አባል ውይይት:Ethiopoet
ርዕስ ጨምርየመሪ ተከታይ ዓይነቶች (በፕ/ር የሺጌታ ገላው)
==========================
[ኮድ አርም]በአመራር ዘርፍ ከፍተኛ ትኩረት ከሚሰጣቸው ዓብይ ጉዳዮች አንዱ የመሪና የተከታዮች መስተጋብር ነዉ:: ይህ እዉነታ በዓለማዊም ሆነ በመንፈሳዊ ተቋማት ዉስጥ ተልዕኮን ከማሳካት አንፃር እጅግ ወሳኝ ነዉ:: የስኬት ሚዛኑም በመሪዎችና በተከታዮች መካከል በሚኖረው የስበት ኃይል ይወሰናል::
የመሪዎች ሚና በሥራ አመራር ዘርፍ ትኩረት የሚሰጠውና ለዘመናት ሲሰጠው የቆየ የስኬት ቁልፍ ምሥጢር ቢሆንም ጠንካራ ተከታዮችም የመሪዎችን ብቃት በማሻሻል ወይንም የመሪዎችን እንከን አጉልቶ በማሳየት ረገድ ሚናቸው የጎላ ነዉ:: ለዚህም ነው ከታላላቅ መሪዎች ስኬት ጀርባ ታላላቅ ተከታዮች አሉ የሚባለው:: ተከታይ የሌለው መሪ የለም፤ እያንዳንዱ መሪም የሌላ መሪ ተከታይ ነው:: ማንኛውም ሰው መሪ ከመሆኑ በፊት ተመሪ ወይም ተከታይ ይሆን ዘንድ ተፈጥሮዓዊ ሕግ ያስገድዳልና። በመርህና በተቋማዊ እሳቤ የተቃኘ የመሪዎችና የተከታዮች መስተጋብር ለተቋማት ስኬት መሰረት ነዉ::
ይህን መስተጋብር በጥልቀትና በስፋት ለማወቅም የዘርፉ ተመራማሪዎችና ልሂቃን እ.ኤ.አ ከ1960ዎች ጀምሮ ከፍተኛ ጥረት ሲያደርጉ ቆይተዋል:: በማድረግም ላይ ናቸው:: እየሱስ ክርስቶስ በዚች ምድር በቆየበት ጊዜ ከተከታዮቹ ጋር የነበረው ግንኙነትና ተከታዮቹ (ዐሥራ ሁለቱን ሐዋርያት ጨምሮ) ያሳዩት የነበረውን ባሕሪያት ለመረመረ ለዘርፉ ልሂቃን ጥሩ መነሻ ሆኗል ብየ አምናለሁ::
በሥራ አመራር ትምህርት ዉስጥ ለሚጠቀሱ ታዋቂ የስኬት መስተጋብራዊ ቀመሮችም ቅዱስ መጽሐፍና ቅዱስ ቁርዓን መነሻ እንደሆኑ መገመት አይከብድም:: የኖህን፣የሎጥን፣ የሙሴን፣ የንጉሥ ዳዊትን፣ የንጉሥ ሶሎሞንን ወዘተ በግብና በጥበብ የታጨቀ የመሪነት ታሪክ እና በተቃራኒዉ ደግሞ የዔሳዉንና የናዝራዊ ሳምሶንን መርሕና ግብ አልባ የመሪነት ታሪክ ለአብነት ማዉሳት ይበቃል:: የዚህን ዝርዝር በሌላ ጽሑፍ ለመዳሰስ እሞክራለሁ::
የተለያዩ የምልከታና የአመራር ዘዴዎችን/ንድፈ ሐሳቦችን/ በመጠቀም የተከታይ ዓይነቶችን ወይንም ዋና ዋና ባሕሪያቸውን ከሶሥት እስከ ሰባት በሚሆኑ መደቦች ከፍሎ ማየት እንደሚቻል ጥናቶች ያመላክታሉ:: አንድ ተከታይ በዉጫዊ ምክንያቶች፣ በአስተሳሰብ ለዉጥ፣ በትምህርትና ስልጠና፣ በልምድ ልዉዉጥ፣ በመሪው የአመራር ዘይቤ/ተግባር/ ወዘተ ከአንዱ ምድብ (ዓይነት) ወደ ሌላ ምድብ ሊገባም ይችላል:: የሀርቫርድ ዩኒቨርሲቲዋ ምሁር ባርባራ ኪለርማን እ.ኤ.አ በ2007ዓ.ም 'መሪዎች ስለተከታዮቻቸው ማወቅ ያለባቸው ጉዳዮች' በሚለው ጽሑፋቸው ተከታዮችን በአምሥት ምድብ በመክፈል ሰፊ ገለፃ አድርገዋል::
