Sahabah story(ሶሀባ)

ከውክፔዲያ

السلام عليكم ورحمه الله وبركاته وبعد

እናታችን አዒሻ (ረ.ዐ)

“በኢስላም የመጀመሪያው የፍቅር መግለጫ ነብዩ ለአዒሻ የነበራቸው ፍቅር ነው።” ከሥረ መሠረቱ ኢስላምን ከንጹህ ምንጭና ከትክክለኛው አካባቢ የመረዳት ምሳሌ ናት። ከመምህራኖቹ ሁሉ ምርጡ መምህር (ከነብዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ)) እንደመማሯም አንድ ሙስሊም ሊደርስበት የሚያስበው የፅድቅ ደረጃ የደረሰች አርአያ ሴት ነች። በመሠረቱ የአዒሻ ምሳሌነት ዘርፈ ብዙ ነው። ከግል ሕይወት እስከ ሕዝባዊ፣ ከቤት ውስጥ ኑሮ እስከ ምሁራዊ ጉዞ፣ ወዘተ። ከነዚህ የአርኣያነት ምሳሌነቶች ውስጥ ወሳኝ ድርሻ ያለው ደግሞ የምዕመናን እናትነቷ ነው። በቁርኣን የተገለጸውን ምርጥ ኢስላማዊ ምግባር በማሟላትም ምሥጉን ስብእና ነበራት። ቸርነት፣ ቅንነት፣ ታማኝነትና እውነትንና ፍትህን መፈለግ የአዒሻ ዋነኛ መገለጫዎች ነበሩ።

አዒሻ እንደተማሪ ከጎበዝ ወጣትነት በተጨማሪ በጠያቂና ተመራማሪ ጭንቅላት ወደ ስኬታማና የተከበረ አዋቂ፣ መምህርና ዳኛ ሆና፤ በተፍሲር፣ በፊቅሂ፣ በሐዲስ፣ በታሪክና በዐረብኛ ቋንቋ ዘርፎች ከፍተኛ ደረጃ ከመድረሷም በላይ በምትሰጣቸው ደፋር፣ ቀጥተኛና የበሰሉ ምሁራዊ ትንተናዎች ትታወቃለች። የአዒሻ ለምታምንበት ነገር ሁሉ ደፋር፣ ግልጽና ቀጥተኛ መሆንን ከፍተኛነት፤ በአሁኑ ሰዓት በሙስሊሙ ዘንድ እንኳ ሴት ልጅ በጾታዋ ምክንያት ብቻ ከማህበረሰቡ የእለት ተዕለት ሕይወት የተገለሉትን ሙስሊም ሴቶች በማየት እንኳ ማረጋገጥ ይቻላል።

አዒሻ ከማንም በበለጠ ኹኔታ በነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) የእለት ተዕለት ሕይወት የነበራት ቦታ እንዲሁም የአስተሳሰብና የባሕሪይ ነጻነቷ በዘመኗ ከነበሩ ታላላቅ ስብዕናዎች ሁሉ የበለጠ ትኩረት እንድትስብ አድርጓታል።

የአዒሻ የኋላ ታሪክ (Background)

አዒሻ ሙሉ ስሟ፤ አዒሻ ቢንት አቡበከር አስ-ሲዲቅ ቢሆንም አዒሻ ቢንት ሲዲቅ በመባል በብዛት ትታወቃለች። ይበልጥ የምትታወቀው ግን አስ-ሲዲቃ ቢንት አስ-ሲዲቅ (እውነተኛዋ የእውነተኛው ልጅ) በሚለው ነው። ነብዩም የእህቷን ልጅ አብዳላህ ኢብኑ ዙበይርን እጅግ በመንከባከቧ ምክንያት (ኡሙ አብደላህ) የአብደላህ እናት በሚል ቅጽል ሥም ይጠሯት ነበር። ሁለቱም ወላጆቿ ኢስላምን ገና በጠዋቱ የተቀበሉ በመሆናቸው አስተዳደጓ በንጹህ ኢስላማዊ ከባቢ (environment) ውስጥ ነበር ማለት ይቻላል። እሷም ስትናገር “ገና ከጨቅላነቴ አንስቶ ወላጆቼ ኢስላምን ሲተገብሩ ለማየት ታድያለሁ” ትል ነበር። ገና ከጠዋቱ ስታስተውለው የኖረችው ኢስላማዊ አኗኗር በኋላ ላዳበረችው የአዕምሮ ንቃትና ሠብዕና ከፍተኛውን ሚና ተጫውቷል። ከልጅነቷ አንስቶ በኢስላም ላይ ከፍተኛ እምነት ስታሳድር ለእውነት መስዋዕት መሆንን ደግሞ አስተምሯታል። በተመሳሳይ ኹኔታም ክህደትና መሃይምነትን ትጠላለች።

