ያልተወለደው ሌባ

ያልተወለደው ሌባ (English: yaliteweledew leba በ2017 ዓ.ም የታተመ)፡ ልብ አንጠልጣይ የሣይንስ፣ የፍቅር እና የታሪክ ልብወለድ ሲሆን በኢትዮ-አሜሪካዊቷ የማቴሪያል ኢንጂነሪንግ ሣይንቲስት በሆነችው ፕሮፌሰር ሶስና ሃይሌ ሕይወት ታሪክ ላይ ያጠነጥናል፡፡
መጽሐፉን ሜክሲኮ የሚገኘው ጃፋር መጽሃፍ መደብር እያከፋፈለው ይገኛል፡፡
ያልተወለደው ሌባ ታሪኩ አዲስ-ዓለም ከምትባል ኢትዮጵያ ውስጥ ካለች አነስተኛ መንደር ውስጥ የሚጀመር ሲሆን፤ ሚናስ ከተባለ አንድ ሚስጥርን እና እንቆቅልሽን ለመፍታት ከሚታትር ሰው ይጀምራል።
ሚናስ በሰፈሩ ውስጥ ቅርብ ጊዜ የተከሰተ አንድ ሽማግሌ ሰው ያስተውላል። ይህ ሰው ቀልቡን ይገዛውና ሰውየውን ይቀራረበዋል፤ በጊዜ ሂደት ሚናስ ሽማግሌውን ተግባብቶ የግል ምስጢሩን ይነግረዋል። ይህ ሽማግሌ ስሙ ብሥራት የሚባል ሲሆን ሀብት ንብረቴን ባልተወለደ ልጅ ተዘረፍኩ የሚል ሰው ነው፤ ብሥራት ሊቀ-ኅሩያን የሚባሉ አያት ነበሩት፤ አያቱ የታወቁ የቤተ-ክህነት መመህር ሲሆኑ በድብቅ ደግሞ አስማተኛም ናቸው፤ ብሥራት በትምሕርቱ ደካማ ስለነበር አያቱ በአንድ ሌሊት ጎጃም ውስጥ ወዳለ የአባይ ወንዝ ገባር በሆነ ተፋሰስ ውስጥ ይወስዱትና ለደካማ የአብነት ተማሪዎች ትምህር እንዲገባቸው የሚደገምን የዘኢያገድፍ ድግምት ይደግሙለታል። ይህ አስማት ከተደረገለት በኋላ ብሥራት እሳት የላሰ ተማሪ ሆነ፤ በኋላ ላይ ብሥራት ወደ ደብረ ታቦር ከተማ በመሄድ የሁለተኛ ደረጃ ትምሕርቱን እየተከታተለ ሳለ ሕዳሴ ከምትባል ልጅ ጋር በፍቅር ይወድቃል። ሕዳሴም በብሥራት ፍቅር ትወድቅና ከእለታት በአንዱ ቀን የግብረ-ሥጋ ግኑኝነት ይፈጽማሉ። ከዚህ ቅጽበት በኋላ ብሥራት የአእምሮ ኃይሉ ቀስ በቀስ እየራቀው ይመጣና በትምሕርቱ ደካማ እየሆነ ይመጣል። ነገሩን ሲያጤን አያቱ ሊቀ-ኅሩያን ከእንስት ጋር እንዳይተኛ እንዳዘዙት ያስታውሳል፤ ይህም ብቻ ሳይሆን ብሥራት ሙሉ የአእምሮውን ኃይል ከፍቅረኛው በጸነሰው ልጅ ይዘረፋል።
ሚናስ ይህንን ታሪክ ከብሥራት ይሰማና ይገረማል፤ ከብዙ ዓመታት በኋላም በጅማ ዩኒቨርስቲ ውስጥ ትምህርቱን እየተከታተለ ሳለ በአሜሪካን ኢምባሲ በተዘጋጀ ውድድር ይሳተፍና ከተወዳዳሪዎች 4ተኛ በመውጣት ናሳን የመጎብኘተ እድልን ያገኛል። ኋላ ላይ ሚናስ ይህ እድል ወጥመድ ሆኖ ያገኘውና ያዝናል፤ የአሜሪካ መንግሥት ሆነ ብሎ በተለያዩ ድሀ ሀገራት እንዲህ ያለ ውድድር አዘጋኝቶ ሰዎችን ወደ አሜሪካ በማምጣት አዲስ የተሠራ የጊዜ ማሽን መሞከሪያ ሊያደርጋቸው ነው፤ የጊዜ ማሽኑ በከፍተኛ ፍጥነት የሚነጠቅ ሲሆን በጊዜ ወደፊት እና ወደኋላ መሄድ ያስችላል፤ ወደኋላ በመሄድ ድሮ የተደረጉ ክስተቶችን ሲያስቃኝ ወደፊት በመሄድ ደግሞ ወደፊት የሚደረጉ ነገሮችን ያሳያል። ይህ ማሽን እስካሁን ሰው ያልተጓዘበት ሲሆን የአሜሪካ መንግሥት