ውክፔዲያ:ጸሐፌ ትዕዛዝ ገብረ ሥላሴ

ከውክፔዲያ
(ከአባል:Yaretselam የተዛወረ)

ሊቁ ንቡረ ዕድ ገብረ ሥላሴ ጸሐፌ ትዕዛዙ ለዳግማዊ ምኒልክ

በዳግማዊ ምኒልክ ዘመን፤ ከኢትዮጵያ መንግሥት የጽሕፈት ሚኒስተርነት መዓርግ ጋር የአዲስ ዓለም ደብረ ጽዮን ንቡረ ዕድነት ሹመት ተሰጥቶአቸው የነበሩት ጸሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ በ፩፰፻፩፯ ዓ.ም. ከአቶ ወልደ አረጋዊና ከወይዘሮ ወለተ ጊዮርጊስ በደብረ ብረሃን አካባቢ ተወለዱ። ዕድሜያቸው ሲፈቅድላቸውም በአንኮበር ከተማ አስቀድመው የንባብ፤ ቀጥሎ የዜማ፤ የቅኔና የትርጓሜ ሐዲሳት ትምህርታችውን ተራ በተራ ተማሩ።

በቅኔና በሥነ ጽሑፍ ሞያቸውም እጅግ የሚመሰገኑ ታላቅ ሊቅ ስለበሩ፡ ብላቴን ኀሩይ ወልደ ሥላሴ የኢትዮጵያ ሊቃውንትን ቅኔ አሰባስበው እንዲያሳትሙ ያነቃቁአቸውና ያበረታቱአቸው እንደነበር የታሪክ ዘገባዎች ያረጋግጣሉ። በዚሁም በታትመው የቅኔ መጽሐፍ ውስጥ በራሳቸው የተቀነባበሩት ልዩ ልዩ ቅኔዎች በከፍተኛ ሊቅነት መድረክ ላይ የቆሙ ለመሆናቸው ማረጋገጫዎች ናቸው። ጸሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ በቤተ ክህነትም ሆነ ቤተ መንግሥት የክበረ አገልግሎት ለማበርከት በነበራቸው ፈላጎት መሠረት፤ በመጀመሪያ የንጉሥ ምኒልክ ባለቤት ለነበሩት ለወይዘሮ ባፈና ልዩ ጸሕፊ በመሆን በቅንነትና መታማኝነት አገልግሎታቸውን ጀመሩ።

በኋላም አለቃ ወልደ መድኅን ይባሉ የነበሩት የዳግማዊ ምኒልክ ጸሐፌ ትእዛዝ ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ፡ በ፩፰፻፮፬ ዓ.ም. "ጸሐፌ ትእዛዝ" ተብለው ተሾሙና የቤተ ክርስቲያንን ሊቃውንት ወደ ቤተ መንግሥት ለማቅረብና ቁልፍ ቁልፍ ይሆኑትንም ከፍተኛ ቦታዎች ለማስያዝ የመሸጋገሪያ ደልድይ ምክንያት ሆኑ። ይኽውም በዚያን ጊዜ የኢትዮጵያ መንግሥት ሥራ አብዛኛውን የሚካሄደው በኢትዮጵያ ሊቃውንት ስለነበር ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የትምህርት ሚኒስቴር በመሆን በመላ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ትምህርት እንዲሰጥ በተጨማሪም የፍርድ ሚኒስቴርነቱንም ሥልጣን በሥራ በመተርጎም በከፍተኛ የነፍስ ግዳይ ወንጀል ላይ እንዃ ሳይቀር “ለሞት የሚያበቃ ወንጀል ነው ወይስ አያበቃውም” ብላ የመጨረሻውን ፍርድ እንዲጸድቅ በማድረግ ለኢትዮጵያ መንግሥት ታላቅ የሥራ ድርሻ በይበልጥ ለማበርከት የቻለችው በጸሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ የሥራ ዘመን እንደሆነ ይነገራል።

