Jump to content

አባል:Ethiopoet

ከውክፔዲያ

Eye Health; Computer Use and the Eye; Danger Eye Disease signs; Vitamins and the Eye; What to do protect the Eyes; Cataract; Dry Eye; Macular Degeneration; red eye; proptosis; Ptosis; UV Radiation; Diabetes; Exercise

የዐይን ጤናን ለመጠበቅ የሚረዱ ዐብይ ተግባራት

ዓይናችን ካሉት አምስት የስሜት ህዋሳት አንዱ ሲሆን በምንኖርበት ወሰን የለሽና እጹብ ዓለም ዉስጥ ከሚገኙ ነገሮች በብርሃን ሞገድ አማካይነት መረጃ በመቀበልና ለአንጎላችን በማድረስ የማየት ጸጋን ያጎናጽፋል። ከሌሎች የስሜት ህዋሳት ጋር ሲነጻጸር 85 ከመቶ የሚሆነዉን መረጃ ለአንጎል በማድረስ ቀን በቀን ከአካባቢያችን ጋር ለምናደርገዉ የመኖር ትንቅንቅ ወይም መስተጋብር እጅግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርግ የረቀቀና የተወሳሰበ፣ ከፍተኛ ክብካቤ የሚሻ የብርሃን ስሜት ህዋስ ነዉ። እይታ ዉድ፣ ብርቅና ድንቅ የሆነ ለሰዉ ልጅ ጸዳል የሚያላብስ የተፈጥሮ ስጦታ ነዉ። በጥቅሉ ዕይታ ከሕይወት በመቀጠል ከሌሎች የስሜት ህዋሳት የበለጠ ታላቅ ቦታ የሚሰጠዉ የሰዉን ልጅ ከዓለም ጋር የሚያገናኝ ተፈጥሯዊ የመገናኛ ዘዴ ነዉ። ስለሆነም የሰዉ ልጅ ቅድመ ጥንቃቄ ሊያደርግለትና ከህመምና መሰል ጉዳቶች ሊጠብቀዉ የግድ ይላል።

የዓይን ጤና ችግሮች ሲከሰቱ ወቅታዊና ተገቢ ሕክምና ከማድረግ ባሻገር ችግሮች እንዳይከሰቱ ጥንቃቄ ማድረግና የዓይንን አጠቃላይ ጤና መጠበቅ የሚያስችሉ ተግባራትን ማከናዎን እጅግ አስፈላጊ ነዉ። ስለሆነም የዓይን ጤናን ለመጠበቅ የሚረዱ የክብካቤና የጥንቃቄ ድርጊቶችን እንደሚከተለዉ እገልፃለሁ::

ዋና ዋናዎቹም፡-

• ጤናማ የአመጋገብ ሥርዓት መከተል

• ለጤና ጠንቅ ከሆኑ ልምዶች ራስን መጠበቅ

• ዓይንን ከአደጋ መጠበቅ

• የቴክኖሎጅ ምርቶችን አጠቃቀም ማስተካከል

• መደበኛ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ እና

• መደበኛ የዓይን ምርመራ ማድረግ ናቸዉ።

ሀ.ጤናማ የአመጋገብ ሥርዓት መከተል

የተመጣጠነ ምግብ መመገብ ለአጠቃላይ ጤና ከሚኖረዉ ፋይዳ ባሻገር ለዓይን ጤናም አስተዋፅኦዉ ከፍተኛ ነዉ። የተመጣጠነ ምግብ ከሚሰጠዉ ቀጥተኛ ጥቅም በተጨማሪም ከተዛባ የአመጋገብ ሥርዓት ጋር ተያይዘዉ የሚመጡ የጤና ችግሮችን (ለምሳሌ አላስፈላጊ ዉፍረት፣ የስኳር ህመም፣ የደም ግፊት፣ ወዘተ) በመቀነስ ለዓይን ጤና አወንታዊ ሚና ይጫወታል። በተለይም በቪታሚንና በማዕድናት የበለጸጉ ምግቦችን መመገብ የዓይን ልባስ (conjunctiva)፣ የሌንስ (crystalline lens) እና የረቲናን (retina) ጤናና ሥራ የተሳለጠ ለማድረግ ከፍተኛ ሚና አላቸዉ።

