AK-47

AK-47 በይፋዊ አጠራሩ አቭቶማት ካላሽኒኮቫ 1947 (ክላሽንኮቭ ፤ ክላሽኒኮቭ ወይም ክላሽ ብቻ በመባልም ይታወቃል) 7.62×39 ሚሜ ጥይት የሚጠቀም ጠመንጃ ነው። ይህ መሣሪያ በቀድሞዋ ሶቪየት ኅብረት በሩሲያዊው ታዋቂ የጦር መሣሪያ ዲዛይነር ሚካሂል ካላሽኒኮቭ የተሠራ ሲሆን የካላሽኒኮቭ የጠመንጃ ቤተሰብ መሠረት ነው። ይህ ኤኬ-47 የተሰኘው ሞዴልና መሰል የጦር መሳሪያዎቹ ከተሠሩ ከሰባት አስርት ዓመታት በላይ ቢቆጠሩም፣ ዛሬም ድረስ በዓለም ላይ በስፋት ከሚታወቁና በብዛት ጥቅም ላይ ከዋሉ የጦር መሣሪያዎች ተርታ ይመደባሉ።
የሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት በጀርመን ኃይሎች ጥቅም ላይ የዋለው ስተርምገዌር 44 (Sturmgewehr 44) የተባለው ጠመንጃ በሶቪየት ወታደሮች ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ አሳድሯል። የጀርመኑ ጠመንጃ አዲስ የሆነ መካከለኛ መጠን (ካሊበር) ያለው ጥይት እንዲሁም እንደ መትረየስ እሩምታ ተኩስ የመተኮስ ችሎታን ያጣመረ ነበር። ሶቪየቶች በመሳሪያው ተደንቀው የራሳቸውን መካከለኛ ካሊበር ያለው አውቶማቲክ ጠመንጃ ለመሥራት አነሳሽነት ሆነ።
ውጤቱም ኤስ ኬ ኤስ በመባል የሚታወቀው ግማሽ አውቶማቲክ ጠመንጃ ነበር። SKS 7.62x39ሚሜ ጥይት ይጠቀማል።[2] ሆኖም ኤስ ኬ ኤስ በቂ አውቶማቲክ ስላልነበረ ብዙም ሳይቆይ ሶቪየቶች ይበልጥ ዘመናዊ የሆነውን ኤኬ-47 የተባለውን ጠመንጃ ሠሩ። ኤኬ-47 በፍጥነት ኤስ ኬ ኤስን በመተካት በሶቪየት ወታደሮች ዘንድ ተወዳጅነትን አገኘ። በኋላም በ1959 እ.ኤ.አ. AKM የተባለ ቀለል ያለ፣ በአረብ ብረት የታተመ የኤኬ-47 ሞዴል ተሰራ። ኤኬኤም ከኤኬ-47 ተከታታይ የጦር መሳሪያ ዘሮች በስፋት የሚገኘው ነው። በ1960ዎቹ ደግሞ አር ፒ ኬ (RPK) የተባለ ቀላል መትረየስ ተሰራ፤ ይኸውም የኤኬ-47 አይነት ሆኖ ይበልጥ ጠንካራ አፈሙዝ እና መቆሚያ ያለው ነበር።
ሚካሂል ካላሽኒኮቭ የጦር መሣሪያ ዲዛይነር በመሆን ሥራውን የጀመረው እ.ኤ.አ በ1941 ሲሆን፣ በዚያን ወቅት በብራያንስክ ጦርነት ወቅት ከደረሰበት የትከሻ ቁስል በማገገም ላይ ነበር። ራሱ ስለዚህ ጉዳይ ሲናገር እንዲህ ብሏል... "ሆስፒታል ውስጥ ነበርኩ፣ ከጎኔ ካለው አልጋ ላይ አንድ ወታደር 'ጀርመኖች አውቶማቲክ መሣሪያ ሲኖራቸው ወታደሮቻችን ሁለት እና ሦስት ሆነው አንድ ጠመንጃ ብቻ የሚይዙት ለምንድን ነው?' አለኝ። በዚህ ምክንያት እኔም እንደ አንድ ወታደር ለወታደሮች የሚሆን ማሽን ለመሥራት ተነሳሁ፤ ያም የካላሽኒኮቭ አውቶማቲክ መሣሪያ ሆነ። መሣሪያው ለመጀመሪያ ጊዜ የተሠራው በ1947 እ.ኤ.አ ነው።" [1]
ኤኬ-47 (AK-47) ቀደም ሲል የነበሩ የጠመንጃ ቴክኖሎጂ ፈጠራዎች ድብልቅ ተደርጎ ሊገለጽ ይችላል። "ካላሽኒኮቭ የአሜሪካን ኤም 1 ጋራንድን (M1 Garand) እና የጀርመኑን ኤስ ቲ ጂ 44ን (StG 44) ምርጥ ባህሪያትን በማጣመር አውቶማቲክ ጠመንጃ ለመንደፍ ወስኗል።"[1] የካላሽኒኮቭ ቡድን እነዚህን የጦር መሣሪያዎች የማግኘት ዕድል ነበራቸው፤ ስለዚህም ከዜሮ መጀመር አላስፈለጋቸውም። ካላሽኒኮቭ ራሱ እንዲህ ሲል ተናግሯል፤ "ብዙ የሩሲያ ጦር ወታደሮች አንድ ሰው እንዴት የጦር መሣሪያ ዲዛይነር መሆን እንደሚችል፣ እንዲሁም አዲስ የጦር መሣሪያ እንዴት እንደሚነደፍ ይጠይቁኛል። እነዚህ በጣም አስቸጋሪ ጥያቄዎች ናቸው። እያንዳንዱ ዲዛይነር የራሱ መንገድ፣ የራሱ ስኬቶችና ውድቀቶች ያሉት ይመስላል። ነገር ግን አንድ ነገር ግልጽ ነው፤ አዲስ ነገር ለመፍጠር ከመሞከርዎ በፊት በዚህ መስክ ውስጥ ያሉትን ነገሮች በሙሉ በጥሩ ሁኔታ መገንዘብ እጅግ አስፈላጊ ነው። እኔ ራሴ ይህ እውነት መሆኑን የሚያረጋግጡ ብዙ ተሞክሮዎች አሉኝ።"
አንዳንዶች ካላሽኒኮቭ እንደ ቡልኪን ቲኬቢ-415ን (TKB-415) ወይም እንደ ሲሞኖቭኤቪኤስ-31ን (AVS-31) ያሉ ንድፎችን ኮርጆ ነው ሲሉ ይከራከራሉ።

ኤኬ-47 (AK-47) በ1940ዎቹ መገባደጃ ላይ በሶቭየት ኅብረት በወቅቱ በነበረው እጅግ የላቀ የጅምላ አመራረት ዘዴ በመጠቀም በፍጥነትና በርካሽ ሊመረት የሚችል ቀላል፣ አስተማማኝና ሙሉ በሙሉ አውቶማቲክ ጠመንጃ ተደርጎ የተነደፈ ነው። ኤኬ-47 (AK-47) በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ከፍተኛ አስተማማኝነትን የሚያረጋግጥ ረጅም-ምት (long-stroke) ጋዝ ሲስተም ይጠቀማል። ትልቁ የጋዝ ፒስተን፣ በእንቅስቃሴ ላይ ባሉ ክፍሎች መካከል ያለው ሰፊ ክፍተት እና ሾጣጣ ቅርጽ ያለው የካርትሪጅ ዲዛይን መሳሪያው ሳይተኮስ ከፍተኛ መጠን ያላቸውን ቆሻሻዎች እንዲቋቋም ያስችለዋል።
ኤኬ (AK) ክላሽ 7.62×39ሚሜ ጥይትን በ715 ሜትር በሰከንድ ፍጥነት ይተኮሳል።

