Dessalew Berihun
- ከታሪክ_ማህደር
ሐምሌ ሃያ ሁለት (22) ቀን ሺህ ዘጠኝ መቶ ሃያ ስምንት (1928) ዓመተምህረት!! #ዝክረ_ታሪክ «እንደዚህ ነው ክህነት ዘመንን መቀደስ በደምና በአጥንት ጽኑ ሀገር ማውረስ» ከሰማኒያ ዘጠኝ (89) ዓመታት በፊት ልክ በዛሬዋ ዕለት ታሪክን የኋሊት!! ከሰማኒያ ዘጠኝ (89) ዓመታት በፊት ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ በእስር ላይ ሆነው የኢትዮጵያ ህዝቡ ለኢጣሊያ እንዲገዛ እንዲ ሰብኩ ተጠይቀው አይሆንም በማለታቸው እና እርሳቸው እንኳንስ ህዝቡ መሬቱን እንዳይገዛ በመግዘታቸው በቀድሞ የማስታወቂያ ሚኒስቴር አጥር ስር በፋሽስት ጣሊያን ጦር በመትረየስ ጥይት ተደብድበው የተሰውበት ዕለት ነበር። ➢ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ በኢጣልያኖች በአደባባይ ሲገደሉ ሒደቱና በዕለቱ የታዩት ክስተቶች ምን ይመስሉ ነበር? የጣልያንን ወረራ ለመከላከል በሺህ ዘጠኝ መቶ ሃያ ስምንት (1928) ዓመተምህረት አዋጅ በታወጀ ጊዜ በወቅቱ የምስራቅ ኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብጹዕ አቡነ ጴጥሮሥ ንጉሠ ነገሥቱን ተከትለው ወደ ማይጨው ዘመቱ። ሐምሌ ሃያ አንድ (21) ቀን ሺህ ዘጠኝ መቶ ሃያ ስምንት (1928) ዓመተምህረት የተባበሩት የአርበኞች ግምባር አዲስ አበባ ላይ የሠፈረውን የጠላት ጦር ለመዋጋት በአደረገው ቀጠሮ መሠረት አቡነ ጴጥሮሥ በነደጃዝማች አበራ ካሣ ይመራ ከነበረው የሠላሌ ጦር አብረው ወደ አአዲስ አበባ ገቡ። ይህ ጦር ግን የሚፈለገው ውጤት አለመምጣቱን በመገንዘብ ወደመጣበት ሲያፈገፍግ አቡነ ጴጥሮሥ የአዲስ አበባን ህዝብ ሠብከው በጠላት ላይ ለማሥነሣት በማሠብ ከጦሩ ተለይተው አዲስ አበባ ቀሩ። ብዙም ሣይቆዩ አንድ ቀን ብቻ እንደቆዩ የጦር አለቆች ፊት ቀረቡ። ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ከተያዙበት ጊዜ ጀምሮ በጠላት ጥይት እስከ ተገደሉበት ጊዜ ድረስ የነበረውን ሂደት ኮርየር ዴ ላሴራ (corriere della sera) የተባለው የጋዤጣ ወኪል እና የምስራቅ አፍሪካ ዜና መዋዕል አዘጋጅ የነበረው ፖጃሌ የተባለ ጋዜጠኛ እንደ አውሮፓውያን የዘመን ቀመር በወረሃ ሰኔ አስራ አምሰት (15) ቀን ሺህ ዘጠኝ መቶ ሰላሳ ስድስት (1936) ዓመተምህረት አዲስ አበባ በነበረ ጊዜ ሂደቱን ባየው እና በተመለከተው መንገድ እንደሚከተለው ፅፎ ነበር።...... ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ቁመታቸው ረዘም ፊታቸውም ዘለግ ያለ እና መልካቸው ጠየም ያለ ዐዋቂነታቸው እና ትሕትናቸው ከገጻቸው የሚነበብ ሲሆን በዚህ ጊዜ ለብሰውት የነበረው ልብሰ ጵጵስና ጥቁር ካባ ያውም በጭቃ የተበከለ ነበር፡፡ በዚህ ሁኔታ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ወደ ችሎት ቀረቡ፡፡ ለፍርድም የተሠየሙት ዳኞች ሦስት ሲሆኑ እነዚህም ጣሊያኖችና የጦር ሹማምንት ናቸው፡፡ የመካከለኛው ዳኛ ኮሎኔል ነበር፡፡ የቀረበባቸውም ወንጀል «ሕዝብ ቀስቅሰዋል፣ ራስዎም አምፀዋል፣ ሌሎችንም እንዲያምፁ አድርገዋል» የሚል ነበር፡፡ ዳኛውም «ካህናቱም ሆኑ የቤተክህነት ባለሥልጣኖች ሊቀጳጳሱ አቡነ ቂርሎስም የኢጣሊያንን መንግሥት ገዢነት አምነው አሜን ብለው ሲቀበሉ እርስዎ ለምን አመፁ፣ ለምን ብቻዎን አፈንጋጭ ሆኑ?» ሲል ጠየቃቸው፡፡............. ... ➢ አቡነ ጴጥሮስም የሚከተለውን መለሱ፡፡ «.....አቡነ ቄርሎስ ግብፃዊ ናቸው፣ ስለኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን የሚገዳቸው ነገር የለም፡፡ እኔ ግን ኢትዮጵያዊ ነኝ። ሐላፊነትም ያለብኝ የቤተክርስቲያን አባት ነኝ። ስለዚህ ስለሀገሬና ስለ ቤተ ክርስቲያኔ እቆረቆራለሁ፡፡ ከዚህ በቀር ለእናንተ ችሎት የማቀርበው ነገር የለኝም፡፡ ለፈጣረዬ ብቻ የምናገረውን እናገራለሁ፡፡ እኔን ለመግደል እንደወሰናችሁ አውቃለሁ፡፡ ስለዚህ በእኔ ላይ የፈለጋችሁትን አድርጉ፡፡ ግን ተከታዮቼን አትንኩ»... አሉ፡፡ ይህንንም ብለው በጥይት ተደብድበው ሲገደሉ እንዲያይ ተጋብዞ ለተሰበሰበው ሕዝብ የሚከተለውን ሕያው መልእከት አስተላለፉ፡፡ «አረመኔያዊ የሆነው የፋሺስት መንግሥት ቤተክርስቲያንን ለማቃጠል፣ ሕዝበ ክርስቲያንን ለመግደል፣ ሃይማኖትን ለማጥፋት፣ ታሪካችንን ለማበላሸት የመጣ ነው። እንጂ በጎ ለመሥራት፣ እወነተኛ ፍርድ ለመስጠት ስላልመጣ ለዚህ ለግፈኛ አትገዙ። ስለ ውድ ሀገራችሁ፣ ስለቀናች ሃይማኖታችሁ ተከላከለ። ነፃነታችሁን ከሚያረክስ ሙታቹህ ስማችሁ ሲቀደስ ታላቅ ዋጋ ያለው ክብር ታገኛላችሁ። የኢትዮጵያ ህዝብ ለዚህ ለጠላት እንዳይገዛ አውግዣለሁ፤ የኢትዮጵያ መሬት ጠላትን ብትቀበል የተረገመች ትሁን። በፈጣሪ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተገዘተች ትሁን።» እኚህ ጳጳስ ሐቀኛ ነበሩ። ነገር ግን ለኢጣሊያ ለጋስዮን ታዝዞ የመጣው አስተርጓሚ ዳኞች የሚሉትን ብቻ ከማስተርጎም በቀር ጳጳሱ የሚናገሩትን ሐቀኛ ንግግር አላስተረጎመም፡፡ እኔ እንኳን የሰማሁት በአዲስ አበበ ለሠላሳ ዓመት የኖረው የእቴጌ ሆቴል ሐላፊ የነበረው የግሪክ ዜጋ ማንድራኮስ አጠገቤ ተቀምጦ ስለ ነበር የተናገሩትን ሁሉ ስለገለጠልኝ ነው፡፡ እኔ እንደ ሰማሁት ፍርዱን ለመስማት በብዛት የተስበስቡት ጣሊያኖችና ታዝዞ የወጣው የአዲስ አበበ ሕዝብ ሐቀኛ የሆነውን ንግግራቸውን ቢሰማ ኖሮ ልባቸው ይነካ ነበር። ሆኖም አስተርጓሚው በጳጳሱ ላይ ተጽዕኖ ስላሳደረበቸው እውነተኛ ንግግራቸው ሳይገለጥ ቀረ። ቀጥሎም ብፁእነታቸው በፍርድ ችሎት ላይ እንዳሉ ሕዝቡ ሁሉ ስለእርሳቸው እያዘነ ሳለ መስቀላቸውን አውጥተው እየጸለዩ ሕዝቡን ባረኩ። ወዲያው የሞታቸው ፍርድ ሲሰማ ሕዝቡ በኢጣልያ የእጅ ሰላምታ ዓይነት እጁን እንዲያነሣ ታዘዘ። በዚያን ጊዜ አቡነ ጴጥሮስ የሞታቸው ሰዓት መድረሱን አውቀው ሰዓታቸውን ከኪሳቸው አውጥተው ተመለከቱ። በዚህ ጊዜ ሁሉ ምንም ፍርሃት አይታይባቸውም ነበር። የሞታቸውን ፍርድ ያነብ የነበረው ኢጣሊያዊ ዳኛ ግን ይንቀጠቀጥ ነበር፡፡ ታላቅ ፍርሃትም በፊቱ ላይ ይታይ ነበር። ይሙት በቃ የተፈረደባቸው ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ በችሎት ፊት ለብዙ ሰዓታት ቆመው ስለዋሉና ደከሞአቸው ስለነበር ለመቀመጥ ፈልገው ዳኛውን በትሕትናና በፈገግታ ጠየቁት፡፡ እንዲቀመጡም ፈቀደላቸው፡፡ በመጨረሻም የሞታቸው ፍርድ ከተነበበ በኋላ የፈረዱባቸውን ዳኞች ፀልየው በመስቀላቸው ባረኩዋቸው፡፡ ብፁዕነታቸው እስከ መቃብር አፋፍ ድረስ የፍርሃት እና የድንጋጤ ምልክት ያይደለ ከልብ የሆነ ፍጹም ቆራጥነት ይታይባቸው ነበር፡፡ የሀገራቸው በጠላት መወረር የሕዝባቸውን መገደል እና መታስር የቤተክርስቲያናቸው መደፈር እስከ ሞት ያደረሳቸው እኚህ እውነተኛ ጳጳስ ለመገደል ሊወሰዱ ጥይት አልፎ ሌላ ስው እንዳይጎዳ ግንብ ይፈለግ ጀመር፡፡ ሩቅ ባለመሔድ ከመካነ ፍትሑ አስር (10) ሜትር ርቆ ግንብ ያለው መግደያ ቦታ ተገኘና ወደዚያ ተወስዱ። ከገዳዮቹም አንዱ «ፊትዎን ለመሸፈን ይፈልጋሉ?» ሲል ጠየቃቸው፡፡ «ይህ የአንተ ሥራ ነው» ሲሉ ብፁዕነታቸው መለሱ፡፡ ከመግደያውም ቦታ እንደ ደረሱ ወንበር ቀረበላቸውና ፊታቸውን ወደ ግንቡ ጀርባቸውን ወደ ሕዝቡ አድርገው እንዲቀመጡ ሆኑ፡፡ ከዚያ በኋላ ስምንት ወታደሮች በስተጀርባቸው ሃያ ርምጃ ርቀው ተንበርክከው በተጠንቀቅ ቆሙ፡፡ ወዲያው አዛዡ «ተኩስ» በማለት ትእዛዝ ሲስጥ ስምንቱም ተኩስው መቱዋቸው፡፡ ግን በስምንት ጥይት ሳይሞቱ ቀሩ። መሞታቸውንና አላመሞታቸውን ለማረጋገጥ ዶክተር ተጠራ። ዶክተሩም እንዳልሞቱ አረጋገጠ።