        ጸሐፌ ትእዛዝ የተማረና የተመራመረ፤ በአስተያየቱ የበሰለ ኢትዮጵያዊ ሊቅ ካጋጠማቸው ለዚያ ምሁር ቀለብ ወይም ተገቢውን ሹመት ሳይሰጡ በፍጹም እንቅልፍ አይወስዳቸውም ነበር የሚሉ ብዙዎች ናቸው፡ ይሁን እንጂ ለሹመት የሚያጩትን እያንዳንዱን የኢትዮጵያ ሊቅ በጠባይ ይዘቱ በኩል ምን ዓይነት አቋም እንዳለው የማጥናቱና የመከታተሉን ጉዳይ ቅድሚያ ይሰጡት እንደነበልም ይነገራል። ያኽውም ዛሬ ሾሞ ነገ መሻሩን እየተሳቀቁና እንደ ነዉርም እየቆጠሩት መሆኑ ይተረካል።

      ጸሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ በጸሐፌ ትዛዝነቱ መዓርግ ለሠላሳ ስድስት ዓመት ያህል በትጋት በቅንነትና በታማኝነት ሲሰሩ ከኖሩ በኋላ ያበረከቱት የአገልግሎት አስተዋጻኦ ተገምግሞ፤ በ፩፱፻ ዓመተ ምሕረት ለመጀመሪያ ጊዜ በዳግማዊ ምኒልክ ዘመን የሚኒስትርነት ሹመት ሲጀመር በዚያው አስቀድሞ ይዘውት የነበረው ሥራቸው ላይ የኢትዮጵያ መንግሥት የጽሕፈት ሚኒስቴር ሚኒስትር በመባል ከፍተኛ መዓረግ አገኙ። በዚህም ወቅት በተጨማሪ የእንጦጦ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤልን እንዲያስተዳድሩ ተሾመዋል። 
     ከዚህም ቀደም ብሎ በ፩፰፻፱፬ ዓ.ም ዳግማዊ ምኒልክ የአዲስ ዓለም ዳግማዊት ጽዮንን ቤተ ክርስቲያን በሚገባ አሳንፀው ሥርዓቷንም ሆን መዓርጓን እንደ አክሱም ተመሳሳይ የሆነ የንቡረ ዕድነቱን ሹመት ለማን እንደሚሰጡት አሳስቦአቸው ነበርና፤ መኳንንቱን ሊቃውንቱ ለዚህ ሹመት ተገቢ የሆነውን ሰው በስብሰባ መርጠው እንዲያቀቡላቸው ትእዛዝ ሰጡ። ለሚመረጠው ሰው ባለሟልነትን ከሊቅነት ጋር አጣምሮ የያዘ መሆን እንደሚገባው መመሪያ ሰጡ፤ ይህም ያስፈለገበት ምክንያት፤ “በባለሟልነቱ ይህ ቀረ ያ ጎደለ እንዲህ እንዲህ ያለው ያስፈልጋል ብሎ ደፍሮ እንዲያስታውሰኝ፤ በትምህርቱ ካህናቱንም ሆነ ምእመናኑን በእውቀት በምርምር እንዲያንፅ፤ መናፍቃንን እንዲገስጽ ነው” አሉ። ይኽንኑ መመሪያ የተቀበሉት መኳንንትና ሊቃውንትም የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤልን፤ አሁን መንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ የተባለውን የቀድሞውን መካነ ሥላሴን አድባራት፤ በየተራ የተሾሙትን ታላቁን ሊቅ አለቃ ወልደ ማሪያምን በተባበረ ድምፅ መርጠው አሳባቸውን አቀረቡ። 