ቪታሚንና ማዕድናት በተለይም ቫይታሚን ‹‹ኢ›› (Vitamin E) ፣ ቫይታሚን ‹‹ሲ››(Vitamin C) እና 'ዚንክ' (Zinc) በዓይን ላይ ጉዳት ሊያደርሱ የሚችሉ በደም ዉስጥ የሚገኙ ኬሚካሎችን ኃይል ለማዳከምና ከእድሜ መግፋት (እርጅና) ጋር ተያይዘዉ የሚመጡ የዓይን ጤና 6ችግሮችን (በተለይም የሰገነተ እይታ መጃጀት (Macular Degeneration) እና የዓይን ሞራ (Cataract)) በቶሎ እንዳይከሰቱ ለማድረግና የጉዳቱንም መጠን ለመቀነስ ይረዳሉ።

በቫይታሚን ‹‹ኤ›› (Vitamin A) የበለጸጉ ምግቦች (ጉበት፣ ካሮት፣ ስኳር ድንች፣ ጎመን፣ ቃሪያ፣ ሰላጣ፣ እንጆሪ፣ ማንጎ፣ ወዘተ) ጥራት ያለዉ እይታ እንዲኖር ከማድረግ ባሻገር የዓይን ልባስ ጤናን በመጠበቅና በቂ የዓይን እርጥበት (Eye Moisture) እንዲኖር በማድረግ የዓይን ድርቀትን (Dry Eye) ይከላከላሉ። ከዚህ በተጨማሪም የዓይን የደም ሥሮችን ቁጣ (inflammation of eye blood vessels) የሚቀንሱና የሰገነተ እይታን ጤናን የሚጠብቁ ምግቦችን (ለምሳሌ ዓሣ፣ የዓሣ ዘይት፣ ወዘተ) መመገብ ጠቀሜታዉ የጎላ ነዉ። በሳምንት አንድ ጊዜ ዓሣ መመገብ የሰገነተ እይታ መጃጀት ተጋላጭነትን (risk of macular degeneration) በከፍተኛ ደረጃ ሊቀንሰዉ እንደሚችል ጥናቶች ይጠቁማሉ።

ከፍተኛ የቫይታሚን ‹‹ኢ›› መጠን ካላቸዉ በሀገራችን ከሚዘወተሩና አስፈላጊ ከሆኑ ምግቦች ደግሞ ቆስጣ፣ የሱፍ ቆሎ፣ አቮካዶ፣ ዓሣ፣ የወይራ ዘይት፣ ስኳር ድንች፣ ጥቁር እንጆሪና ማንጎ ይገኙበታል። በተመሳሳይም ለሰዉነታችን የቀን ፍጆታ የሚያስፈልገዉን የዚንክ ማእድን ከእንስሳትና ከተክል ተዋፅኦ (ለምሳሌ እንጉዳይ፣የዱባ ፍሬ፣ የበግ ሥጋ፣ የዶሮ ሥጋ፣ የስንዴ ቆሎ፣ ቆስጣ፣ ለዉዝ፣ አተር፣ ወዘተ) ማግኘት ይቻላል።

ለ.ለጤና ጠንቅ ከሆኑ ልምዶች ራስን መጠበቅ

ሲጋራ ማጨስ ለአጠቃላይ ጤና ጠንቅ ከመሆኑም በላይ በሲጋራዉ ጭስ ዉሥጥ የሚገኙ መርዛማ ኬሚካሎች በዓይን ሌንስ፣ ሰገነተ ዕይታ (Macula)፣ ዕይታይ ነርቭ (Optic Nerve) እና የዓይን ደም ስሮች ላይ ጉዳት ስለሚያደርሱ ዕይታን ይጎዳሉ። ለሌላ የዓይን ጤና ችግርም (የዓይን ሞራ፣ የሰገነተ እይታ መጃጀት፣ ወዘተ) ያጋልጣል። ስለሆነም ሲጋራ ከማጨስ መቆጠብና የሚያጨሱ ከሆነም ለማቆም መሞከር ተገቢ ነዉ። ሲጋራ ማጨስ በሚያቆሙበት ጊዜም ለዓይን ጤና ችግር ያለዉ ተጋላጭነት እየቀነሰ ይሄዳል።