እ.ኤ.አ በ2014ዓ.ም ካናዳዊቷ ብሪጀት ሀያስንፍ የተባሉት ተመራማሪ በጥናታቸው የመሪ ተከታዮችን በሰባት ከፍለዉ ያዩበት መንገድ የተሻለና ሁሉን አካታች ሆኖ ስላገኘሁት የራሴን ሰፊ የግል ምልከታና ተሞክሮ በማካተት ዝርዝሩን እንደሚከተለው አቅርቤአለሁ::
ሰባቱ የተከታይ ዓይነቶች:-
1.ታማኝ ደጋፊ፣
2.እውነተኛ (ምክንያታዊ)፣
3.ወላዋይ (ጥቅመኛ)፣
4.አሽቃባጭ (ብልጣብልጥ)፣
5.ተመልካች (ጉልት)፣
6.ሤረኛ(ሸፍጠኛ/ከዳተኛ) እና
7.ነቃፊ (ተቃዋሚ) ናቸው::
መሪዎች የተከታዮቻቸውን ዓይነት ጠንቅቀው ማወቅና ተቋምን ያስቀደመ አካባቢያዊ መስተጋብር መፍጠር ይገባቸዋል:: ከዚህ በተጨማሪም ሂደቱ ዉስብስብና አስቸጋሪ ቢሆንም በአንድ ምድብ ዉስጥ የሚገኙ ተከታዮችን ብዛትና ያላቸውን ተቋማዊ ሚና በተቻለ መጠን ማወቅ ይጠበቅባቸዋል:: ታዋቂዉ ፈላስፋ አርስቶትል እንዳለውም ተከታዮቹን ጠንቅቆ ማወቅ ያልቻለ መሪ ዉጤታማ ለመሆን ይቸገራል::
ፕ/ር ዶናልድ ሎምባርዲ አዳዲስ የጤና አመራሮችን ለማገዝ በ2001ዓ.ም (እ.ኤ.አ) በጻፉት መጽሐፋቸው እንደተገለፀው ከተከታዮች መካከልም ኮከብ ሠራተኞች ከ15-20%፣ አጥጋቢ/መካከለኛ/ አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ከ60-70%፣ ለተቋማዊ ስኬት አወንታዊ ሚና የሌላቸው ደግሞ ከ10-15% እንደሆኑ አውቆ መስተጋብሩን ከዚህ ስሌት አንፃር መቃኘት ያስፈልጋል::
1.ታማኝ ደጋፊ ተከታዮች፤
እነዚህ ተከታዮች መሪያቸውን ከልባቸዉ የሚደግፉ፣ የሚወዱና የሚያደንቁ ደቀ መዝሙሮች ናቸው:: የመሪያቸው ተልዕኮ እንዲሳካና ተቋማቸው ዉጤታማ እንዲሆን እጅግ የሚተጉ ናቸው:: መሪያቸዉም በእነዚህ ሰዎች ይተማመናል፤ አብዛኛዉን ሥራም በእነዚህ ሰዎች በኩል ያስፈጽማል:: ለእነዚህ ተከታዮች መታመን አንጡራ ሀብታቸው ነው:: ይሁን እንጅ እነዚህ ተከታዮች የመሪያቸዉ ፍፁም አድናቂ ከመሆናቸው የተነሳ በሥራ ሂደት የሚታዩ ስህተቶችን መጠቆም/ማመላከት/ ስለማይችሉ መሪያቸዉ በሚያገኘው እንከን የለሽ ግብረ መልስ አማካኝነት አልፎ አልፎ ወደ ተሳሳተ አቅጣጫ ሊያመራ ስለሚችል ግቡን እንዳያሳካ ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ::