ከዚያም ሌላ ወታደር በሦስት የሽጉጥ ጥይት ራስ ቅላቸውን መትቶ ገደላቸው፡፡ የብፁዕነታቸው አሰክሬን ማንም እንዳይወስደው በአስቸኳይ ከአዲስ አበባ ውጭ ማንም በማያውቀው ቦታ በምሥጢር አንዲቀበር ተደረገ። በዚያች ሌሊት በአዲስ አበባ ውስጥ በየቤቱ ለቅሶና ዋይታ ሆነ በተጨማሪም ደራሲ እና ጋዜጠኛ ጳውሎስ ኞኞ «አቡነ ጴጥሮስ እንዴት ሞቱ» ሲል ሙሴ ፓይላክን ጠይቆአቸው እርስቸውም የሚክተለውን ተናግረዋል። አቡነ ጴጥሮስ ሲገደሉ እዚያው ነበርኩ። መጀመሪያ በእጃቸው ይዘውት የነበረውን መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ተሳለሙት። ቀጥለውም በያዙት መስቀል አማትበው ሕዝቡን ባረኩ፡፡ የኪሳቸውንም ሰዓት አውጥተው ካዩ በኋላ መልሰው ከኪሳቸው ከተቱት። ወዲያው ወታደሮች በሩምታ ተኩስው ገደሉዋቸው፡፡ ይህ እንደሆነ አስገድዶ ኮሎኔል ተመልካቹን ሕዝብ አጨብጭቡ ብሎ አዘዘና ተጨበጨበ። ማታ ከአስገዳዩ ኮለኔል ጋር ተገናኝተን ስንጫወት «በዚህ ቄስ መገደል እኮ ሕዝቡ ተደሰቷል» አለኝ «እንዴት?» ብለው «አላየህም ሲያጨበጭብ» አለኝ። እኔም «ባታውቀው ነው እንጂ የሕዝቡ ባህል ሲናደድም ያጨበጭባል» አልኩት። «እንዴት?» ቢለኝ እጄን እያጨበጨብኩ አሳየሁት። እሱም አሳየኝ። ከዚህ በኋላ «የሆነው ቢሆን እኔ ትልቅ ማስታወሻ አግኝቼአለሁ» ብሎ አቡነ ጴጥሮስ ሲገደሉ ይዘውት የነበረውን መስቀል እና መጽሐፍ ቅዱስ የኪስ ሰዓታቸውን ጭምር አሳየኝ። መጽሐፍ ቅዱሱ መሐል ለመሐል በጥይት ተሰንጥቋል። መስቀሉም ልክ በመሐከሉ ላይ ጥይት በስቶት ወጥቷል። የኪስ ሰዓታቸውንም እንዳየሁት፡ እንደዚሁ ጥይት በስቶታል። ጠላት ድል ተደርጎ ኢትዮጵያ ነፃነቷን ካገኘች በኋላ የብፁዕነታቸውን አኩሪ ታሪክ ትውልድ ሲዘክርላቸው እንዲኖር መታሰቢያ ይሆናቸው ዘንድ በግርማዊ ቀዳማዊ ንጉሠ ነገሥት አሳቢነት ሐምሌ አስራ ስድስት (16) ቀን ሺህ ዘጠኝ መቶ ሰላሳ ስምንት (1938) ዓመተምህረት በአዲስ አበባ ከተማ ሐውልት ቆሞላቸዋል። «ሂያጅ ተሳፋሪ፣ ሰዎች ከሆናችሁ ኧረ ለመቼው ቀን፣ ቤት ትሠራላችሁ መልሱን ስጡት እንጂ፣ ለምን ዝም አላችሁ ተጣርቶ ተጣርቶ፣ ያ ሰው ሄደላችሁ።» #የኋላው_ከሌለ_የለም_ የፊቱ #ይህ_የኛ_ የኢትዮጵያውያን_ ታሪክ_ነው