የምዕመናን እናት አዒሻ ከነብዩ ባለቤቶች መካከል ብቸኛዋ ልጃገረድ ናት። የሁለቱ ትዳር የተፈጸመው በአላህ ትዕዛዝ ነበር። አዒሻም ስታገባ በወቅቱ በነበሩት በዐረቦች፣ በእብራውያንና በሌሎች ሕዝቦች ባህል እንደተለመደው ትንሽ እድሜ ነበራት። ይህንን የዕድሜ ሁኔታ አሁን ከ1400 ዓመታት በኋላ ባለው ባህልና ዝንባሌ ለመገምገም መሞከርም ስህተት ነው። የነብዩ የትዳር ሁኔታ ከሳቸው ተልዕኮ ተለይቶ ሊታይ አይችልም። ተልዕኮዋቸውም የዐረቦችን አንድነት መፍጠርና እውቀትና ጥበባቸውን ለሠው ዘር ማስተላለፍ ናቸው። ካለፉትም ከአሁኖችም ምሁራን አስተያየት ማረጋገጥ እንደሚቻለው አዒሻ (ረ.ዐ) በአስተዳደጓም ሆነ በተፈጥሮዋ ምርጥ የተባለችው ምርጫ ነች። ይህንን ተግባርም በወሳኝ እድሜዋ ከነብዩ ጎን በመኖር እየኖረችው በብቃት ፈጽማዋለች።

አዒሻ ለነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) በነበራት ፍቅርና እርሳቸውን የግሏ ብቻ ለማድረግ ባላት ጽኑ ፍላጎት ምክንያት በሌሎቹ ሚስቶቻቸው ላይ ትቀና ነበር። ነብዩም ይህን ፍቅሯን ተመሳሳይ መጠን ያለውን ፍቅር በመስጠት መልሰውላታል። የሳቸው ፍቅር ለሰሃቦችም ምሳሌ ነበር። አነስ (ረ.ዐ) እንደዘገቡትም፤

“በኢስላም የመጀመሪያው የፍቅር መግለጫ ነብዩ ለአዒሻ የነበራቸው ፍቅር ነው።” ነብዩ ለሷ የነበራቸው ፍቅር ከአካላዊ ውበቷ ጋር የተሳሳረም አይደለም። ይልቅስ፤ አዒሻ ከተሰጣት አምላካዊ ተልዕኮና የነብያዊ ተግባሩን ቀጣይነት ከማረጋገጥ ጋር የተቆራኘ ነው። የዚህ የማይታለፍ ሚና ማሳያ ነብዩ (ሶ.ዐ.ወ) ከሌሎች ሚስቶቻቸው ጋር የማይገጥማቸው ወህይ ከኢዒሻ ጋር ከተቀመጡባቸው ወቅቶች ሲሆኑ ጅብሪልን አይተዋል። ይህ ደግሞ በነብዩ (ሶ.ዐ.ወ) እንደተነገረው የሠማያዊው ክብር ሥጦታ መገለጫ ነው።

አዒሻ (ረ.ዐ) የገጠሟትን ፈተናዎች፣ የነበራትን እጅ የመስጠት (የኢስቲስላም) አመለካከት ምክንያት በማድረግ የወረዱትን የቁርኣን አንቀፆች በመመልከት “የአላህ እዝነት መፍሰሻ” ትባላለች። ምክንያቱም፤ እነዚህ አንቀፆች ከሷም በኋላ ላለው ትውልድ ሁሉ የሚያገለግል ነው። አንዳንድ ሶሃባዎች የአዒሻን የአላህ እዝነት መገለጫነት ለመግለጽ ከሚጠቀሙት ነገሮች አንዱ የተየሙም ድንጋጌ በአዒሻ ምክንያት መውረዱን ነው። ከዚህም አልፎ አላህ (ሱ.ወ) ይህች እናታችን ስሟ በመናፍቃን በሐሰት በመወሳቱ ምክንያቱ በሱረቱ አን-ኑር ምዕራፍ 24 በተለይም አንቀጽ 23 እና 26 ላይ ክብሯን በመመለስ አንቀጹን ያነበበ ሁሉ ትምህርት እንዲሆነው አድርጓል።