ከድሀ ሀገራት ሰዎችን መልምሎ መሞከሪያ ሊያደርጋቸው ነው፤ በአጠቃላይ አሥር ሰዎች ከተለያየ ሀገራት ሲሰበሰቡ ሚናስ ኢትዮጵያን በመወከል ከአሥሩ አንዱ ነው፤ በጊዜ ማሽኑ የመጀመሪያ ሙከራ ጉዞ ላይ አሥር ሰዎች ሲሳተፉ፤ በጉዞው ላይ ዘጠኙ ሰዎች ሞተው ሚናስ ብቻውን ይተርፋል፤ ለዚህ ሚስጥሩ ደግሞ ከተመራማሪዎቹ አንዱ ከሁሉም የተለየ የጉዞ ጭንብል ስላጠለቀለት ነው፤ ሚናስ ይህ ሰው ለምን ለእሱ ብቻ እንዲህ እንዳደረገለት ግራ ገብቶት ሲጠይቀው፤ ወረቀት ጽፎ ይሰጠዋል፤ ሁሉም ተመራማሪዎች ጭንብል ስላደረጉ መልካቸው አይታይም፤ ወረቀቱ ላይ “ማታ ሆቴልህ ክፍል መጥቼ አናግርሀለው” ይላል፤ ሚናስ ሆቴሉ ክፍል ውስጥ ቁጭ በሎ ሲጠብቅ ይውልና እኩለ-ሌሊት ላይ ሆቴል የያዘበት ክፍል ይንኳኳል፤ ወጥቶ በሩን ሲከፍት ከፊት ለፊቱ አንዲት ኢትዮጵያዊት ሴት ያያል እርሷም ፕሮፌሰር ሶስና ሃይሌ ትባላለች፤ ሕይወቱን ስላተረፈችለት ሕይወት ብሎ ይጠራታል፤ በቆይታቸው ስለ ሕይወት ታሪኳ፣ ስለ ጊዜ ማሽን ኮንሰፕት እና ስለ አጠቃላይ የዓለም መጻኢ እድል ትነግረውና ይጽፋል፤
ሚናስ የጉብኝት ጊዜውን አጠናቆ ከአሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ ጉዞ ላይ ሳለ፤ ድሮ በሚያውቀው ሽማግሌው ብሥራትና እና በሕይወት መሀከል የሆነ ግኑኝነት እንዳለ የሚመስል አንድ ፍንጭ ያገኝና ለማጣራት ባለመሞከሩ እና ያኔ ሀሳቡ ስላልመጣለት ይናደዳል፤ አላስችል ይለውና እንደ እብድ አድርጎት ከዋሽንገተን ተነስቶ ወደ ኢትዮጵያ እየበረረ ያለውን አይሮፕላን መልሰህ ወደ ዋሽንገተን ተመለስ ብሎ ጉዞ ላይ ግርግር ሲፈጥር የእንቅልፍ መዳኒት ወግተው ጸጥ ያሰኙታል፤ ኋላ ላይ ይህንን እንቆቅልሽ ለመፍታት ይታትራል።
መጽሐፉ ባለ 380 ገጽ ሲሆን የታሪክ፣ የሳይንስ በተለይም የጊዜ ማሽን ጽንሰ ሀሳቦችና እና የፍቅር ይዘቶች አሉት፤ የታተመው በማይቢቲ ማተሚያ ቤት ሲሆን የመጽሐፉ ደራሲ በግልጽ አይታወቅም፤ የብእር ስሙ ዶ/ር በኃይሉ ደመቀ ሲሆን ምናልባት የሄኖክ ኃይሌ ሊሆን ይችላል የሚል ግምት አለ፤ መጽሐፉ “the best Amharic fiction book” and ‘the first Amharic science fiction’’ የሚል እውቅናን አግኝቷል፡፡
መጽሐፉ ከዚህ ቀደም መጽሀፍ ጽፈው ባሳተሙ ወይም ደግሞ ከፍተኛ የሥነ-ጽሁፍ ሙያ ባለው ደራሲ ወይም አንድ የታሪክ እና የሣይንሥ እውቀት ባለው ሰው የተጻፈ መሆኑ አያሻማም፡፡ በዚህም መሠረት መጽሐፉን ጽፈውት ሊሆን ይችላል ተብለው ሊጠረጠሩ የሚችሉ ሰዎችን እንደሚከተሉት ናቸው፡፡
ዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ፡ መጽሐፉ ማንነቱ በግልጽ ባልታወቀ ነገር ግን በብዕር ስሙ “ዶ/ር በሐይሉ ደመቀ” በሚባል ሰው ተጽፏል፡፡ የጸሐፊውን የብዕር ስም እንዲሁም የታተመበት ሥፍራን ከግምት ውስጥ በማስገባት፤ አንዳንድ ሰዎች የልብወለዱ ደራሲ ዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ ሊሆን ይችላል የሚል ግምት ይሰጣሉ፤ “ደመቀ” የሚለው ስም የሄኖክ ኃይሌ ባለቤት የሆነችው የወ/ሮ ሣምራዊት ደመቀ የአባት ስም ሲሆን፤ በኃይሉ ደግሞ የሄኖክ አባት ሥም ኃይሌ ጋር መመሳሰሉ ከፍተኛ ጥርጣሬን ሊጥል ችሏል፡፡
መጽሐፉ ጥልቅ በሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ አስተምሕሮዎችና ሚሥጥራት የተሞላ መሆኑ፤ በመጽሐፉ ውስጥ የተጠቀሱት የሣይንስ ጽንሰሀሳቦችም እርሱ ከተማረው የኢንጂነሪንግ የትምሕርት መሥክ ጋር የሚዛመድ መሆኑ፤ ሕማማት የሚለውን መጽሐፉን ባሳተመበት ማተሚያ ቤት ያልተወለደው ሌባም የታተመ መሆኑ እንዲሁም የደራሲው የብዕር ሥም ከሄኖክ አባት እና ከባለቤቱ ከወ/ሮ ሣምራዊት አባት ጋር የሚመሳሰል መሆኑ ከፍተኛ ጥርጣሬን ይጭራል፤ ለምን በራሱ ስም አያሳትመውም ለሚሉ ክርክሮች ምናልባትም በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የተካተቱት የፍቅር ታሪኮች ውስጥ ባሉት ገጸ-ባህርያት መካከል የሚፈጠሩት ግልጽ የወሲብ ነክ ድርጊቶች ከእርሱ ክብር እና ተቀባይነት ጋር የማይሄዱ በመሆናቸው ይሄንን መንገድ መርጦ ተጠቅሞ ሊሆን ይችላል የሚል ግምት አለ፡፡
ዲ/ን ዳንኤል ክብረት፡ ከላይ እንተጠቀሰው ይህ መጽሐፍ እጅግ በጣም ብዙ የሆኑ ገዳማትን እንዲሁም የጥንት ከተሞች ታሪኮችን በሚገባ አሰናስሎ ያቀረበ ሲሆን አብዛኛው የገዳማት ታሪክ ዲ/ን ዳንኤል ክብረት ከጻፈው “የቤተ-ክርስቲያን መረጃዎች” ከሚለው የገዳማት ታሪከ መዝገብ መጽሐፍ ጋር እጅግ ተቀራራቢ ታሪኮችን የያዘ በመሆኑ፤ ከዚህ በተጨማሪም ያልተወለደው ሌባ የሚለው መጽሐፍ ውስጥ አንድ የሐዲስ ኪዳን የሆኑ መምሕር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐብይ አሕመድ በሥደት የነበረውን የአቡነ መርቆርዮስን ሲኖዶስ ሀገር ቤት ካለው የአቡነ ማትያስ ሲኖዶስ ጋር በማስታረቃቸው ክርስትናን አንድ ለማድረግ ከጣረው ንጉሥ ዜኖ (Emperor Zeno) ጋር በማመሳሰል ሲያወድሱት መገኘታቸው ዳንኤል ክብረት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አድር ባይነቱን ያሳየበት መጥሐፍ ሊሆን ይችላል የሚል ከፍተኛ ግምት ያጭራል፡፡ ከዚህም ባለፈ ያለፈውን የሕወኃት ሥርአት የሚያጥላላ ይዘት መጽሐፉ ውስጥ መገኘቱ ይህንን ሀሳብ ያጠናከረዋል፡፡ ለምን በራሱ ሥም አላሳተመውም ለሚለው ክርክር ከአብዛኛው ምዕመናን በተለይም በሰሜኖች ዘንድ በከፍተኛ ደረጃ እየወረደ የመጣውን ተቀበይነቱን ባይፓስ ለማድረግ ነው የሚሉ አሉ፡፡