የእድሜ መግፋትም ሲጋራ በእይታ ላይ የሚያደርሰዉን ጉዳት እንዲጨምር ያደርጋል። በአጠቃላይ ሲታይ እድሜ እየገፋ ሲሄድ የሚያጨሱ ሰዎች ከማያጨሱት ሰዎች በሁለት እጥፍ በበለጠ ዕይታቸዉን የማጣት እድል አላቸዉ። በተመሳሳይ መንገድ የአልኮል መጠጥ አብዝቶ መዉሰድ ሌንስን፣ ሰገነተ እይታንና እይታይ ነርቭን ሊጎዳ የሚችል የኬሜካል ዉህድ ስለሚፈጥር የአልኮል መጠጥ መቀነስ ከተቻለም ማቆም ለዓይን ጤና ድርሻዉ የጎላ ነዉ።

ሐ.ዓይንን ከአደጋ መጠበቅ

ዓይንን ለአደጋ በሚያጋልጡ ማንኛዉም ዓይነት የሥራ ዘርፎችና ቦታዎች (ፋብሪካዎች፣ የእርሻ ልማት፣ የመኪና ጋራዥ ቤቶች፣ የግንባታ ቦታዎች፣ የብየዳ ሥራ፣ የድንጋይ ፈለጣ፣ የአትክልተኛነት ሥራ፣ ወዘተ)፣ መዝናኛዎችና ስፖርቶች ተገቢ የሆነ የአደጋ መከላከያ መነጽር ማድረግ ያስፈልጋል። ከዚህ በተጨማሪም ለብርሃን ጨረር መጋለጥ (በተለይም ለልእለ ሃምራዊ (አልትራቫዮሌት) ጨረር (ultraviolet light/rays)) በዓይን የተለያዩ ክፍሎች ላይ ጉዳት ስለሚያደርስና ለሌሎች ችግሮች (ሞራና የሰገነተ እይታ መጃጀት) ስለሚያጋልጥ ከልእለ ሃምራዊ ጨረር መከላከል የሚችል የፀሐይ መነጽር (UV Protection Sun Glasses) መጠቀም ተገቢ ነዉ።

ሁሉም የፀሐይ መነጽሮች እኩል የመከላከል ብቃት ስለሌላቸዉ የፀሐይ መነጽር ሲገዙ ከ99-100% የመከላከል አቅም ያላቸዉ መሆኑን ማረጋገጥ ያስፈልጋል። ለዕይታም ለፀሐይም የሚሆን መነጽር የሚጠቀሙ ከሆነ ደግሞ ከሌሎች በተሻለ ሁኔታ ቀለማትን መለየት ስለሚያስችል ግራጫ መልክ ያለዉን (በእንግሊዝኛዉ አጠራር ‹‹ፎቶ ግሬይ›› (photo gray glasses) የሚባለዉን) የፀሐይ መነጽር መጠቀም ጥሩ ነዉ። ከዚህ በተጨማሪም ፀሐያማ በሆኑ አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች የፀሐይ ባርኔጣ ቢጠቀሙ በፊት ቆዳ ላይ የሚደርሰዉን ጉዳት ከመከላከል ባለፈ በዓይን ላይ የሚያደርሰዉን የጨረር ጉዳት ይቀንሳል (ለዝርዝሩና ምስላዊ መግለጫ የዐይን ጤናና ክብካቤ መጽሐፍ ምዕራፍ 14 ገጽ 155-162 ያንብቡ)።

መ.የቴክኖሎጅ ምርቶችን አጠቃቀም ማስተካከል

የቴክኖሎጅ ምርቶችን (ኮምፒዩተር፣ ታብሌት፣ ተንቀሳቃሽ ስልክ/ሞባይል፣ መጫወቻ መሣሪያዎች፣ ወዘተ) የሚጠቀም ሰዉ ቁጥር ከመጨመሩም ባሻገር ሰዎች ከእነዚህ ዘመነኛ እቃዎች ጋር ከፍተኛ ቁርኝት በመፍጠር በቀን ብዙ ሰዓታትን እንደሚያሳልፉ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