ﺇِﻥَّ ﺍﻟْﻤُﺴْﻠِﻤِﻴﻦَ ﻭَﺍﻟْﻤُﺴْﻠِﻤَﺎﺕِ ﻭَﺍﻟْﻤُﺆْﻣِﻨِﻴﻦَ ﻭَﺍﻟْﻤُﺆْﻣِﻨَﺎﺕِ ﻭَﺍﻟْﻘَﺎﻧِﺘِﻴﻦَ ﻭَﺍﻟْﻘَﺎﻧِﺘَﺎﺕِ ﻭَﺍﻟﺼَّﺎﺩِﻗِﻴﻦَ ﻭَﺍﻟﺼَّﺎﺩِﻗَﺎﺕِ ﻭَﺍﻟﺼَّﺎﺑِﺮِﻳﻦَ ﻭَﺍﻟﺼَّﺎﺑِﺮَﺍﺕِ ﻭَﺍﻟْﺨَﺎﺷِﻌِﻴﻦَ ﻭَﺍﻟْﺨَﺎﺷِﻌَﺎﺕِ ﻭَﺍﻟْﻤُﺘَﺼَﺪِّﻗِﻴﻦَ ﻭَﺍﻟْﻤُﺘَﺼَﺪِّﻗَﺎﺕِ ﻭَﺍﻟﺼَّﺎﺋِﻤِﻴﻦَ ﻭَﺍﻟﺼَّﺎﺋِﻤَﺎﺕِ ﻭَﺍﻟْﺤَﺎﻓِﻈِﻴﻦَ ﻓُﺮُﻭﺟَﻬُﻢْ ﻭَﺍﻟْﺤَﺎﻓِﻈَﺎﺕِ ﻭَﺍﻟﺬَّﺍﻛِﺮِﻳﻦَ ﺍﻟﻠَّﻪَ ﻛَﺜِﻴﺮًﺍ ﻭَﺍﻟﺬَّﺍﻛِﺮَﺍﺕِ ﺃَﻋَﺪَّ ﺍﻟﻠَّﻪُ ﻟَﻬُﻢ ﻣَّﻐْﻔِﺮَﺓً ﻭَﺃَﺟْﺮًﺍ

ﻋَﻈِﻴﻤًﺎ 

“ሙስሊሞች ወንዶችና ሙስሊሞች ሴቶች፣ ምእምናንና ምእምናትም፣ ታዛዦች ወንዶችና ታዛዦች ሴቶችም፣ እውነተኞች ወንዶችና እውነተኞች ሴቶችም፣ ታጋሾች ወንዶችና ታጋሾች ሴቶችም፣ አላህን ፈሪዎች ወንዶችና አላህን ፈሪዎች ሴቶችም፣ መጽዋቾች ወንዶችና መጽዋቾች ሴቶችም፣ ጿሚዎች ወንዶችና ጿሚዎች ሴቶችም፣ (ካልተፈቀደ ሥራ) ብልቶቻቸውን ጠባቂዎች ወንዶችና ጠባቂ ሴቶችም፣ አላህን በብዙ አውሺዎች ወንዶችና አውሺዎች ሴቶችም፣ አላህ ለእነርሱ ምሕረትንና ታላቅን ምንዳ አዘጋጅቶላቸዋል።” (አል-አህዛብ 33፤ 35)

የአዒሻ ኃይማኖተኛነትና ዙሕድ ከተከበረ፣ ሃብታም፣ ዝነኛና ከፍ ካለ ቤተሠብ ብትወለድም ከሃብታሙ አቡበከር (ረ.ዐ) ተወልዳ በምቾት ብታድግም፤ ከነብዩ (ሶ.ዐ.ወ) ጋር ችግርን በትዕግስት አሳልፋለች፤ ሕይወትን በዙህድ (ቀለል ያለና የምድራዊውን ዓለም ሕይወት የናቀ የአኗኗር ዘይቤ) መርታለች ቀለል ባለ ኑሮ ኑራለች። አላህም ለሁሉም የነብዩ ሚስቶች አላህን፣ መልዕክተኛውን እና የመጨረሻውን ዓለም በመምረጥ ከነብዩ ጋር የችግር ህይወት መምራትና ምድራዊ ደስታን በመምረጥ መካከል ምርጫ አስቀመጠላቸው። እነሱም የመጀመሪያውን መረጡ።