        ዳግማዊ ምኒልክ በባለሙዋልነትም ሆነ በትምህርት የተሟላ ይዘት ያላቸው አለቃ ወልደ ማርያምን ለአዲሱ ዓለም ደብር ተሿሚ የራስ ወርቅ፤ የወርቅ ጫማ፤ የወርቅ ላንቃ ካባ፤ የወርቅ መቋሚያ፤ የወርቅ ጸናጽልና የወርቅ ወንበር በአስቸኳይ ተዘጋጅቶ ንቡረ ዕድነቱ አንዲሰጣቸው አዘዙ። በዚህም ወቅት ዳግማዊ ምኒልክ አንድ ነገር ትዝ አላቸው፤ ይኸውም የቤተ ክህነቱን ሥርዓት በሚገባ ጠንቅቀው የሚያውቁትና በሀሳብ አቅራቢነት ችሎታቸውም ተደማጭነት የነበራቸው የአፈ ንጉሥ እስጢፋኖስ በጉባኤው አለመገኘት ነበር። በመሆኑም አፈ ንጉሡን ወዲያውኑ አስጠርተው የጥናቱንና የውሳኔውን ሁኔታ ቢያስረዱአቸው፤ የሊቁን ተፈላጊነት እንደሚያምኑበትና የቀረበውንም የውሳኔ ሀሳብ እንድሚስማሙበት አረጋገጡ።

        “ብቻ” እሱ አፈ ንጉሥ እስጢፋኖስ “ንቡረ ዕዱ በታላላቅ በዓላት የወርቅ ጫማ መጫማት አለበት፤ ስለዚህ የሊቁ አንድ እግራቸው በሽተኛ ነውና፤ የወርቅ ጫማ ለማድረግ ያስቸግር የመስለለኛል” አሉ። በዚህም ወቅት በአዲስ ዓለም ዳግማዊት ጽዮን ደብር ምንም ዓይነት ነቀፌታን ያስከተለ ነጥብ እንዲገኝ የማይፈልጉት ዳግማዊ ምኒልክ ከቀሩት መማከርት ያመለጠው ሀሳብ ከአፈ ንጉሥ በመገኘቱ እጅግ አድርገው አደነቁና የአለቃ ወልደ ማርያምን ሹመት በዚሁ ብቻ ውድቅ አድርገው “የተደከመበትን ሀሳብና ጥናት ማፍረስ ብቻ ሳይሆን እንደገና ሌላ አዲስ ሕንፃ ማነፅ ያስፈልግሃልና አንተ በበኩልህ ማን ቢሆን ይሻላል ትላለህ ብለው አፈ ንጉሡን ቢጠይቁአቸው፤ እንደ እኔማ ቢሆን በአንድ በኩል ደግሞ በቅርብ የሚያውቁትና ጠባዮን የመረመሩት ጸሐፊ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ ስለሆነ በዚሁ በያዘው ሹመት ላይ ንብረ ዕድነቱ ቢፈቀድለት ደስ ይለኛል” ሲሉ ሀሳብ አቀረቡ።

        በዚህ ሀሳብ ላይ ምንም ዓይነት ተቃውሞ ለመሰንዘር ያልፈለጉ ዳግማዊ ምኒልክ፤ ጸሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ የክብር ልብሱን ለብሰው፤ የወርቁን ጫማ ተጫምተውንና የራስ ወርቁን ደፍተው እንዲቀርቡ፤ መዃንንቱና ሊቃውንቱም እንዲሰበሰቡ ውዲያው አዘዙ። ጸሐፌ  ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ እንደሚሾሙ ተነግሯቸው፡ የክብር ልብስ ለብሰው እጅ ለመንሣት ሲቀርቡ ዳግማዊ ምኒልክ “ገብረሥላሴ!! የመረጡህ ታማኝነትህና አገልግሎትህ ተባብረው ነው፤ እኔ አሰተናባሪና አዳይ እንጂ፤ ሰጪው እግዚአብሔር ነው” ስለ አሉዋቸው በዚህ አነጋገር ልባቸው የተነካ ጸሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ እያለቀሱ “ከትቢያ ላይ አንስተው ሰው ቢያደርጉኝ፤ ሰው ሆንኩ እንጂ ለርስዎ ስጦታ የኔ ታማኝነትና አገልግሎት ምን ይመጥነዋል” በማለት ዕንባቸው አልታገድ አለ።