'የመሪ እንጅ የተመሪ እዉር የለም' የሚባለው አባባል ለታማኝ ተከታዮች አይሰራም:: ለእነዚህ ተከታዮች ጥሩ ምሳሌ የሚሆነው የዐፄ ቴዎድሮስና የፊታውራሪ ገብረሕይወት ጎሹ ('ገብርየ') የመሪና የተከታይ ታሪክ ነው::
ታሪክ ዘካሪው ተክለፃዲቅ መኩሪያ እንደከተበው ብላቴናው ገብርየ ገና በሃያ ዓመቱ በመይሳው አባ ታጠቅ ካሳ ጀግንነት ተማርኮ መይሳውን ከተሻረከባት ዕለት ጀምሮ የጦር አበጋዝ ሆኖ ለመይሳው በጀግንነት ከጀነራል ሮበርት ናፒየር ጦር ጋር በመፋለም ላይ እንዳለ በኢሮጌ መቅደላ በክብር እስከተሰዋባት ቀን (ሚያዝያ 3፤1860ዓ.ም) ለመሪው ለዐፄ ቴዎድሮስ ፍፁም ታማኝነቱን ያረጋገጠ የጦር መሪ ነበር:: ስለሆነም በኔ ዕይታ እነዚህ ታማኝ የመሪ ተከታዮች 'ገብርየዎች' ተብለው ሊጠሩ ይችላሉ::
2.እዉነተኛ(ምክንያታዊ)ተከታዮች፤
እነዚህ ተከታዮች የተቋማቸዉን ነባራዉ ሁኔታና የመሪያቸዉን አፈፃፀም በመርህ፣ በእዉነትና በአመክንዮ እየገመገሙ መልካም ሥራ እስከተሠራ ድረስ መሪያቸዉን መቶ በመቶ የሚደግፉ ናቸው:: በሥራ ሂደት የሚታዩ ስህተቶች/ክፍተቶች/ ካሉ ደግሞ በይፋ ገንቢ አስተያየት ይሰጣሉ:: ለተቋማቸው ዉጤታማ መሆን የተሻለ መንገድ አለ ብለው ሲያምኑ መሪያቸዉን በአመክንዮ ይሞግታሉ::
ከተቋም ግንባታ አንፃር የእነዚህ ተከታዮች አስተዋጽኦ እጅግ ከፍተኛ ስለሆነ መሪዎች በቅርበት ሊይዟቸው ይገባል:: አልፎ አልፎ በመሪውና በእውነተኛ ተከታዮች መካከል ሰፊ የእሳቤ ወይም የልምድ ልዩነት ሲኖር የመሪዉ አዳዲስ ፈጠራዎች/የአመራር ዘዴዎች እንዳይተገበሩ ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ::
3.ወላዋይ (ጥቅመኛ) ተከታዮች፤
እነዚህ ተከታዮች ዋናው ትኩረታቸው የራሳቸዉን ጥቅም ማስጠበቅ ስለሆነ ስልጣን/ጉልበት/ ካለው አካል ጋር ከመጣበቅ ወደኋላ አይሉም:: በመሪያቸው መወደስ፣ መመስገን፣ መሸለም ወዘተ የደስታቸው ምንጭ ነዉ:: መሪያቸውን ለግላዊ ስኬታቸው መሰላል አድርገው ይቆጥራሉ:: "አንች ምን ቸገረሽ ሁለት አባት አለሽ÷ አንዱ ሲሞትብሽ 'ባንዱ ትምያለሽ" እንደሚባለው እነዚህ ተከታዮች የተሻለ ጥቅም የሚያስገኝላቸው አካል ካገኙ ወይም የሚያገኙ ከመሰላቸው ደግሞ በብርሃን ፍጥነት ዐይናቸዉን በጨው አጥበው ዘወር የሚሉ፣ ኃፍረት (ይሉኝታ) የሚባል ነገር የማያዉቁ አፍቅሮተ ዉዳሴ/ንዋይ/ የተጠናወታቸው ናቸው:: መርጦ ማወደስና መርጦ ማልቀስ መገለጫቸው ነው:: ለእነዚህ ሰዎች ጨዋነት፣ ሥነ ምግባር፣ ሞራል፣ አሠራርና ደንብ ዋጋ የላቸውም/ይጣሳሉ/::
