ገና

ከውክፔዲያ

ገና
የኢየሱስ ክርስቶስ ልደትና ጥምቀት የ ሚያሳይ ስዕል
የክርስቶስ ልደት ቀን
ዓመተ ዓለም አልፎ በዚች ዕለት ዓመተ ምሕረት ጀመረ
የተወለደው በግርግም (በከብቶች በረት)


ገና የማይከበሩባቸው አገራት።

ገናኢየሱስ ክርስቶስ ልደት የሚከበርበት ቀን ነው። ስሙ የወጣ ከግሪክ Χριστούγεννα /ቅሪስቶው/ገና ማለትም «የክርስቶስ ልደት» ነው። የከበረና የተመሰገነ ታላቅ የልደት በዓል ሆነ የጌታችንና የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከከበረች ድንግል ማርያም የተወለደባት ዕለት ከበዓላት ሁሉ ተለይታ ከፍ ከፍ ያለች ናት ።

ስለ ገና ክፍል ፩[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የቤተ ክርስቲያን መምህራን አባቶቻችን የከበረ የልደትን በዓል በሁለት ቀኖች ያከብሩ ዘንድ በምክራቸው ተስማሙ ከወደኋላ ባለ በሃያ ስምንት ሌሊቱ የልደት በዓል ነው በሃያ ዘጠኝ መዓልቱ ጳጉሜን ስድስት በሆነ ጊዜ በዚያች ዓመት የልደት በዓል በሃያ ስምንት በመዓልት ይከበራል ። ጳጉሜን አምስት ከሆነ ግን በሃያ ዘጠኝ ይሆናል ስለዚህ የበዓላት ሁሉ ራስ የሆነ የከበረ የልደት በዓል በሁለቱ ቀኖች እንዲከበር አዘዙ ወሠኑ ።

የበዓላት ራስ ስለሆነ ስለ ከበረ የልደት በዓል የከበረ ወንጌል እንዲህ አለ ። በንጉሡ በኄሮድስ ዘመን በይሁዳ ዕፃ በቤተልሔም ጌታ ኢየሱስ በተወለደ ጊዜ እነሆ የፍልስፍና ሰዎች ከምሥራቅ መጥተው ወደ ኢየሩሳሌም ደረሱ ። ኮከቡን በምሥራቅ አይተን እንሰግድለት ዘንድ መጥተናልና የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው እያሉ ።

እሊህ ፈላስፎች ከበለዓም ወገን ናቸው እነርሱም በከዋክብት የሚፈላሰፉ ናቸው በመጽሐፋቸው በበለዓም መጽሐፍም የአይሁድ ንጉሥ ሊወለድ እንዳለው ተጽፎአል እርሱ በለዓም ከያዕቆብ ኮከብ ይወጣል ከእስራኤልም ንጉሥ ብሎ ነበርና ።

ይቅር ባይ እግዚአብሔርም በረቀቀ ጥበቡ አለበማቸው በሚያምኑበትም ሳባቸው እነርሱ ከዋክብትን በመጠባበቅ የሚፈላሰፉ ናቸውና ይህንንም ኮከብ ገለጠላቸው በአዩትም ጊዜ ደስ አላቸው መልኩ በብዙ አይነት ልውጥ ነውና ። ሕፃን የታቀፈች ድንግል ብላቴናን ይመስላል እርሱም በቀን ይጓዛል በሌሊትም ይሠወራል ከሰውም ሲገናኙ ይሠወርና ሲቆሙ በሌላ አንጻር ይገለጥላቸዋል ።

እነርሱም ወደ ኢየሩሳሌም ሲደርሱ ያ ኮከብ ተሠወራቸው እጅግ አዘኑ የሚያደርጉትንም አላወቁም ከዚህም በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ ገብተው ስለተወለደው ንጉሥ ጠየቁ ። የእሊህም ሰዎች ቊጥራቸው ሠላሳ ሽህ ነው ነገሥታቱ ሦስት ናቸው ለየእንዳንዱ ንጉሥ ዐሥር አሥር ሽህ ሠራዊት አለው ።