ረ/ፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ፡ ያልተወለደው ሌባ መነሻው አዲስ ዓለም ማርያም መሆኑ እና ስለቤተ-ክርስቲያኒቱ ታሪክ፣ ስለ ታቦተ ጽዮን እና ስለ አጼ ምኒልክ ቦታዋ ላይ ስለነበራቸው ሰፊ ታሪክ የሚተነትን መሆኑ፤ ቦታው ደግሞ የፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ የትውልድ ሥፍራ መሆኑ እንዲሁም ነብዩ ባዬ የመንግሥት ሹመኛ መሆኑና በመጽሐፉ ውስጥ ከንቱ ውዳሴን የሚወዱትን ዶ/ር ዐብይ አሕመድን ከላይ በተጠቀሰው ሥፍራ ሲያወድስ መገኘቱ፤ ከዚህ በተጨማሪም የልብወለዱ ፍሰት እጅግ ልብ አንጠላጣይ መሆኑ ፕሮፌሰሩ ካላቸው የሥነ-ጽሑፍ እውቀት የመነጨ ሊሆን የሚችል ፍንጭ መስጠቱ ምናልባት በእርግጥም የፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ ድርሰት ሊሆን የሚችልበት ከፍተኛ እድል አለ፡፡ ነገር ግን ለምን ራሱን መደበቅ አስፈለገው ለሚለው ክርክር ያን ያህል አሳማኝ ምክንያት ሊገኝ አልተቻለም፡፡
ዶ/ር ዳዊት ወንድምአገኝ፡ ያልተወለደው ሌባ ላይ አንድ አእምሮን ለማመን የሚከብድ የሕክምና ሣይንስ ተረክ ይዟል፤ ይህም በጽንስ ላይ ጽንስ ወይም ደግሞ በእንግሊዝኛው Superfetation የሚለው ጽንሰ ሀሳብ ነው፤ ይህ ጽንሰ ሀሳብ በሕክምና ሳይንሱ የተደገፈ ሲሆን አንዲት ነፍሰ-ጡር ካረገዘች በሁዋላ ከወር ወይም ከሁለተኛ ወር በኋላ ደግሞ ሌላ ተጨማረ ጽንስ ልትይዝ ትችላለች፤ ያልተወለደው ሌባ የሚለው መጽሐፍ ፕሮፌሰር ሶስና ኃይሌ የተረገዘችበት መንገድ በሱፐርፈቴሽን እንደሆነ ያስረዳል፤ ይህ በሕክምናው የረቀቀው ጽንሰ ሃሳብ በሪሰርች የተደገፈ መሆኑ እንዳለ ሆኖ ይህንን ሀሳብ ሊረዳ ወይም ሊያውቅ የሚችል ሰው የሕክምና ባለሙያ እንደመሆኑ መጠን ዶ/ር ዳዊት የዚህ መጽሐፍ ደራሲ ሊሆኑ ይችላሉ የሚል ከፍተኛ ግምት ያሰጣቸዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ ዋነኛው የልብወለዱ ገጸ-ባሕሪ ሚናስ እራሱን ዶክተር ብሎ የሚጠራ መሆኑና የደራሲው የብዕር ስም ከበስተኋላው ዶ/ር የሚል ተቀጽላ መያዙ ግምቱን ያጠናክረዋል፡፡
ከዚህም ባለፈ ዶ/ር ዳዊት ዲያቆን ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩ ሰው መሆናቸው በመጽሐፉ ውስጥ ለተጠቀሱት ኃይማኖታዊ ታሪኮች ባዳ የሆኑ ሰው አለመሆናቸውንም ያሳያል፡፡
ሌላኛው እርሳቸውም እንደሌሎቹ የመንግሥት ሹመኛ እንደመሆናቸው በመጽሐፉ ዶ/ር ዐብይ አሕመድን ሊያወድሱ ይችላሉ፡፡ በዚህም ምናልባትም እርሳቸው የመጽሀፉ ደራሲ ሊሆኑ የሚችልበት እድል ከፍተኛ ነው፡፡ በራሳቸው ስም ለምን አላሳተሙትም ለሚለው ክርክር ምናልባትም ሳይካትሪስት እንደመሆናቸውና በመጽሀፉ ውስጥ ሱፐርስቲሺያል የሆኑ ነገሮች መገኘታቸው ከሙያቸው ጋር የሚቃረን ሆኖ ተገኝቷል፡፡