ይህን ዓይነት ባሕሪ የተላበሱ ሰዎች በሁሉም የሥራ ዘርፎች/ተቋማት ቢኖሩም የፖለቲካዉ ዓለም የዘወትር ነፀብራቅ ናቸው:: የታዳጊ ሀገራት መሪዎች ከበለፀጉ/ኃያላን/ ሀገራት መሪዎች የሚኖራቸው ግንኙነት በአብዛኛው በዚህ የመሪ-ተከታይ መስተጋብር ላይ የተመሰረተ ነው::
በንግድ ሥራ በተሰማሩና በማኅበረሰብ አንቂዎችም ዘንድም ይታያሉ:: መሪዎች እነዚህን ተከታዮች በተቻለ መጠን ለይተዉ ማወቅ ከቻሉ ለተቋም ግንባታ ሊጠቀሙባቸው ይችላሉ:: ከሽልማት ጋር የተቆራኙ ፍፁማዊ ለውጦችን በፍጥነት ከመተግበር አንፃር ሚናቸው የጎላ ነዉ:: ጥቅማቸው ሳይከበር ሲቀር ደግሞ የተቃዋሚ ተከታዮችን ጎራ በቀላሉና በፍጥነት ሊቀላቀሉ ይችላሉ::
4.አሽቃባጭ (ብልጣብልጥ) ተከታዮች፤
እነዚህ ተከታዮች 'ንጉሡ ሺ ዓመት ይንገሱ'፣ 'ሰማይ አይታረስ ንጉሥ አይከሰስ'፣ 'አለቃ ሁሌም ትክክል ነዉ' ወዘተ የሚሉ ዓይነት ሰዎች ናቸው:: ከመሪያቸው የመጣን ነገር ቢያምኑበትም ባያምኑበትም፣ ትክክል ይሁንም አይሁንም እሽ በማለት የተካኑ አሽቃባጭ ተከታዮች ናቸው:: 'ፀሀይ በምዕራብ ትወጣለች' ወዘተ ቢባሉ ጌታዬ ልክ ብለዋል የሚሉ ዓይነት ሰዎች ናቸው:: ለመሪያቸው ስጦታና መሰል ነገሮችን በመስጠት አድናቆታቸዉን ለመግለጽና መሪያቸውን በዉዳሴ ለማማለል ይሞክራሉ:: አድናቂ መሆናቸውን ለማሳወቅ የማስታወሻ ፊርማ እስከ ማስፈረም ሊሄዱ ይችላሉ:: ይህ ባሕሪ በኪነ ጥበብና በፖለቲካው ዓለም እጅግ የተለመደ ነው:: አብዱል ራሽድ በሴራሊዮን ቴሌግራፍ (ህዳር 2018ዓ.ም እ.ኤ.አ) እንደፃፈው የአፍሪቃ ፖለቲካ (የፖለቲካ መሪዎችና የተከታዮቻቸው ግንኙነት) በዚህ የተቃኘ ነው::
እነዚህ ተከታዮች ለራሳቸው ያልታመኑና አለቃቸዉን ለመገሰፅ ቅንጣት የማይደፍሩ አስመሳዮች በመሆናቸው ከፍተኛ ማሳለሰል ለሚጠይቁና ከበድ ያለ ዉሳኔ ለሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች አጋዥ አይሆኑም::
መሪዎች ሳያውቁ ከበድ ባሉ ጉዳዮች ላይ እነዚህን ተከታዮች ሲያማክሩ/ሲያሳትፉ/ ከፍተኛ ጥንቃቄ ካለደረጉ የተሳሳተና አደገኛ ዉሳኔ እንዲወስኑ ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ:: ተቋሙን ለውድቀት ሊዳርጉት ይችላሉ:: የመሪዎች ታላቁ ፈተናም እነዚህንና መሰል ተከታዮችን ከታማኝ ደጋፊዎች የመለየቱ ሥራ ነዉ::