        በዚህ ወቅት ፈሊጠኛው አፈ ንጉሥ እስጢፋኖስ “ሲሾሙህ ያለቀስክ ቢሽሩህ ምን ልትል ነው” ? ብለው ሁኑንም ስለ አሳቁት የጸሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ ኃዘን በቀልድ ተለውጦ፤ በቤት መንግሥቱ እንዲሁም በተሿሚው መኖሪያ ቤት ደስታ ሆነ። የዳግማዊ ምኒልክ ጸሐፌ ትእዛዝ፤ ንቡረዕድ ገብረ ሥላሴም ከጥቂት ቀናት በኋላ በብዙዎች ሊቃውንትን መዃንንት ታጅበው በዘመኑ የትራንስፖርት አገልግሎት ይሰጥ በነበረው ሠረገላ ከባለቤታቸው ጋር ሆነው በአዲስ ዓለም ዳገማዊት ደብረ ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ሲደርሱ፤ ጥንግ ድርብ፡ ባለ ወርቅ ካባና ቀሚስ ለብሰው የብር መቋሚያና ጽናጽል ይዘው የሚጠባበቁት ካህናት በይባቤ ተቀበሉዋቸው።

     የባለቤታቸውም ስም “ወይዘሮ ዕሤተ” ስለነበር ሊቃውንቱ ይኽንኑ ሁኔታ በማስመልከትና ምሥጢሩን ከምሥጢር በማስተባበር “ዘዕሤቱ ምሰሌሁ ወምግባሩ ቅድመ ገጹ ገብረ ሥላሴ ጸሐፌ ትእዛዙ ለዳግማዊ ምኒልክ ንጉሠ ጸዮን ጻድቅ ወየዋህ ምኒልክ” የሚል ግሥ ገሥሠው እንደወረቡና በዚሁም በጣም እንደተመሰገኑበት ይነገራል። በዚህም ወቅት አዲስ ዓለም እንደ ስሟ በእውነቱ አዲስ ዓለም ሆነች፤ የመጀመሪያው ንቡረ ዕድ ገብረ ሥላሴ ፤ የብሉያት፤ የሐዲሳት፤ የሊቃውነት ትርጓሜ፤ የዜማና የቅኔ መምህራን ሊቃውንትን፤ እጥፍ እየሆኑ በአዲስ ዓለም ደብረ ጽዮን ጉባዔ ዘርግተው እንዲያስተምሩ አደረጉ። በዚህ ጊዜ ነበር ታዋቂ የሐዲስ የነበሩት ሊቁ ወልደ ሚካኤል በአዲስ ዓለም ደብረ ጽዮን ጉባዔ ዘርግተው ትርጓሜ ሐዲሳትን ሲያስተምሩ የነበረው።
   የብሉዩና የቅኔው መምህር ስመ ጥሩው አለቃ ተጠምቆም በዚሁ ደብር ጉባዔ ዘርግተው ያስተምሩ ነበር። ጸሐፌ ትእዛዝ በትምህርትና በመልካም ጠባይ የተማመኑባቸውን ሊቃውንት በተከታታይ በአዲስ ዓለም፤ በእንጦጦ ራጉኤል፤ በሌሎቹም ታላላቅ አድባአት ሁሉ በመመደባቸው ይልቁንም በጎንደር፤ በጎንደር፤ በጎጃም፤ በሸዋ የሚገኙትን ሊቃውንት ደጅ ሳይጠኑ ራሳቸው ካሉበት እያስፈለጉ በገዳማትንና በአድባራት እንዲሾሙና የተወሰነ መተዳደሪያ እየተሰጣቸው እንዲያስተምሩ በማድረጋቸው ከፍ ያለውን መንፈሳዊ ዝና ለማትረፍ ቻሉ።