ለመተኮስ ተኳሹ ሙሉ መጋዘን ያስገባል፣ ከዚያም ማቀባበያውን ወደ ኋላ ጎትቶ ይለቀዋል፣ ቀጥሎም አነጣጥሮ ቃታውን ይጫናል። በከፊል-አውቶማቲክ ሁኔታ መሳሪያው አንድ ጊዜ ብቻ ይተኩሳል፤ ለቀጣዩ ጥይት ቃታው ተለቅቆ እንደገና መጫን ያስፈልጋል። ሙሉ-አውቶማቲክ (fully automatic) ሁኔታ ላይ መጋዘኑ እስኪያልቅ ወይም ከቃታው እስኪለቀቅ ድረስ ጠመንጃው አዲስ ጥይቶችን ወደ ክፍሉ እያስገባ በእሩምታ መተኮሱን ይቀጥላል።
ኤኬ-47 (AK-47) የሚሠራው በጥይት ቃጠሎ አማካኝነት በሚፈጠር ጋዝ ግፊት ነው። ቃታው ሲጫን፡-
- መዶሻው ወደ ፊት ይፈናጠራል፤ የመተኮሻውን መርፌም ይመታል።
- ይህም መተኮሻውን መርፌም የጥይቱን ፕሪመር ይመታል, ይህም ጥይቱ እንዲተኮስ ያደርገዋል። ጥይቱ ከተተኮሰ በኋላ ከፍተኛ መጠን ያለው ጋዝ ይፈጠራል።
- ይህ ጋዝ በአፈሙዙ አናት ላይ ወዳለው የጋዝ ሲሊንደር ይጓዛል።
- በጋዝ ሲሊንደሩ ውስጥ ጋዙ ፒስተን የሚባለውን ክፍል ወደ ኋላ ይገፋል። ፒስተኑ ከቦልት ተሸካሚው ጋር የተያያዘ ነው፤ ስለዚህ ፒስተኑ ወደ ኋላ ሲገፋ ቦልት ተሸካሚውንም አብሮ ይገፋዋል። ቦልት ተሸካሚው ወደ ኋላ ሲንቀሳቀስ የሚከተሉትን ተግባራት ያከናውናል፤
- የመጀመሪያውን ጥይት የተኮሰውን ቀለሃ ያስወጣል።
- በተመሳሳይ ጊዜ, የመመለሻ ስፕሪንግ በመባል የሚታወቀው ክፍል ተጨምቆ ለቀጣዩ ተግባር ኃይል ያከማቻል።
- መዶሻውን ወደ ኋላ በመሳብ ለቀጣዩ ተኩስ ያዘጋጃል።
- ቦልት ተሸካሚው የመመለሻ ስፕሪንግ በመጠቀም ወደ ፊት ሲመለስ አዲስ ጥይት ከመጋዘኑ ወደ ክፍሉ እንዲገባ ያደርጋል፣ መቀርቀሪያውን ይቆልፋል። አሁን መሳሪያው ለመተኮስ ዝግጁ ነው።


ኤኬ-47ን (AK-47) ለመተኮስ የሚውለው መቆጣጠሪያ በቀኝ በኩል የሚገኝ ትልቅ ዘንግ ሲሆን፣ ይህም ጠመንጃው አቧራ እንዳይገባበት የሚከላከል ከመሆኑም በላይ "ቁልፍ" (Safe) ላይ ሲሆን መሳሪያውን ለመጫን የሚያገለግለውን እጀታ (ማቀባበያውን) ሙሉ በሙሉ ወደ ኋላ እንዳንጎትተው ይከለክለናል። ይህ መቆጣጠሪያ በቀኝ እጃችን አመልካች ጣት የምንገለገልበት ሲሆን በሦስት ዓይነት ቦታዎች ላይ ይቆማል፤ እነዚህም "ቁልፍ" (ወደ ላይ)፣ "እሩምታ" (መሃል) እና "አንድ በአንድ/ ከፊል-አውቶ" (ወደ ታች) ናቸው። እንዲህ የተደረገበት ምክንያት ወታደሮች በተደናገጡ ጊዜ መቆጣጠሪያውን