5.ተመልካች(ጉልት) ተከታዮች፤
እነዚህ ተከታዮች ሥራ የሚሠሩት ለደሞወዝ/ለክፍያ/ ብቻ ስለሆነ በመሪያቸውና በተቋማቸው ጉዳይ ዉስጥ በፍፁም አይገቡም:: መሪያቸዉን አይቃወሙም፣ አይደግፉም:: ድምፀ-ተአቅቦ የዘወትር መገለጫቸው ነዉ:: 'እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነዉ' ባዮች ናቸው:: ለራሳቸው ተቆጥሮ የተሰጣቸውን ሥራ ከመከወን ዉጭ በተቋማቸው ዉስጥ ምንም ዓይነት ንቁ ተሳትፎ አያደርጉም:: ስለሆነም 'ጉልት' ተከታዮች ተብለው ሊጠሩ ይችላሉ::
6.ሤረኛ(ሸፍጠኛ/ከዳተኛ) ተከታዮች፤
እነዚህ ተከታዮች መሪያቸዉን ያለበቂ ምክንያት በስዉር አምርረው የሚጠሉና ስኬታማ እንዳይሆን ቀን ከሌሊት ሤራ/ሸፍጥ/ የሚሸርቡ ሰዎች ናቸው:: ስለመሪያቸው ከፍተኛ የሆነ የጥላቻ ስሜት ያለባቸው ተከታዮች ናቸው:: ተቆርቋሪና ታማኝ መስለው ከመጋረጃው በስተጀርባ ደግሞ ለመሪያቸው መቃብር ይቆፍራሉ:: በሌላ አገላለፅ 'የጭቃ እሾህ' የሚባሉ ዓይነት ሰዎች ናቸው:: ተሳካም አልተሳካም መሪያቸዉንና ተቋማቸዉን አሳልፈው ለመስጠት እጅግ ይተጋሉ:: መሪያቸውን ለማድማትና ለማቁሰል እንዲሁም ክስተት የሆኑ ለተቋም አስቸጋሪና ፈታኝ የሆኑ አጋጣሚዎችን ካገኙ መሪያቸው ብቃት እንደሌለው ዐይኔን ግንባር ያርገው ብለው በመሪያቸው የሚሳለቁና በሐሰት ለመመስከር የሚቀድማቸው ተከታይ የለም::
በቅዱስ መጽሐፍ "እንጀራዬን የበላ ተረከዙን አነሳብኝ" ተብሎ እንደተጻፈው መሪያቸው የቱንም ያህል መልካም ቢሆን ጥፋትን ይሰንቃሉ::
በአጠቃላይ ምግባራቸዉ ክርስርቶስን በሠላሳ ዲናር አሳልፎ ከሰጠው ከአስቆረቱ ይሁዳ ጋር ስለሚመሳሰል 'ይሁዳዎች' ይባላሉ:: የሐዲስ ኪዳን መጽሐፍ የትርጓሜ ሊቃውንት እንደሚሉት ከዳተኛው ይሁዳ ክርስቶስን ለመሸጥ ሲወስን ሁለት ዓይነት የጥቅም እሳቤዎች ነበሩት። አንደኛው እሳቤ ጠቁሜ ገንዘቤን እቀበላለሁ፣ ክርስቶስም በተዓምራት አምልጦ እራሱን ያድናል የሚል ሲሆን፥ ሁለተኛው እሳቤ ደግሞ የመጀመሪያዉ ካልተሳካ ገንዘቤን እቀበላለሁ፣ ክርስቶስንም በመስቀል ይሰቀል ዘንድ አሳልፌ እሰጣለሁ የሚል ነበር። ይህን መሰል እሳቤ የሚኖራቸው ንዑስ ተከታዮችም ይኖራሉ::
እነዚህ ተከታዮች የተመሰከረላቸውና የተካኑ ከያንያን/ተዋንያን/ በመሆናቸው ጎበዝና አስተዋይ መሪዎች ሳይቀሩ እነዚህን ሰዎች በአጭር ጊዜ ለመለየትና በቅርብ ርቀት ለመከታተልና የሚፈጥሩትን ጫና ለመቀነስ ብሎም ለማስወገድ ሊቸገሩ ይችላሉ::