አዒሻም ቀለል ያለ የዙህድ (ምድራዊውን ሕይወት የናቀ) ሕይወት በመምረጧ ምክንያት ጥቂት እየተመገበች፣ ጥቂት እየጠጣች፣ የተጣጠፈ እየለበሠች ካላትም ትንሽ ላይ እየለገሠች ለመኖር ተገደደች። እዚህ ጋር ሳይጠቀስ የማያልፈው ነገር የአዒሻ አለጋገስ ነብዩ (ሶ.ዐ.ወ) እንዳሉት ቀኟ ሲለግስ ግራዋ አያውቅባትም። ተምሳሌታዊ ለጋስነቷ አንዳንድ ጊዜ የራሷን አንገብጋቢ ፍላጎቶች እስከመርሳት ያደርሳል። ይህ ሁኔታዋ አላህ በቁርኣን “የራሳቸው አንገብጋቢ ፍላጎት ቢኖርባቸውም እንኳ ሌሎችን ከራሳቸው ያስበልጣሉ” እንዳለው ነው። ከአዒሻ ተማሪዎች መካከል የነበረው ታላቁ የኢስላም ምሁር ዑርዋ ኢብን ዙበይር አዒሻ በየቦታው የተጣጣፈ ልብስ ለብሳ ሰባ ሺህ ዲርሃም ለምስኪኖች ስትሰጥ ማየቱን ተናግሯል።

እናታችን ምንም እንኳ እድሜዋ ለጋ ቢሆንም ለአላህ ካላት መተናነስና ለነብዩ (ሶ.ዐ.ወ) ካላት ክብርና ለተልዕኮዋቸው ካላት ጽኑ እምነት የተነሳ ነበር ቀለል ያለ ሕይወትን ለመኖር የመረጠችው። ይህ ምርጫዋ ደግሞ ብዙ የሕይወት ስንክሳሮችን እንድትጋፈጥ አድርጓታል። ከነብዩ (ሶ.ዐ.ወ) ኅልፈት በኋላም አዒሻ በዙህድ መኖር፣ መጾም መጸለይ እና ለወላጅ አጦች እንዲሁም ለድሆች መርዳቷ ቀጥላለች።

እውቀቷና ብልህነቷ፣የአዒሻ የአዕምሮ ብስለትና ፍጥነት ለጥቂቶች ብቻ የተሠጠ የሚባል ዓይነት ነበር። ከመምህራኖች ሁሉ ምርጡ መምህር ዘንድ የምትማር የኃይማኖት ተማሪ ብትሆንም እንዲሁ የተሠጣትን ብቻ ተቀብላ የምትነፍስ አልነበረችም። ይልቅ፤ ተመራማሪ ጭንቅላትና ጠያቂ አዕምሮ ነበራት። መታወቂያዋም ይኀው ነው። ነብዩ እየመለሱ እሷ ግን መላልሳ እየጠየቀች የምትታይባቸው ብዙ አጋጣሚዎችም ነበሩ።

ለአብነት ያህልም፡- በአንድ አስፈሪ ሌሊት እርሳቸው ለሞቱ ሶሃባዎች ዱዓእ ሊያደርጉ በወጡበት ሳያውቁ እርሷ ግን ተከትላቸው መምጣቷን ሲያስተውሉ “ለምን በዚህ አስፈሪ ጨለማ ተከተልሽኝ? ጂኒሽ ጎብኝቶሽ እንዴ?” አዒሻ ግን ይህን አጋጣሚ እንኳ ጥያቄ ለመጠየቅ ተጠቀመችበት። ምን አለች? “ሁሉም ሰው የሚከታተለው ጂን አለ እንዴ?” ነብዩም (ሰ.ዐ.ወ) “አዎ እኔን ጨምሮ ጂን ይከታተለናል። ነገር ግን የኔውን አላህ አስልሞታል (በክፉ አያዘኝም)” አሏት። ሌላም የአዒሻን ጠያቂ ባህሪ የሚያሳይ ምሳሌ ማሳየት ይቻላል። ነብዩ ስለ ዕለተ ትንሳዔ ሲናገሩ ሁላችንም ራቁታችንን ያልተገረዝን ሆነን እንደምንቀሰቀስ ሲገልጹ አዒሻ (ረ.ዐ) እንደተለመደው “ታዲያ ሁሉም እርቃኑን ሆኖ ሲነሳ አንዱ የአንዱን ኃፍረተ-ገላ ሊያይ ነው?” ስትል ጠየቀች። ነብዩም “አዒሻ ሆይ! የእለቱ ችግር አንዱ የአንዱን ኃፍረት ለማየት የሚያስችለው አይደለም” ሲሉ መለሱላት።

