ ታሪኩ አዲስ-ዓለም ከምትባል ኢትዮጵያ ውስጥ ካለች አነስተኛ መንደር ውስጥ የሚጀመር ሲሆን፤ ሚናስ ከተባለ አንድ ሚስጥርን እና እንቆቅልሽን ለመፍታት ከሚታትር ሰው ይጀምራል።

ሚናስ በሰፈሩ ውስጥ ቅርብ ጊዜ የተከሰተ አንድ ሽማግሌ ሰው ያስተውላል። ይህ ሰው ቀልቡን ይገዛውና ሰውየውን ይቀራረበዋል፤ በጊዜ ሂደት ሚናስ ሽማግሌውን ተግባብቶ ምስጢሩን ይነግረዋል። ይህ ሽማግሌ ስሙ ብሥራት የሚባል ሲሆን ሀብት ንብረቴን ባልተወለደ ልጅ ተዘረፍኩ የሚል ሰው ነው፤ ብሥራት ሊቀ-ኅሩያን የሚባሉ አያት ነበሩት፤ አያቱ የታወቁ የቤተ-ክህነት መመህር ሲሆኑ በድብቅ ደግሞ አስማተኛም ናቸው፤ ብሥራት በትምሕርቱ ደካማ ስለነበር አያቱ በአንድ ሌሊት ጎጃም ውስጥ ወዳለ የአባይ ወንዝ ገባር በሆነ ተፋሰስ ውስጥ ይወስዱትና ለደካማ የአብነት ተማሪዎች ትምህር እንዲገባቸው የሚደገምን የዘኢያገድፍ ድግምት ይደግሙለታል። ይህ አስማት ከተደረገለት በኋላ ብሥራት እሳት የላሰ ተማሪ ሆነ፤ በኋላ ላይ ብሥራት ወደ ደብረ ታቦር ከተማ በመሄድ የሁለተኛ ደረጃ ትምሕርቱን እየተከታተለ ሳለ ሕዳሴ ከምትባል ልጅ ጋር በፍቅር ይወድቃል። ሕዳሴም በብሥራት ፍቅር ትወድቅና ከእለታት በአንዱ ቀን የግብረ-ሥጋ ግኑኝነት ይፈጽማሉ። ከዚህ ቅጽበት በኋላ ብሥራት የአእምሮ ኃይሉ ቀስ በቀስ እየራቀው ይመጣና በትምሕርቱ ደካማ እየሆነ ይመጣል። ነገሩን ሲያጤን አያቱ ሊቀ-ኅሩያን ከእንስት ጋር እንዳይተኛ እንዳዘዙት ያስታውሳል፤ ይህም ብቻ ሳይሆን ብሥራት ሙሉ የአእምሮውን ኃይል ከፍቅረኛው በጸነሰው ልጅ ይዘረፋል።