ጀማሪ መሪዎች የእነዚህን ሰዎች ተንኮል አስቀድሞ ማወቅና በቂና አዋጭ ተግባራዊ ምላሽ መስጠት ላይ ዉሱንነት ስላለባቸው በቶሎ እጅ ሊሰጡና ተገቢዉን የመሪነት ሚና ሳይወጡ ሊቀሩ ይችላሉ:: ሳይደግስ አይጣላም እንዲሉ የእነዚህ ተከታዮች ቁጥር እጅግ አናሳ ነዉ::
7.ነቃፊ(ተቃዋሚ) ተከታዮች፤
እነዚህ ተከታዮች ደግሞ መደበኛ ሥራቸው የመሪያቸውን ርዕይ፣ ተልዕኮ፣ የአመራር ስልቶች፣ ፖሊሲዎች፣ የሥራ ዉጤቶች ወዘተ መንቀፍና መቃወም ነዉ:: ካልነቀፉ/በተቃርኖ ካልቆሙ/መንግሥተ ሰማይን የሚወርሱ አይመስላቸዉም:: በመሪያቸው ወይም በተቋማቸው ተገቢዉን ክብር ወይም ሽልማት አላገኘንም ብለው የሚያስቡ ወይም ግላዊ ትልማቸው የተሰናከለባቸው በመሆናቸው የተቃዉሞ ድምፅ በይፋ በማሰማትና አሉታዊ ተፅዕኖ በማሳደር በራሳቸው እሳቤ ይገባናል የሚሉትን ክብርና ዝና ለማስመለስ ደፋ ቀና ይላሉ:: ድርጊታቸው በቅዱስ መጽሐፍ (ዘፍጥረት 28:1፤6-9) ከጠተቀሰው ዔሳው ጋር ይመሳሰላል፤ ዔሳው ወላጆቹን የሚያስደስተውን ሲያውቅ የእርሱን ተቃራኒ ያደርግ ነበርና:: ስለሆነም 'ዔሳውያን'/የዔሳው ተከታዮች/ የሚል ስያሜ ሰጥቻቸዋለሁ::
ነቃፊ ተከታዮች የሚባሉት ለንግሥና መታጨት የማይፈልጉ (ወይም የማይታጩ)፣ የሚፈልጉትን ለማንገሥ ግን ብዙኃኑን ለማንቀሳቀስ የሚታትሩ ተከታዮች ናቸው:: የተቋም ዉክልና ሳይሰጣቸው ከመሪያቸው በተቃራኒ ጎራ በመሰለፍ እራሳቸውን የተቋሙ አጋፋሪ ወይም ጠበቃ አድርገው ይቀርባሉ:: ወደ ተቋማቸው አዲስ ሠራተኛ ወይም እንግዳ ሲመጣ ፈጥነዉ አቀባበል በማድረግና የተቋማቸውን ገጽታ በማጠልሸትና ጨለምተኛ አስተሳሰብንና የተበዳይነት መንፈስን በማስረፅ መሰል ተከታይ ለማፍራት ከፍተኛ ጥረት ያደርጋሉ::
እነዚህ ሰዎች በባሕህሪያቸው መልካቸዉን ስለማይቀያይሩና ተቃዋሚ መሆናቸውን በይፋ ስለሚያሳውቁ፤ ከእነርሱ የሚጠበቀውም ስለሚታወቅ ለመሪዎችና ለሌሎች ተከታዮች ከባድ ፈተና አይሆኑም:: ሆኖም ግን በመሪዉና በሌሎች ተከታዮች ያልታዩ ምልከታዎችን ለማዬት ሊያግዙ ይችላሉ::
በአጠቃላይ ፕ/ር በርናርድ ሞሪስ ባስ (2008ዓ.ም እ.ኤ.አ) እንደሚሉት ጥሩ ተከታዮች መሪያቸዉን በመደገፍና በማቅናት የተሻለ ስኬት እንዲመዘገብ የድርሻቸዉን ይወጣሉ፤ መጥፎ ተከታዮች ደግሞ በተቃራኒው ይሠራሉ:: ለዚህም ነው አሜሪካዊው ተመራማሪ ጂም ኮሊንስ በ2001ዓ.ም እ.ኤ.አ በጻፈው ተወዳጅ መጽሐፍ ('Good to Great') የመሪ የመጀመሪያ ሥራው ጥሩ/ትክክለኛ ሰዎችን ወደ አዉቶብሱ ማሳፈርና ጥሩ ያልሆኑትን ደግሞ ከአዉቶብሱ ማስወረድ ነው የሚለው:: ግብን ከማሳካት አንፃር ጥሩ መሪዎችና ተቋማት ከተከታዮቻቸው በጎ ባሕሪያትን ይፈልጋሉ::