ንጉሡ ኄሮድስም በሰማ ጊዜ ደነገጠ ኢየሩሳሌምም በመላዋ ከእርሱ ጋር ደነገጠች ። የካህናት አለቆችና የሕዝቡን ጸሐፊዎች ሁሉ ሰብስቦ ክርስቶስ በየት ይወለዳል ብሎ ጠየቃቸው ። በይሁዳ ዕፃ በቤተልሔም ነው አሉት በነቢይ እንዲህ ተብሎ ተጽፏልና ።

የኤፍራታ ዕፃ ቤተልሔም አንቺም ከይሁዳ ነገሥታት አታንሺም ወገኖቼ እስራኤልን የሚጠብቅ ንጉሥ ካንቺ ይወለዳልና ። ከዚህም በኋላ ኄሮድስ ሰብአ ሰገልን በጭልታ ጠርቶ ኮከቡ የታየበትን ዘመን ከነሱ ተረዳ ።

ሒዳችሁ የዚያን ሕፃን ነገር እርግጡን መርምሩ ያገኛችሁትም እንደሆነ እኔም መጥቼ እሰግድለት ዘንድ በኔ በኩል ተመልሳችሁ ንገሩኝ ብሎ ወደ ቤተልሔም ሰደዳቸው ። የነገራቸውንም ሰምተው ከንጉሡ ሔዱ እነሆ በምሥራቅ ያዩት ከከብ ወደ ቤተልሔም እስኪያደርሳቸው ይመራቸው ነበር ሕፃኑ ካለበትም ዋሻ ላይ ደርሶ ቆመ ።

ክፍል ፪[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ኮከቡንም ባዩ ጊዜ እጅግ ደስ አላቸው ወደ ቤትም በገቡ ጊዜ ሕፃኑን ከእናቱ ከድንግል ማርያም ጋር አገኙት ወድቀውም ሰገዱለት ሣጥናቸውንም ከፍተው ወርቅ ከርቤ ዕጣን እጅ መንሻ አቀረቡለት ።

በእግዚአብሔርም ፈቃድ ዮሴፍ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሕፃኑ ጌታ ኢየሱስም በዚያች ዕለት ወደ ቤተልሔም መጡ ስለዚህም ሰብአ ሰገል አገኙአቸው የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ናዝሬት በሌላ ቦታ አላደገምና ከተወለደም ዕድሜው ሁለት ዓመት ሆኖት ነበር

አምላክ ነውና ስለ መንግሥቱ ወርቅን ገበሩለት ክህነትም ገንዘቡ ነውና ዕጣንን ገብሩለት ማሕየዊ ለሆነ ሞቱ ምልክትም ከርቤን ገበሩለት ። ወደ ኄሮድስም እንዳይመለሱ በሕልም ነገራቸው በሌላ መንገድም ወደ አገራቸው ተመልሰው ገቡ ። አምላክ በሥጋ ስለመገለጡ ዓዋጅ ነጋሪዎችና ሰባኪዎች ሆኑ ።

ይችም ዕለት ነቢዩ ኢሳይያስ ትንቢት ስለርሷ የተናገረላት ናት እንዲህ ብሎ እነሆ ድንግል ፀንሳ ወንድ ልጅን ትወልዳለች ስሙንም ዐማኑኤል ትለዋለች ትርጓሜውም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ማለት ነው ።

ስለዚችም የከበረች ድንግል ነቢይ ሕዝቅኤል እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ እግዚአብሔርም አለኝ ይህች በር ተዘግታ ትኖራለች አትከፈትም የሚገባበትም የለም የእስራኤል ፈጣሪ እግዚአብሔር እንደተዘጋች ይገባባታልና ተዘግታ ትኑር አለ ።

ነቢዩ ዳንኤልም አለ ሌሊት በራእይ አየሁ እነሆ ታላቁ እንደ ሰው ልጅ በሰማይ ደመና መጣ ዘመኑን ወደ ሚያስረጅ ደረሰ ከፊቱም አቀረቡት የዘላለም አገዛዝ ጌትነት መንግሥት ተሰጠው ሕዝቡና አሕዛቡ ሁሉ መንደር መንድረው የሚኖሩትና ነገዱም ነገሥታቱም ሁሉ ይገዙለታል አገዛዙም የዘላለም አገዛዝ ነው መንግሥቱም የማያልፍ የማይጠፋ ነው ።