ወደ ታች አጥብቀው ስለሚገፉት "እሩምታ" የሚለውን አማራጭ ትተው በቀጥታ ወደ "አንድ በአንድ" በመቀየር ጥይት እንዳይባክንባቸው ነው። ጠመንጃውን ሆን ብለን "እሩምታ" ላይ ለማድረግ፤ አስበንበት መቆጣጠሪያውን በትክክል ወደ መሃል ማምጣት ያስፈልጋል። ይህንን መቆጣጠሪያ በቀኝ እጃቸው የሚጠቀሙ ሰዎች እጃቸውን ከመያዣው ላይ ለትንሽ ጊዜ ማንሳት ስለሚጠበቅባቸው በጣም ምቹ አይደለም። ለዚህ ችግር መፍትሄ ለመስጠት አንዳንድ የኤኬ (AK) አይነት ጠመንጃዎች ከጎን በኩል ሌላ መቆጣጠሪያ የተገጠመላቸው ሲሆን ይህም በተኳሹ ቀኝ አውራ ጣት የሚሠራ ነው። ይህ አዲሱ መቆጣጠሪያ ሦስት ቦታዎች ያሉት ሲሆን እነርሱም፡- "ቁልፍ" (ወደ ፊት)፣ "እሩምታ" (መሃል) እና "አንድ በአንድ" (ወደ ኋላ) ናቸው።

ኤኬ-47 (AK-47) ላይ የተገጠመው የብረት ማነጣጠሪያ ከ100 ሜትር ጀምሮ እስከ 800 ሜትር ርቀት ድረስ በ100 ሜትር ልዩነት የሚስተካከል ነው። ይህ ማነጣጠሪያ በ100 ሜትር ልዩነት ምልክት የተደረገበት ሲሆን ርቀቱን ለመለካት ያስችላል። የፊት ማነጣጠሪያው ከፍታውን ለማስተካከል የሚያስችል ሲሆን ይህ ማስተካከያ በውጊያ ላይም ቢሆን ሊከናወን ይችላል። ነገር ግን ጎንዮሹንለማስተካከል ልዩ መሣሪያ ያስፈልጋል፤ ይህ ማስተካከያ የሚደረገውም የጦር መሣሪያ ባለሙያዎች አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ብቻ ነው። የማነጣጠሪያው መስመር ከአፈሙዙ በግምት 4.85 ሴንቲሜትር ከፍ ብሎ የሚገኝ ሲሆን "П" ተብሎ የተጻፈበት ቦታ ለ300 ሜትር ርቀት የተስተካከለ ነው። ይህ ማለት አንድ ወታደር 300 ሜትር ርቀት ላይ ላለ ጠላት ኢላማውን ሲያነጣጥር በቀላሉ የጠመንጃውን ማነጣጠሪያ በጠላት ሰውነት መሃል ላይ (በቀበቶው አካባቢ) ማድረግ ብቻ ነው የሚያስፈልገው። በዚህ ርቀት ውስጥ የጠላት ርቀት ቢሳሳትም እንኳ በተነጣጠረው የሰውነት ክፍል ላይ ጥይቱ ስለሚመታ ስህተቱ ብዙም ጉዳት አያመጣም። አንዳንድ የኤኬ (AK) ዓይነት ጠመንጃዎች በጨለማ ውስጥ ለመዋጋት እንዲያግዝ የፊት ማነጣጠሪያው ላይ የሚገለባበጥና በ50 ሜትር ርቀት ላይ የተስተካከለ ብርሃን ያለው ምልክት ይኖራቸዋል።