የእያንዳንዱ ተከታይ ባሕሪ ሚናና ለስኬት ያለው ሁለንተናዊ ድርሻ እንደ ተቋሙ ባሕሪና የመሪው ምልከታ ሊለያይ ይቻላል:: ለምሳሌ በጃኔት ሎዌ (1977ዓ.ም) ገለጻ መሰረት ታዋቂውና ቢሊየነሩ ዋረን ቡፌት እንደመሪ የራሳቸውን ተከታቶች/ሠራተኞች/ ለመቅጠር ከፍተኛ ትኩረት የሚሰጧቸው ሶሥት መመዘኛዎችን ነው:-"ቅንነት (integrity)፣ ብልሃት (intelligence) እና ጉልበት/ኃይል (energy):: የመጀመሪያው የጎደለውን ሰው ከቀጠርህ ሌሎች ሁለቱ አንተን እንደሚገሉህ /እንደሚያጠፉህ/ እርግጠኛ ሁን" ይላሉ:: ጂም ኮሊንስም ተከታታዮችን ለመምረጥ ከቴክኒካል ክህሎት ይልቅ ለሥራ ያላቸው ዉስጣዊ የራስ ተነሳሽነት/ፍላጎት/ እና ተመራጭ/በጎ ህሕሪያት ዋና መስፈርት ሊሆኑ ይገባል ይላሉ::
በአሜሪካዊቷ ላውረንስ ሱዳ ጥናት ዉጤት(2013ዓ.ም እ.ኤ.አ) መሰረት ደግሞ ተምኔታይ/እጅግ ተስማሚ/ የተከታይ ባሕሪያት የሚባሉት:-
1.የእችላለሁ አስተሳሰብና ሥነ ልቦና፣
2.የተባባሪነት መንፈስና ቀናኢነት፣
3.ራስን ብቁ አድርጎ የመገኘት ፍላጎት እና
4.ራስን የመለወጥና የማሳደግ ጉጉት ናቸው::
እንደ ላውረንስ ሱዳ (2013ዓ.ም እ.ኤ.አ) እና ፕ/ር ኖርማን ቦልድዊን (2017ዓ.ም እ.ኤ.አ) ጥናታው ጽሁፍ እንዲሁም የራሴ ግላዊ የመሪነት ምልከታ/ተቋማዊ ልምድ/ ከእነዚህ ወሳኝና ጥቅል ባሕሪያት በተጨማሪ መሪዎች ከተከታዮቻቸው የሚከተሉትን ዐሥራ አምሥት ባሕሪያት ይጠብቃሉ:: እነሱም:-
1.ሥራ ለመሥራት ፈቃደኛ መሆን፣
2.የዉጤታማ ተግባቦትና የጠንካራ ማኅበራዊ ክህሎቶች ባለቤት መሆን፣
3.አስቸጋሪና ፈታኝ የሆኑ ሥራዎችን ተቀብሎ የመሥራት ፍላጎትና ቁርጠኝነት፣
4.ለመሪ፣ ለተቋምና ለሥራ ባልደረባ አጋዥ መሆን፣
5. የመሪን የሥራ ዘይቤና አጀንዳዎች ማጥናትና መረዳት መቻል፣
6.ዉጤታማ ሥራ መሥራትና ሌሎችን ተከታዮች ማሠራት፣
7.አዋጭና ተአማኒነት ያላቸውን የለዉጥና የስኬት መንገዶችን ለመጠቆም መትጋትና በተሻለው አማራጭ መፅናት፣
8.የግልና ውጫው የሆኑ ችግሮችን ወደ ተቋም ይዞ አለመግባት/ሻንጣን አራግፎ መግባት/፣
9.በያገባኛልና በተቆርቋሪነት መንፈስና በተዓማኒነት መሥራት፣