ከአቀማመጥ ጋር በተያየዘም የተለያዩ የጡንቻና የመገጣጠሚያ ችግር (የአንገት ህመም፣ የጀርባ ህመም፣ የትክሻ ህመም፣ የእጅ እጣት ህመም፣ ወዘተ) የኮምፒዩተር ተጠቃሚዎች የእለት ከለት ችግር እየሆነ ነዉ። በሰለጠነዉ ዓለም የኮምፒዩተር ሱስ ራሱን የቻለ ሕክምና የሚያስፈልግዉ የጤናና የማኅበራዊ ችግር ከሆነም ዉሎ አድሯል። ለሰዉ ልጅና የቴክኖሎጂ ምርት ቁርኝት ዋነኛ የሆነዉ ዓይንም የጤና መታወክ ይገጥመዋል። ረዘም ላለ ጊዜ ኮምፒዩተር ላይ በሚያሳልፉበት ወቅት የቅንድብ መርገብገብ (Spontaneous Eye Blinking) ከመደበኛዉ ስለሚቀንስና በቂ የእንባ ስርጭት ስለማይኖር የዓይን ድርቀት ስሜት ይሰማል። ከዚህ በተጨማሪም ዓይናችን ለብዙ ጊዜ ተከፍቶ ሲቆይ የእንባ መጠን በትነት (evaporation) ምክንያት ስለሚቀንስ የድርቀት ስሜቱን ያባብሰዋል። የዕይታ ብዥታም (blurred vision) ሊኖር ይችላል። ከድርቀት በተጨማሪም ሌሎች የዓይነ ዝለት/ስትራፖ/ ምልክቶች (የዓይን ዙሪያ ህመም፣ የራስ ህመም፣ የዓይን መቅላት፣ የመቆጥቆጥ ስሜት፣ ወዘተ) ሊኖሩ ይችላሉ። እነዚህ ችግሮች በቀን ከሁለት ሰዓት በላይ ኮምፒዩተር ላይ በሚያሳልፉ ሰዎች ላይ ጎልተዉ የሚታዩ ሲሆን ሰዎች ኮምፒዩተር መጠቀም ሲያቆሙ ግን ይጠፋሉ።

በአጠቃላይ በኮምፒዩተር መጠቀም ምክንያት የሚከሰተዉ የዓይን ጤና መታወክ ችግር ጊዜያዊና ቋሚ ጉዳት የማያስከትል ነዉ። ብዙ ሰዓት ኮምፒዩተር ላይ ማሳለፍ የግድ ከሆነ ተገቢዉን ጥንቃቄዎች በማድረግ የሚፈጠሩ የዓይን ስሜቶችን መከላከልና መቀነስ ይቻላል (ለዝርዝሩና ምስላዊ መግለጫ የዐይን ጤናና ክብካቤ መጽሐፍ ምዕራፍ 18 ገጽ 195-199 ያንብቡ)።

