አባል:Ermias The Alene
ብፁዕ አቡነ ሄኖክ
ብፁዕ አቡነ ሄኖክ የምዕራብ አርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የተዋሕዶ ሚዲያ ማዕከል የበላይ ጠባቂና የቦርድ ሰብሳቢ
ጥቅምት 5 ቀን 1966 ዓ.ም በቀድሞ አጠራሩ ወለጋ ጠቅላይ ግዛት ጊምቢ ከተማ በደብረ ፀሐይ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን አካባቢ ከአባታቸው ከአቶ ቡልቶሳ ዱፌራና ከእናታቸው ከወ/ሮ በልዩ ተፈራ ተወለዱ።
ዕድሜያቸው ለትምህርት በደረሰ ጊዜ ፣ በቂልጡ ካራ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የአብነት ትምህርት ቤት በመግባት መሪጌታ አእምሮ ከሚባሉ መምህር፣ ንባብና ዳዊት ተምረዋል ፤ በደብረ ሊባኖስ ገዳም ከየኔታ ቀጸላ ከውዳሴ ማርያም ዜማ እስከ ምዕራፍ ተምረዋል ብፁዕነታቸው በ1975 ዓ.ም ከብፁዕ አቡነ ዜና ማርቆስ ማዕረገ ዲቁናን ተቀብለዋል፡፡
በተያያዘም ትምህርታቸውን ለመቀጠል ወደ ጎጃም ክፍለ ሀገር በመሄድ በሞጣ አካባቢ በመዘዋወር ከየኔታ ኪነጥበብ የቅኔ ትምህርትን ተምረዋል ፤ እንዲሁም በዚያው በሞጣ ከየኔታ አእመረ ቅዳሴ ተምረዋል ፥ በመቀጠል ወደ ርዕሰ አድባራት መርጦለማርያም ገዳም በመሄድ ከየኔታ ሀብቴ ለአምስት አመታት የቅኔ ትምህርታቸውን በመከታተል አጠናቅቀዋል ፤ እንዲሁም ከየኔታ ይሁን ዝማሬ መዋሥዕት በመማር አጠናቅቀዋል። በዚያው በመርጡለማርያም ገዳም ምንኵስናን ከመምህር አባ ኃ/ኢየሱስ በ1985 ዓ.ም ከተቀበሉ በኋላ ፣ 1990 ዓመተ ምህረት ከብፁዕ አቡነ ዘካርያስ የቅስና ማዕረግን ተቀብለዋል፤ በመርጡለማርያም ገዳም በነበሩበት ጊዜ፣ በጸሎተ ማኅበር፣ የልማት ሥራ በመሥራትና አቅመ ደካሞችን በመርዳት ገዳሙን አገልግለዋል፡፡
ከዚያ በመቀጠል በጎጃም ክፍለ ሀገር በተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር በቅዳሴና በማኅሌት ከማገልገል ጎን ለጎን በሞጣ ከየኔታ ኅሩይ አርባዕቱን ወንጌላት ተምረዋል፡፡
ዘመናዊ ትምህርታቸውንም በጊምቢ ከተማ አሶ ትምህርት ቤት እና አድቬንቲስት ትምህርት ቤቶች እና በጊምቢ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ትምህርታቸውን ተከታትለዋል ፤ ከ1994 ዓ.ም ጀምሮ በብፁዕ አቡነ ኤልያስ የወለጋ ሀገረ ስብከት መልካም ፈቃድ የነቀምቴ ገነተ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ዋና አስተዳዳሪ በመሆን እስከ 1997 ዓ.ም ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በቅንነትና በታማኝነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል።
ከ1994 ዓ.ም ጀምሮ በነቀምቴ መስከረም 2 ትምህርት ቤት በመግባት የመሰናዶ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁት ብፁዕነታቸው ከአዲስ አበባ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በአካውንቲንግ እና ፋይናንስ በዲፕሎማ ተመርቀዋል። የባችለር ዲያግሪያቸውን በንግድ አስተዳደር ከቅድስት ማርያም ዩኒቨርሲቲ ያገኙት ብፁዕ አቡነ ሄኖክ ጀርመን ሀገር ከሚገኘው ኢንተርናሽናል ቢዝነስ ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት በፕሮጀክት ማኔጅመንት ከፍተኛ ዲፕሎማ አግኝተዋል ፤ በአሁኑ ወቅት ብፁዕነታቸው በሀገረ ጀርመን ከሚገኘው አይ ቢ ኤም አይ በፕሮጀክት ማኔጅመንት የማስተርስ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ ይገኛሉ።
የቀድሞው አባ ገ/ኢየሱስ ቡልቶሣ ባላቸው በቂ የቤተ ክርስቲያን ዕውቀትና ባሳዩትም የመንፈሳዊ አገልግሎትና ሥራ ወዳድነት ፣ ቤተ ክርስቲያናችን ፣ ነሐሴ 22 ቀን 1997 ዓ.ም ባደረገችው የ17 አዳዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ፣ በካህናትና በምዕመናን በከፍተኛ ድምፅ ተመርጠው የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ኤጲስ ቆጶስ ኾነው ብፁዕ አቡነ ሄኖክ ተብለው ተሹመዋል፡፡