10. ለሌሎች ተከታዮች ጥሩ ምሳሌ ሆኖ መገኘት፣
11.በፈታኝ/በአስቸጋሪ/ ሁኔታ ዉስጥም ሆኖ በተስፋ መራመድ መቻል፣
12.ጠንካራና በመተማመን ላይ የተመሰረተ ሞያው ግንኙነት መገንባት፣
13.ለሞያዊ ሥነ ምግባር ተገዥና ታማኝ መሆን፣
14.እብሪተኛና ራስ ወዳድ አለመሆን እና
15.ለራስ የሚሰጥ ከፍተኛ ግምትን (የተጋነነ/ገደብ የለሽ/ የእችላለሁ እሳቤን) ('ego') መቆጣጠር መቻል ናቸው::
ከላይ እንደገለጽሁት የመሪ ተከታዮች ክፍፍል በጥቅሉ የተከታዮችን ዝርዝር ባሕሪያት ለማሳየት ቢረዳም አንድ ሰው በሂደታዊ/ምክንያታዊ/ወዘተ ለዉጦች ከአንዱ ምድብ (ዓይነት) ወደ ሌላ ዓይነት ተከታይ ሊቀየር/ሊለወጥ/ እንደሚችል በማወቅ የተከታዮችን ወቅታዊ ምድብ በማጤን በተመተሩ ስልቶች መስተጋብርንና ተግባቦትን በየጊዜው ማስተካከል የግድ ይላል::
ታዋቂው አሜሪካዊ የሥነ ልቦና ባለሙያና ተመራማሪ ስኮት ቤሪ ኮፍማን እንደሚሉት ሰዎች ብዙ ጊዜ ከጥሩው ባሕሪያቸውና ማንነታቸው ይልቅ ወደ መጥፎውና በመጠራጠር የተሞላውን ውስጣዊ ስሜት ይመርጣሉ። ስለሆነም መሪዎችም የተመሰከረላቸውንና ነባራዊ ሁኔታን ያገናዘቡ የመሪነት ጥበቦችን በመጠቀም ተከታዮቻቸው ገንቢ ባሕሪያትን እንዲላበሱ የአንበሳውን ድርሻ መወጣት ይኖርባቸዋል::
የቁስ፣ የገንዘብና መሰል ነገሮች ልዕልና ገኖ የሞራልና የመንፈስ ልዕልና እንዳይኮስስ መሪዎች የተቋማቸውንና የተከታዮቻቸውን የግብረ ገብ ዕሴቶች በማሳደግ መልካም ባሕሪያትን ለማስረፅ መጣር አለባቸው:: ከዚህ በተጨማሪም እንደተቋሙ ነባራዊ ሁኔታ፣ የማኅበረሰብ እድገት/የእሳቤ ደረጃ/ እና የሥነ ልቦና ውቅር ተፈላጊ ባሕሪያትን ለይቶ በማወቅና በማጎልበት እንዲሁም ከተቋሙ የሥራ ዘርፎች ጋር በማጣጣም የመሪ ተከታይ ስምሪት መፍጠር ይገባል:: ይህ የአመራር ዘይቤ ተከታይ መሪዎችን ለማፍራትም ጠቀሜታው የጎላ ነው::
ዋቢ መጽሐፍት/ጽሁፎች
===
[ኮድ አርም]1.ባርባራ ኪለርማን (2007ዓ.ም): መሪዎች ስለተከታዮቻቸው ማወቅ ያለባቸው ጉዳዮች
2.ብሪጀት ሀያስንፍ (2014ዓ.ም): ሰባቱ የመሪ ተከታይ ዓይነቶች
3.ዶናልድ ሎምባርዲ (2001ዓ.ም): የመምሪያ መጽሐፍ ለአዳዲስ የጤና አመራሮች
4.በርናርድ ሞሪስ ባስ (2008ዓ.ም): የባስ የመሪነት መምሪያ መጽሐፍ: ንድፈ ሃሳብ፣ ምርምርና አተገባበር
5.ላውረንስ ሱዳ (2013ዓ.ም): ተከታዮችን ማሞገስ
6.ኖርማን ቦልድዊን (2017ዓ.ም): ዘጠኙ ተምኔታይ የተከታዮች የስብዕና ቅንጣቶች/ባሕርያት/