   በአዲስ ዓለም የግል ቤታቸውን ከቤተ ልሔም ላስምጧቸው፤ ለመዝገብ ድጓው መምህር ለሊቀ ቴዎድሮስ ሰጡ፤ የመኖሪያ ቤታቸው ማዕድ በሊቃውንት ብቻ የተከበበ በመሆኑ፤ ምግብ ተጀምሮ ከፍ እስኪል ድረስ ከሊቃውንቱ ጋር ስለ ትርጓሜ መጻሕፍት ምሥጢር ከመነጋገርና ሀሳብ ለሀሳብ ከመለዋወጥ በቀር ሌላ ዓለማዊ ነገር አይነገርም ነበር እየተባለ ይተረካል። ንቡረዕድ ገብረ ሥላሴ ሠርቶ በማሰራት፤ የሥራን ክቡርነትም አውቆ በማሳወቅ፤ በጣም የተመሰገኑ እንደ ነበሩ ታሪክ ያረጋግጣል።
  ለምሳሌ አንድ የግል ጸሐፊያቸው ሆኖ በቤታቸው የሚኖር ሠራተኛ ለሥራ እየፈለጉት ሊያገኙት ስለ አልቻሉ ከመገሠጽም ሆነ በገንዘብ ከመቅጣት የተሻለ መስሎ የታያቸውን ልዩ ዘዴ መረጡ፤ የኸውም ቀጥሎ የትመለከተው ነው፤ አንድ ባዶ የሆነ ኤንቬሎፕ አሽገው ጧት ከቤታቸው ወደ ቤተ መንግሥት በበቅሎ ሲሔዱ የኸንን ከዚያው ከግቢ ስደርስ ትሰጠኛለህና የዘህ ተከተለኝ ብለውት ከቤተ መንግሥት ደርሰው ከበቅሎ ሲወርዱ ቢሰጣቸው ወደ ቤት ስንመለስ ትሰጠኛለህ አሉት።
  በዚህም ዓይነት ከቤት ሊሰጣቸው ከቤተ መንግሥት፤ ከቤት መንግሥት ሲሰጣቸው ከቤት እያሉ ለአሥራ አምስት ቀናት ያህል እንዳይለያቸው አደረጉ፤ ከዚያ በኋላ ግን እየወተወተ ስለ አስቸገራቸው ለልዩ ጸሐፊያቸው እንዲሰጥ አዘዙት። ልዩ ጽሐፊውም ተቀብሎ ቢከፍተው ባዶ ኤንቬኖፕ ሆኖ ስለ አገኘው "የሰጡህም ጽሑፍ ከሥራህ ላይ እየታጣህ ስለ አስቸገርክ በዘዴ ትምህርት ሊሰጡህ ነውና ለወደፊቱ ተጠንቀቅ" ብሎ መክረው። ጸሐፊውም ሁኔታውን ስለ ተረዳው የሥራን ክቡርነት ዐውቆ ጠባዩን ሊያሻሻል እንደቻለ ይነገራል።
  ጸሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ "የታሪክ ዘመን ዘዳግማዊ ምኒልክ" ተብሎ በ፩፱፻፭፱ ዓ.ም የታተመውን መጽሐፍ ቀደም ብለው ረቂቁን አዘጋጅተው፤ በአንዳንድ ገዳማትና አድባራት እንዲቀመጥ አድርገው እንደ ነበር የኸው መጽሐፍ ያስረዳል። 
  ስለዚህ የዳግማዊ ምኒልክ ጸሐፌ ትእዛዝ የነበሩት፤ ንቡረ ዕድ ገብረ ሥላሴ ከዚህ በላይ በተዘረዘረው የሥራ ፍሬአቸው፤ ለኢትዮጵያ ቤተ መንግሥትና ቤተ ክህነት ባለውለታ ናቸው ለማለት ይቻላል። 
   ይኸንንና ይኸንን በመሳሰለው ሁኔታ ሕይወታቸውን በታሪክና በሥራ ሲያስጌጡ ከኖሩ በኋላ ጥቅምት ፪፯ ቀን ፩፱፻፭ ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተው ባቀኑት፤ ባፀኑትና ባስተዳደሩት በእንጦጦ ራጉኤል ደብር የቀብራቸው ሥነ ሥርዓት ተፈጽሟል።