ኤኬ-47 (AK-47) መጀመሪያ ላይ በጠጣ እንጨት በተሠሩ ሰደፍ የእጅ መያዣ እና የላይኛው ሙቀት መከላከያ ክፍሎች ነበር የሚመጣው። ዓይነት 3 ተቀባይ ከተዋወቀ በኋላ ሰደፉ፣ የታችኛው የእጅ መያዣ እና የላይኛው ሙቀት መከላከያው ከበርች እንጨት ጣውላዎች ተሠሩ። እነዚህ እንጨቶች ከአንድ ቁራጭ እንጨት ይልቅ ጠንካራ ከመሆናቸውም በላይ ቅርጻቸውን የመጠበቅ አቅማቸው የላቀ ነው፣ ብዙ ጊዜ መቆየትም አያስፈልጋቸውም፣ እንዲሁም ዋጋቸውም ያነሰ ነው። ኤኬኤስ (AKS) እና ኤኬኤምኤስ (AKMS) ሞዴሎች እንደ ጀርመናዊው ኤም ፒ 40 (MP40) ንዑስ ማሽን-ጠመንጃ ወደ ታች የሚታጠፍ የብረት ሰደፍ ነበራቸው ።

መደበኛ የመጋዘን አቅም 30 ጥይት ነው። ባለ 10፣ 20 እና 40 ሳጥን መጋዘን እንዲሁም ባለ 75-ዙር ጥምዝ መጋዘኖች አሉ።
የኤኬ-47 (AK-47) መደበኛ ባለ30 መጋዘኖች ጥይቶችን ወደ ክፍሉ በቀላሉ ለማስገባት የሚያስችል ጎልቶ የወጣ ኩርባ አላቸው። ከብረት የተሠሩት እነዚህ መጋዘኖች ከ"የጥይት መግቢያ ከንፈሮች" ጋር በአንድ ላይ (የጥይት መግቢያ ከንፈሮች ማለት ጥይቱ ወደ ክፍሉ የሚገባበትን አቅጣጫ የሚቆጣጠሩት የመጋዘኑ የላይኛው ክፍል ናቸው) እጅግ በጣም ጠንካራ ከመሆናቸው የተነሳ ጉዳት ለማድረስ እጅግ አስቸጋሪ ያደርጋቸዋል። እነዚህ መጋዘኖች በጣም ጠንካራ ከመሆናቸው የተነሳ "ወታደሮች መዶሻ በማድረግ አልፎ ተርፎም የጠርሙስ መክፈቻ በመጠቀምባቸው ይታወቃሉ።"[1][2] ይህ የኤኬ-47 (AK-47) መጋዘኖችን ይበልጥ አስተማማኝ እንዲሆኑ ከማድረጉም በላይ ከአሜሪካ እና ከኔቶ መጋዘኖች የበለጠ ክብደት እንዲኖራቸው አድርጓል።


ከጠመንጃው ጋር ከሚቀርቡት ተጨማሪ መሣሪያዎች መካከል 387 ሚሊ ሜትር (15.2 ኢንች) ርዝመት ያለው 6H3 ጩቤ (bayonet) ይገኝበታል፤ ይህ ጩቤ 200 ሚሊ ሜትር (7.9 ኢንች) ርዝመት ያለው ጦር የሚመስል ጫፍ ያለው ስለት (blade) አለው። ኤኬ-47 (AK-47) ጩቤን ለመግጠም የ17.7 ሚሊ ሜትር (0.70 ኢንች) የሆነውን የአፈሙዝ ቀለበትበአፈሙዙ ዙሪያ በማንሸራተት እጀታውን ከፊት ማነጣጠሪያው በታች ባለው ጩቤ ማያያዣ ላይ መቆለፍ ያስፈልጋል።
ኤኬ-47 (AK-47) እና ተያያዥ የጦር መሳሪያዎቹ በበርካታ አገራት ውስጥ የተመረቱ ሲሆን ጥራታቸውም እጅግ በጣም ጥሩ ከሚባሉት ጀምሮ እስከ አጠራጣሪ ጥራት ያላቸው ይገኙበታል። በዚህ ምክንያት ኤኬ-47 በአማካይ ከ6,000 እስከ 15,000 ጥይት እድሜ አለው። ኤኬ-47 ርካሽ፣ ቀላል እና ለማምረት ምቹ የሆነ ጠመንጃ እንዲሆን