ሚናስ ይህንን ታሪክ ከብሥራት ይሰማና ይገረማል፤ በኋላም በጅማ ዩኒቨርስቲ ውስጥ ትምህርቱን እየተከታተለ ሳለ በአሜሪካን ኢምባሲ በተዘጋጀ ውድድር ይሳተፍና ከተወዳዳሪዎች 4ተኛ በመውጣት ናሳን የመጎብኘተ እድልን ያገኛል። ኋላ ላይ ሚናስ ይህ እድል ወጥመድ ሆኖ ያገኘውና ያዝናል፤ የአሜሪካ መንግሥት ሆነ ብሎ በተለያዩ ድሀ ሀገራት እንዲህ ያለ ውድድር አዘጋኝቶ ወደ አሜሪካ ያመጣቸውና አዲስ የተሠራ የጊዜ ማሽን መሞከሪያ ሊያደርጋቸው ነው፤ የጊዜ ማሽኑ በከፍተኛ ፍጥነት የሚነጠቅ ሲሆን በጊዜ ወደፊት እና ወደኋላ መሄድ ያስችላል፤ ወደኋላ በመሄድ ድሮ የተደረጉ ክስተቶችን ሲያስቃኝ ወደፊት በመሄድ ደግሞ ወደፊት የሚደረጉ ነገሮችን ያሳያል። ይህ ማሽን እስካሁን ሰው ያልተጓዘበት ሲሆን የአሜሪካ መንግሥት ከድሀ ሀገራት ሰዎችን መልምሎ መሞከሪያ ሊያደርጋቸው ነው፤ በአጠቃላይ አሥር ሰዎች ከተለያየ ሀገራት ሲሰበሰቡ ሚናስ ኢትዮጵያን በመወከል ከአሥሩ አንዱ ነው፤ በጊዜ ማሽኑ የመጀመሪያ ሙከራ ጉዞ ላይ አሥር ሰዎች ሲሳተፉ፤ በጉዞው ላይ ዘጠኙ ሰዎች ሞተው ሚናስ ብቻውን ይተርፋል፤ ለዚህ ሚስጥሩ ደግሞ ከተመራማሪዎቹ አንዱ ከሁሉም የተለየ የጉዞ ጭንብል ስላጠለቀለት ነው፤ ሚናስ ይህ ሰው ለምን ለእሱ ብቻ እንዲህ እንዳደረገለት ግራ ገብቶት ሲጠይቀው፤ ወረቀት ጽፎ ይሰጠዋል፤ ሁሉም ተመራማሪዎች ጭንብል ስላደረጉ መልካቸው አይታይም፤ ወረቀቱ ላይ “ማታ ሆቴልህ ክፍል መጥቼ አናግርሀለው” ይላል፤ ሚናስ ሆቴሉ ክፍል ውስጥ ቁጭ በሎ ሲጠብቅ ይውልና እኩለ-ሌሊት ላይ ሆቴል የያዘበት ክፍል ይንኳኳል፤ ወጥቶ በሩን ሲከፍት ከፊት ለፊቱ አንዲት ኢትዮጵያዊት ሴት ያያል እርሷም ፕሮፌሰር ሶስና ኃይሌ ትባላለች፤ ሕይወቱን ስላተረፈችለት ሕይወት ብሎ ይጠራታል፤ በቆይታቸው ስለ ሕይወት ታሪኳ፣ ስለ ጊዜ ማሽን ኮንሰፕት እና ስለ አጠቃላይ የዓለም መጻኢ እድል ትነግረውና ይጽፋል፤

ሚናስ የጉብኝት ጊዜውን አጠናቆ ከአሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ ጉዞ ላይ ሳለ፤ ድሮ በሚያውቀው ሽማግሌው ብሥራትና እና በሕይወት መሀከል የሆነ ግኑኝነት እንዳለ የሚመስል አንድ ፍንጭ ያገኝና ለማጣራት ባለመሞከሩ እና ያኔ ሀሳቡ ስላልመጣለት ይናደዳል፤ አላስችል ይለውና እንደ እብድ አድርጎት ከዋሽንገተን ተነስቶ ወደ ኢትዮጵያ እየበረረ ያለውን አይሮፕላን መልሰህ ወደ ዋሽንገተን ተመለስ ብሎ ጉዞ ላይ ግርግር ሲፈጥር የእንቅልፍ መዳኒት ወግተው ጸጥ ያሰኙታል፤ ኋላ ላይ ይህንን እንቆቅልሽ ለመፍታት ይታትራል።

መጽሐፉ ባለ 380 ገጽ ሲሆን የታሪክ፣ ሳይንስ እና ፍቅር ይዘቶች አሉት፤ የታተመው በማይቢቲ ማተሚያ ቤት ሲሆን የመጽሐፉ ደራሲ በግልጽ አይታወቅም፤ የብእር ስሙ ዶ/ር በኃይሉ ደመቀ ሲሆን ምናልባት የሄኖክ ኃይሌ ሊሆን ይችላል የሚል ግምት አለ፤ የደራሲው የብዕር ሥም ከሄኖክ አባት እና ከሄኖክ ሚስት አባት የተወሰዱ ሁለት ሥሞች ድብልቅ ነው።