ኦጦ

ከውክፔዲያ
(ከኦቶ የተዛወረ)
ኦጦ የሮሜ ቄሣር

ማርኩስ ሳልዊዩስ ኦጦ ለአጭር ዘመን ለ፫ ወር ከጥር ወር 61 ዓም ጀምሮ የሮሜ መንግሥት ቄሣር ነበር። የአራቱ ቄሣሮች ዓመት ሁለተኛው ንጉሥ ነበረ።

ኦጦ በ24 ዓም በጣልያን ተወለደ። በሮሜ ግቢ፣ ነጉሥ ኔሮን እንደ ጎበዝ ወጣት ቆጠረው። ኔሮን ግን ሚስቱን ከቃመ በኋላ ኦጦን ወደ ሉሲታኒያ (ፖርቱጋል) እንደ አገረ ገዥ ላከው።

ጋሊያ ሉግዱኔንሲስ (ፈረንሳይ) እና የሂስፓኒያ ታራኮኔንሲስ (ስፔን) ክፍላገራት አገረ ገዦች በአመጽ ሲነሡ ኦጦም ከጸረ-ኔሮን ወገን ጋራ ተባበረ። ኔሮን ራሱን ከገደለ በኋላ የሂስፓኒያ አገረ ገዥ ጋልባ ቄሣር ሆነ።

የኦጦ መሀለቅ

በጥር ወር 61 ዓም የጌርማኒያ ሥራዊት በጋልባ ላይ አመጹበትና የጌርማኒያ አገረ ገዥ ዊቴሊዩስ ንጉሥ እንዲሆን አዋጁ። ጋልባ በሮሜ ቆይቶ አልጋ ወራሹ ሉኪዩስ ካልፒኒዩስ ፒሶ እንዲሆን ሰየመው። በዚህ ኦጦ በተለይ ተናደደ፣ አልጋ ወራሽነቱን ለራሱ መኝቶ ነበርና። የሮሜ ሥራዊት ደግሞ ኦጦን ደገፈውና በጋልባ ላይ አመጹ። ጋልባ በድካምነቱ በቃሬዛ ተሸክሞ ሲቀርብላቸው ገደሉትና ያንጊዜ ኦጦ ለአጭር ወራት በፈንታው የሮሜ ቄሣር ሆነ። መልኩ ለኔሮን ተመሳሳይነት ስለነበረው በሮሜ ዜጎች መኃል እንደ አዲሱ ኔሮን ተወደደ። የኔሮንም ሰዶማዊ «ባል» ስፖሩስ ለራሱ «አገባ»።

ከዚያ ኦጦ የጋልባን ሰነዶች አንብቦ የዊቴሊዩስ ሥራዊት ከጌርማኒያ ቶሎ እንደሚደርስ ተረዳ። የዊቴሊዩስ ወገን ወደ ጣልያን ገብቶ አሸንፎም ኦጦ ብሔራዊ ጦርነት እንዳይስፋፋ እንደ ኔሮን ራሱን እንደ ገደለ ይባላል። ስለዚህ በፈንታው ዊቴሊዩስ በሚያዝያ የሮሜ ቄሣር ሆነ።