ኑግ በሮማይስጥ Guizotia abyssinica በመባል የታወቀው የእህል ዘር ነው። ኑግ በተፈጥሮ በኢትዮጵያ እና ማላዊ የተገኘ ተክል ነው። በአሁኑ ዘመን፣
ይህን የዘይት እህል በብዛት የሚያመርቱ ኣገሮች ኢትዮጵያና ሕንድ ናቸው ይባላል፣ ሌሎችም አሉ።
ወፎች ስለሚወድዱት ብዙ አገሮችም ያስገቡታል። ዘሩ ወደ ሌላ አገር ሳይገባ ግን የአረም ዘሮች ስላሉበት ጉንቆል እንዳይሆኑ ለ15 ደቂቃ በከፍተኛ ሙቀት እንዲቆይ ይገደዳል።
በደቡብ ሕንድ አበሳሰል በአንዳንድ ወጥ ወይም ስጎ ውስጥ ይገኛል። የኑግ ዘይት፣ ቅባኑግም ያስገባሉ፤ በአበሳሰል በወይራ ዘይት ፈንታ ሊጠቀም ይችላል፣ ወይም ሳሙና፣ ቀለም መቀብያ በማዘጋጀት በኢንዱስትሪዎች ይጠቀማል። በተለይ በኢትዮጵያ ቅባኑግን ከማውጣት የተረፈው የዘሩ እንጐቻ ለከብት መኖ ይሰጣል።
በኢትዮጵያ የተቆለለና የተደቀቀ ኑግ ውጥ በስኳርና በውሃ ጉንፋን ለማከም ይጠቀማል። የደቀቀ ኑግና ተልባ ለጥፍ ለቆዳ ፋቂዎች ይጠቀማል። እንዲሁም የኑግና የመተሬ ዘር ለጥፍ ለኮሶ በሽታ ይሰጣል። ቁንጭር (ሌይሽመናይሲስ) ለማከም የኑግ፣ የነጭ ሽንኩርት ልጥና የኣዞ ሓረግ ቅጠል ተደቅቀው በለጥፍ ትንሽ ሙቅ ተደርጎ ይቀባል።[1]