በዚህ ሀገረ ስብከት ፣ ምዕመናንን በማስተማርና የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን በማጠናከር ሀገረ ስብከቱ በሰው ልማትም ይሁን በራስ ኘገዝ ልማት ራሱን እንዲችል ለማድረግ በከፍተኛ ሁኔታ አገልግሎት ሲሰጡ ቆይተዋል። ብፁዕነታቸው ጥቅምት 1998 ዓ.ም ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት የኦሮምኛ ቅዳሴ ትርጉም እንዲዘጋጅና ለምዕመናኑ ተደራሽ እንዲሆን በማድረግ ረገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ከማድረግም በላይ በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን በቋንቋቸው እንዲማሩ እና የኦሮምኛ ቅዳሴ ትርጉም ተዘጋጅቶ ለአገልግሎት እንዲበቃ የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳሉ።
ብፁዕነታቸው ከ1998 ዓ.ም ጀምሮ ከምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት በተጨማሪ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ሀገረ ስብከትን በተደራቢነት እንዲመሩ በቅዱስ ሲኖዶስ የተመደቡ ሲሆን በክልል የሚገኙ ብሔረሰቦች በቋንቋቸው እንዲያገለግሉ ከማበረታታትም በላይ በርካቶች መሠረታዊ እና ከፍተኛ የቲዮሎጂ ትምህርት በመማር የአካባቢውን ሕብረተሰብ ማገልገል እንዲችሉ በማድረግ በከፍተኛ ሁኔታ የኖላዊነት ግዴታቸውን ሲወጡ ቆይተዋል። በ2001 ዓ.ም በምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ሥር የነበረው የቄለም ወለጋ ሀገረ ስብከት ራሱን ችሎ እንዲቋቋም በማድረግ የቄለም ወለጋ ምዕመናን መንፈሳዊ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አገልግሎቶች በቅርበት እንዲያገኙ ለማድረግ አስተዋፅኦ አድርገዋል።
ከ2008 ዓ.ም ወርኃ ግንቦት ጀምሮ የአውስትራሊያና የኒውዝላንድ አህጉረ ስብከትን እንዲመሩ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተመደቡት ብፁዕ አቡነ ሄኖክ በአህጉረ ስብከቱ የነበረውን ከፍተኛ አለመግባባት እና የአስተዳደር ችግር በማስተካከል ፣ ከአኃት አብያተ ክርስቲያናት ጋር ያለው ግንኙነት እንዲጠናከር በማድረግና በውጭ የተወለዱ ሕጻናት በምግባርና በሃይማኖት እንዲታነፁ ለማድረግ ከፍተኛ ሥራን ሲሰሩ ቆይተዋል።
ብፁዕ አቡነ ሄኖክ ሊቀ ጳጳስ ከጥቅምት ወር 2011 ዓ.ም ከምዕራብ ወለጋ ፣ ከአውስትራሊያና ኒውዝላንድ አህጉረ ስብከት በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ ወደ ምዕራብ አርሲ ሀገረ ስብከት በመዘዋወር ሀገረ ስብከቱ በአጭር ጊዜ ውጤታማ የሆነ የአመራር እና የመንፈሳዊ አገልግሎት ሂደትን እንዲከተል አስችለዋል። የተዋሕዶ ሚዲያ ማዕከልን በመመስረት ፣ በቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ የመጀመሪያ የሆነውን የሕዝብ ቆጠራ አፕሊኬሽን በማሰራት የምዕመናን ቆጠራን ማስደረጋቸው ፣ የሰው ኃይል አስተዳደር ሲስተም በሀገረ ስብከቱ እንዲተገበር ማድረጋቸው እና የሀገረ ስብከቱ አጠቃላይ እንቅስቃሴ ዕቅድ መር እንዲሆን ማስቻላቸው ፣ የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን በማጠናከር ኢአማንያን ወደ እውነተኛው የክርስቶስ በረት እንዲቀላቀሉ መደረጉ እና ሕገ ቤተ ክርስቲያንንና ቃለ ዓዋዲን በማስከበር ረገድ የተሰሩ ዐበይት ክንውኖች ብፁዕነታቸው በምዕራብ አርሲ ሀገረ ስብከት ከፈፀሟቸው ሐዋርያዊ የአገልግሎት ተግባራት መካከል ጥቂቶቹ ናቸው።