ዳግመኛም ኢሳይያስ እግዚአብሔር እንደ እኔ የሥጋ መጋረጃ በመጋረድ ተገለጸልኝ አለ ። አሁንም ደግሞ አዲስ ሰማይ አዲስ ምድር እሠራ ዘንድ አለኝ አለ ሁለተኛም ከዕሴይ ሥር በትር ትወጣለች ከእርሷም ጽጌ አበባ ይወጣል አለ ። ዳግመኛም ሕፃን ተወልዶልናልና ወንድ ልጅም ተሰጥቶልናልና ይኸውም ሥልጣን በጫንቃው የሆነ ክርስቶስ ነው ። ስሙም ድንቅ መካር የዘላዓለም አባት የሰላም አለቃ ይባላል አለ ።

ኤርምያስም አለ እግዚአብሔር እንዲህ አለ በዚያን ወራት ለዳዊት ብርሃንን አወጣለሁ በምድርም የቀና ፍርድን ያደርጋል እግዚአብሔርም ያመኑበትን ያድናቸዋል ።

ኤልሳዕም እንዲህ አለ ። እ ግዚአብሔር ከሰማይ ይወርዳል በእስራኤል ልጆች አደባባይም በመመላለስ ለሕዝቡ ዕውነትን ያስተምራቸዋል ከአብርሃም ልጅነት ልዩ ከሆኑ ወገኖች በቀር አሕዛብ ሁሉ ይታዘዙለታል ። ናሆም ነቢይም እንዲህ አለ ። እግዚአብሔር በእኔ አርአያ ይመጣል ልብሱም እንደልብሴ ነው።

ክፍል ፫[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ነቢዩ ኢዩኤልም እንዲህ ተናገረ የእግዚአብሔር ዙፋን የሆነች ብላቴና ድንግልን አየሁ እርሷም እንደ እሳት ያልባት ነበር ስለርሷም ይቺ ማን ናት ብዬ ኪሩብን ጠየቅሁት ከአዳም ልጆች የተመረጠች የእግዚአብሔር ዙፋን ይህች ድንግል ናት በርሷም የተጐሳቈሉ አሕዛብ ይድናሉ ለአመነባትም ረድኤትና መጠጊያ ናት ።

ዳዊትም በመዝሙሩ እንዲህ አለ እግዚአብሔር አንተ ልጄ ነህ ዛሬም በተዋሕዶ ወለድኩህ አለኝ ። ለምነኝ አሕዛብን ርስት አድርጌ እሰጥሃለሁ ግዛትህም በመላው ዓለም ነው ። ዳግመኛም አብ አለ ቀዳማዊ ወልድ በኃይል ቀን ካንተ ጋራ ሳለሁ ከአጥቢያ ኮከብ በፊት ከሆድ ወለድኩህ እንደ መልከጼዴቅ ሥርዓት አንተ የዓለሙ አገልጋይ ካህን ነህ ብሎ እግዚአብሔር ማለ ከማለም አይጸጸትም

ቤዛ ይስሐቅ በግዕ ከኅቱም ዕፀ ሳቤቅ እንደተገኘ ለእስራኤልም በበረሀ ውስጥ ከኅቱም አለት ውኃ እንደ ፈለቀ የደነቀች የአሮን በትርም እንደለመለመችና እንደ አፈራች ። በሶምሶንም እጅ ውስጥ ከአህያ መንጋጋ ዐጥንት ውኃ እንደ ፈሰሰ ።

እንዲሁ የጌታችን ልደት በኅቱም ድንግልና ሆነ ። በዕፀ ጳጦስ ውስጥ እሳት እንደ ነደደች ዕፂቱም እንዳልተቃጠለች እንዲሁ የመለኮቱ እሳት ድንግልን አላቃጠላትም ። ለርሱም ከቸር አባቱ ከማሕየዊ መንፈስ ቅዱስ ጋር ጌትነት ክብር ምስጋና ሰጊድ ከርሱ ጋር በትክክልነት ይገባል ለዘላለሙ አሜን ።