1.የኮምፒዩተር አቀማመጥን ማስተካከል፤

2.የኮምፒዩተሩን ማሳያ/ሞኒተር/ የቀለም ስብጥርና ደማቅነት ማስተካከል፤

3.ነጸብራቅ የሚከላከሉ የሞኒተር ልባሶችን መጠቀም፤

4.ሞኒተሩን ከአቧራና ከጣት አሻራ የጸዳ ማድረግ፤

5.የፊደላትን መጠን ከፍ ማድረግና ሞኒተሩን ብዙ ነገር በመክፈት አለማጨናነቅ፤

6.በክፍል ዉስጥ በቂ ብርሃን እንዲኖር ማድረግ የዓይን ምቾት ይሰጣል፤

7.መቀመጫ ወንበርን ማስተካከል፤

8.በተደጋጋሚ የዓይን ቆብን በማርገብገብ የዓይን እርጥበትን መጠበቅ፤

9.ለዓይን በቂ ዕረፍት መስጠት፤

10.የዓይን እንቅስቃሴ ማድረግ፤

11. መደበኛ የኮምፒዩተር ተጠቃሚ ከሆ ቢያንስ በዓመት አንድ ጊዜ የዓይን ምርምራ ማድረግ።

ሠ.መደበኛ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ

ዓይናችን ጤናማ ሆኖ ለመቆየትና ሥራዉን በተገቢዉ ሁኔታ ለማከናወን ከፍተኛ የኦክስጅን መጠን ያስፈልገዋል። ስለሆነም በደም ዉስጥ የሚገኘዉን የኦክስጅን መጠን የሚጨምር የአካል ብቃት እንቅስቃሴ (በእንግሊዝኛዉ አጠራር ‹‹ኤሮቢክስ›› (aerobics) የሚባለዉ) ለዕይታ ነርቭ ህዋስ የሚያስፈልገዉን ኦክስጅን ከመጨመር ባለፈ የዓይን ግፊትን (intraocular pressure) ለመቀነስ ይረዳል። በተለይ ደግሞ የዓይን ግፊት ህመም (Glaucoma) እና ከመደበኛዉ በላይ የሆነ የዓይን ግፊት መጠን (high intraocular pressure) ላለባቸዉ ሰዎች ጥቅሙ የጎላ ነዉ።

ሌሎች የጤና ችግሮችን (ለምሳሌ የስኳር ህመምን) ለመቆጣጠር ስለሚረዳም እንደ ስኳር ያሉ ህመሞች የሚያደርሱትን ቀጥተኛ የዓይን ጉዳት ለመቀነስ ያግዛል። ስለሆነም በተቻለ መጠን ባለሙያን በማማከር የ30 ደቂቃ እንቅስቃሴ (ለምሳሌ ፈጠን ያለ ጉዞ (jogging)፣ ወዘተ) በሳምንት ለ5 ቀን ማድረግ ተገቢ ነዉ።

ረ.መደበኛ የዓይን ምርመራ ማድረግ

መደበኛ የዓይን ምርመራ ማድረግ የዓይን ጤናን ከመጠበቅ ባሻገር ዓይን መስኮተ ጤና በመሆኑ ስለ አጠቃላይ የጤና ሁኔታ በመጠቆም ወቅታዊና ተገቢ ሕክምና ለማድረግ ድርሻዉ የጎላ ነዉ። ይህንም ማድረጉ ችግሮችን በቶሎ ለማወቅና ለመታከም ይረዳል። ምልክት የማያሳዩ የዓይን ህመሞችን (ለምሳሌ፡-ዘገምተኛ የዓይን ግፊት ህመም) ከፍተኛ ጉዳት ሳያደርሱ ለማወቅ ስለሚረዳም ሁሉም ሰዉ ከህጻን እስከ አዋቂ መደበኛ የዓይን ምርመራ ሊያደርግ ይገባል።

የምርመራዉ አስፈላጊነትና ተደጋጋሚነት በእድሜ፣ በአጠቃላይ የጤና ሁኔታ፣ ለዓይን ጤና ችግር ተጋላጭነት፣ ወዘተ የሚለያይ ሲሆን ጠቅለል ባለ መልኩ በሚከተለዉ የጊዜ ሰሌዳ መሠረት የዓይን ምርመራ ማድረግ የላቀ ዉጤት እንደሚያስገኝ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

ሀ.ለልጆች፡- በተወለዱ በ6 ወር፣ 3 ዓመት ሲሞላቸዉ፣ 1ኛ ክፍል ከመግባታቸዉ በፊት እና ከዚያ በኋላ 18 ዓመት እስኪሞላቸዉ ድረስ በ2 ዓመት አንድ ጊዜ።

ለ.ለአዋቂዎች፡- ከ19-40 ዓመት የእድሜ ክልል ላሉ በሁለት ወይም በ3 ዓመት አንድ ጊዜ፤ ከ41-60 ዓመት የእድሜ ክልል ላሉ በ2 ዓመት አንድ ጊዜ፤ ከ61 ዓመት እድሜ በላይ ለሆኑ ደግሞ በዓመት አንድ ጊዜ።