ተደርጎ የተሠራ ሲሆን ይህም የሶቪየት ኅብረት የጦር ኃይል መሣሪያዎችንና ቁሳቁሶችን እንደ ጊዜያዊ አድርጎ ከሚመለከትበት አስተምህሮ ጋር የሚስማማ ነው። የጦር ኃይሎቹ ብዙውን ጊዜ በቂ ድጋፍ ሳይደረግላቸው ስለሚሰማሩ እና ከአውድማ በሚያገኙት አቅርቦት ላይ ጥገኛ ስለሆኑ የጦር መሣሪያዎችን ከመጠገን ይልቅ መተካት የበለጠ ወጪ ቆጣቢ ይሆናል።

- ቀደምት አይነቶች (7.62×39 ሚሜ)
የ1948/49 እትም፡ ዓይነት 1፡ እጅግ በጣም ቀደምት ሞዴሎች ሲሆኑ የታተመ የብረት ሽፋን ተቀባይ- ያላቸው ናቸው፤ በአሁኑ ጊዜ እጅግ ብርቅ ናቸው። የ1951 እትም፡ ዓይነት 2፡ የተቀረጸ ተቀባይ አለው። በርሜሉና ክፍሉ ዝገትን ለመቋቋም በክሮሚየም ተለብጠዋል። የ1954/55 እትም፡ ዓይነት 3፡ የቀለለ፣ የተቀረጸ ተቀባይ ያለው ሞዴል ነው። የጠመንጃው ክብደት 3.47 ኪሎ ግራም (7.7 ፓውንድ) ነው።[7] ኤኬኤስ (AKS) (ኤኬኤስ-47)፡ ዓይነት 1፣ 2 ወይም 3 ተቀባዮች ያሉት ወደ ታች የሚታጠፍ የብረት ሰደፍ ነበረው።
- ዘመናዊ (7.62×39 ሚሜ)
- AKM : ቀላል፣ ቀላል የ AK-47 ስሪት; ዓይነት 4 ተቀባይ የሚሠራው ከተጨፈለቀ ብረት ነው።
- RPK : በእጅ የሚያዝ መትረየስ ስሪት ከረጅም አፈሙዝ እና እግር ጋር።
- የውጭ ስሪት (7.62×39 ሚሜ)
ኤኬ-47 (AK-47) እና ኤኬ-103 (AK-103) በተለይም ኤኬ-103 በኢትዮጵያ ውስጥ በመንግስት በሚተዳደረው የጋፋት የጦር መሳሪያ ምህንድስና ኮምፕሌክስ "ኢቲ-97/1" (Et-97/1) በሚል ስያሜ በአገር ውስጥ ይመረታል።
በዓለም ዙሪያ ኤኬ (AK) እና ተያያዥ የጦር መሣሪያዎቹ በመንግሥታት፣ በአብዮተኞች፣ በአሸባሪዎች፣ በወንጀለኞች እንዲሁም በሲቪሎች ዘንድ በስፋት ጥቅም ላይ ይውላሉ። በአንዳንድ አገሮች ለምሳሌ ሶማሊያ፣ ሩዋንዳ፣ ሞዛምቢክ፣ ኮንጎ እና ታንዛኒያ የኤኬ (AK) የጦር መሣሪያዎች በጥቁር ገበያ ከ30 እስከ 125 ዶላር ይሸጣሉ፤ በጅምላ ከሚጭበረበሩት ምርቶች የተነሳ ዋጋቸው ባለፉት አስርት ዓመታት ውስጥ ቀንሷል። [1] በኬንያ "አንድ ኤኬ-47 (AK-47) በገንዘብ ሲገዛ ከሚገኘው ዋጋ በግማሽ ያህል ያነሰ ዋጋ አምስት ራሶች ከብቶች (ወደ 10,000 ኬንያ ሺሊንግ ወይም 100 የአሜሪካ ዶላር ገደማ) ያስወጣል"። [2] በዓለም ዙሪያ የኤኬ (AK) ዓይነት የጦር መሣሪያዎችን "በ6 ዶላር ወይም በዶሮ ወይም በአንድ ከረጢት እህል መለወጥ የሚቻልባቸው ቦታዎች አሉ።" [3][4][5]


በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት ሶቭየት ኅብረትና ቻይና እንዲሁም አሜሪካና ሌሎች የኔቶ አገሮች በዓለም ዙሪያ ላሉ በርካታ አገሮችና አማፂ ኃይሎች የጦር መሳሪያና የቴክኒክ እውቀት ይሰጡ ነበር። በዚሁ ጊዜ ምዕራባውያን አገሮች እንደ ኤፍ ኤን ፋል (FN FAL)፣ ኤች ኬ ጂ 3 (HK G3)፣ ኤም 14 (M14) እና ኤም 16 (M16) ያሉ በአንጻራዊነት ውድ የሆኑ አውቶማቲክ ጠመንጃዎችን ይጠቀሙ ነበር። በሌላ በኩል ሩሲያውያንና ቻይናውያን ኤኬ-47ን (AK-47) ይጠቀሙ ነበር፤ አነስተኛ የምርት ወጪውና በቀላሉ የመሥራት ችሎታቸው ኤኬዎችን በብዛት እንዲያመርቱ አስችሏቸዋል።
በቀድሞው የኮሚኒስት መንግስታትን ይደግፉ በነበሩ አገሮች ኤኬ-47 (AK-47) የሶስተኛው ዓለም አብዮት መገለጫ ሆኖ ነበር የሚታየው። በካምቦዲያ የእርስ በርስ ጦርነት እንዲሁም በካምቦዲያና ቬትናም መካከል በተደረገው ጦርነት በስፋት ጥቅም ላይ ውሏል። በ1980ዎቹ ሶቭየት ኅብረት ምዕራባውያን ማዕቀብ በጣሉባቸው እንደ ሊቢያና ሶሪያ ላሉ አገሮች የጦር መሣሪያ ዋና አቅራቢ ነበረች፤ እነዚህ አገሮችም ከእስራኤል ጋር በሚያደርጉት ጦርነት የሶቭየት ኅብረትን ድጋፍ በደስታ ይቀበሉ ነበር። ሶቭየት ኅብረት ከፈረሰች በኋላ ግን ኤኬ-47 (AK-47) የጦር መሣሪያዎቹ በገንዘብ ለሚገዙ ሁሉ በጥቁር ገበያም ሆነ በግልጽ መሸጥ ጀመሩ፤ በዚህም የተነሳ የአደንዛዥ ዕፅ አዘዋዋሪዎችን፣ የአምባገነን መሪዎችን እንዲሁም እንደ አልቃይዳ፣ አይሲስና ታሊባን ያሉ አክራሪ እስላማዊ ቡድኖች፣ በኮሎምቢያ የሚገኙትን ፋርክንና ኤጀርሲቶ ደ ሊበራሲዮን ናሲዮናልን የመሳሰሉ የሽምቅ ተዋጊዎችን እጅ ውስጥ ለመግባት በቅተዋል። ዛሬ በአፍጋኒስታንና ኢራቅ ብቻ ሳይሆን በየቦታው ይገኛል።
በሩሲያ ውስጥ ክላሽ የብሔራዊ ኩራት ምንጭ ነው።
- ^ Fisk, Robert (22 April 2001). "For Patriotism and Profit: An interview with Mikhail Kalashnikov". The Independent (London, England). http://www.worldpress.org/cover5.htm.
- ^ The Illustrated Directory of 20th Century Guns. 2001.