ሰ.ሌሎች ለዓይን ጤና የሚጠቅሙ ጥንቃቄዎችን ማድረግ

• በቂ እንቅልፍ መተኛት፤

• የግልና የአካባቢ ንጽህናን መጠበቅ፤

• ቆሻሻ ወይም የተበከለ ነገር ነክቶ እጅን ሳይታጠቡ ዓይንን አለመንካት፤

• ህጻናት የጸረ-ስድስት ክትባት (በተለይም የኩፍኝ ክትባት) መዉሰዳቸዉን ማረጋገጥ፤

• አልፎ አልፎ አንድ ዓይንን ተራ በተራ በመጨፈንና የሁለቱን ዓይኖች እይታ በማነጻጸር መሠረታዊ የዕይታ ችግር እንደሌለ ለማወቅ መሞከር፤

• የዓይን መድኃኒቶችን (ጠብታ፣ ቅባት) በንጹህ ቦታ ማስቀመጥ፤ እንዲሁም ተከፍተዉ 3 ወር የሞላቸዉን አለመጠቀም፤

ህጻናትና ልጆች ስለ እይታቸዉ ችግር መናገር ስለማይችሉ ወላጆች የሚከተሉትን ምልክቶች ካዩ ሳይዘገዩ ወደ ህክምና ተቋም በመዉሰድ ማስመርመር ይገባል።

• በቀን ወይም በምሽት ለማየት መቸገር፤

• ትኩረት ለሚስቡ ነገሮች /መጫወቻዎች/፣ ወዘተ የዓይን ትኩረት አለመስጠት ወይም በእጃቸዉ ለመያዝ አለመሞከር፤

• ድምጽ ሲሰሙ ድምጹ ወዳለበት አቅጣጫ ለመዞር ወይም ለማየት አለመሞከር፤

• የዓይን መቅላት፣ ማሳከክ/ማሸት/፣ የዓይናር መያዝ፣ ብርሃን መፍራት፤

• የእንባ መፍሰስ (ያለማቋረጥ የሚያለቅሱ ይመስል እንባ

• የዓይን ብሌን ዉስጥ ነጭ ነገር ማየት (የድመት ዓይን መምሰል ወይም የሚያበራ ዓይን መምሰል)፤• የዓይን ፈጣን እንቅስቃሴ (ዓይነ ዥዋዥዌ (nystagmus))፤

• የዓይን መንሸዋረር /ዓይን ማጠናገር/፤

• የዓይን ቆብ መቅላት ወይም ማበጥ፤

• የዓይን ቆብ መዛል (Ptosis)፤

• የዓይን ወደ ዉጭ መዉጣት (መጎልጎል (proptosis))፤

• የዓይነ ኳስ መጠን መተለቅ (ማበጥ) ወይም ማነስ፤

• በዓይን ላይ ወይም በዓይን ዙሪያ እባጭ ነገር መከሰት፤

• መደበኛ ያልሆነ የጭንቅላት አቀማመጥ ሲኖር (አገጭ ከፍ /ዝቅ/ ማድረግ፣ ጭንቅላትን ወደ ቀኝ/ግራ/ማዘንበል፣ ፊትን ወደ ቀኝ/ግራ/ማዞር)

በአጠቃላይ ወላጆች ያልተለመደና ለየት ያለ ነገር ካዩ ለሀኪም ማሳየት አለባቸዉ። በዋናነት ከጥሩ እይታ ባሻገር የተለያዩ የዓይን ክፍሎች ተፈጥሯዊ ቀለማቸዉን፣ መጠናቸዉንና ቦታቸዉን ሊይዙ ይገባል።

(ምንጭ መጽሐፍ:- የዓይን ጤናና ክብካቤ በፕ/ር የሺጌታ ገላው:- ምዕራፍ 18 ገጽ 191-202 በደራሲዉ ፈቃድ በከፊል ተወስዶ የዓለም ዕይታ ቀንን (World Sight Day Oct 14 2021) ምክንያት በማድረግ የተለጠፈ)፡፡