ለከፍተኛው ብልሃቷ ምስጋና ይግባውና አዒሻ ኢ-ምክንያታዊ ለሆኑና ከቁርኣን አስተምህሮ ጋር የሚጋጩ “ኃይማኖታዊ” ተግባራትን ታግሳ የምታልፍበት ልብ አልነበራትም። እሷ በምንም ሁኔታ የቁርኣን አስተምህሮ ከምክንያታዊነት ጋር አይጋጭም የሚል ጽኑ እምነት ነበራት። እንዴት ሆኖስ ይጋጫል አላህ ራሱ “በቁርኣኑ ውስጥ ምንም መጋጨትን አታገኙም” እያለ? በዚህ እይታዋ ምክንያት የአብደላህ ኢብኑ ዑመርን “አንድ ሠው ሲሞት ቤተሰቦቹ በሚያለቅሱት መረን የለቀቀ ለቅሶ ምክንያት ይቀጣል” የሚለውን ሐዲስ ሳትቀበል ቀርታለች። ምክንያቷም፤ “ቁርኣን ‘ማንም ነፍስ የማንኛይቱንም ኃጢያት አትሸከምም’ እያለ ነብያችን እንዴት እንዲህ ይላሉ?” የሚል ነው።

ሌላኛው የአዒሻ ተመራማሪነት ማሳያ የሚሆነው ነብዩ “ውሻ፣ አህያና ሴት እነዚህ ሶስት ነገሮች ሶላት ያበላሻሉ።” ብለዋል መባሉን አለመቀበሏ ነው። አዒሻ ይሄንን አባባል ስትሰማ “ምን ያህል ብትደፍሩን ነው እኛን ከውሻና ከአህያ ጋር የምታነፃፅሩን? ነብዩ እንኳ እኔ ተኝቼ ለሊት ሲሰግዱ ሱጁድ ማድረጊያ ቦታቸው ላይ እግሬን ዘርግቼ ሲያገኙ እግሬን ቀስ አድርገው ይገፉትና ሱጁዳቸውን ያደርጋሉ” አብደላህ ኢብኑ ዑመር ሴቶቹን በትጥበት (ጉስል) ወቅት ጸጉራቸውን እንዲፈቱ ማዘዙን ስትሰማ “ታዲያ አንድነቱን ጸጉራቸውን እንዲላጩ አያዛቸውም ነበር? እኔኮ ከነብዩ ጋር በአንድ የውሃ መያዣ ስታጠብ ጸጉሬ ላይ ሶስት ጊዜ ውሃ ከማፍሰስ ውጪ ፀጉሬን አልፈታውም ነበር።” ማለቷ ይነገራል።

አዎንታዊ ምልከታዋ

የአዒሻን አስደናቂ ባህሪና ጥንካሬ ለመግለጽ በሕይወቷ እጅግ አስቸጋሪ የሆነውን አጋጣሚ፣ በሀሰት የዝሙት ክስ ሲቀርብባት እንዴት እንዳለፈችው መግለጹ ጠቃሚ ነው። ይህ ክስ ሲቀርብባት አዒሻ እጅግ አዘነች በጣም ኃይለኛ ድብርት ውስጥ ገባች። ሆኖም፤ ፈጽሞ አላፈገፈገችም፤ ለማንምም አላጎበደደችም። ይልቅስ፤ መተማመኛዋን አላህን በማድረግ እሱ ራሱ ንጽህናዋን እስኪገልጽ ድረስ በጽናት ቆመች። አላህ ንጽህናዋን እንደሚገልፅ እርግጠኛ ብትሆንም ቅሉ በሷ ምክንያት አላህ ለመልክተኛው ወህይ (ራዕይ) ያወርዳል ብላ ግን አልጠበቀችም ነበር። ዳሩ ግን፤ አላህ ሙሉ ሱራ (ምዕራፍ) ሲያወርድ በተለያዩ ቦታዎች ላይ የሷን ንጽህናና ታማኝነት ሲገልጽ ነብዩን ለማመስገን ፈቃደኛ ሳትሆን ቀረች።

አላህን ብቻ ነው የማመሰግነው በማለት በአቋሟ ጸናች። ይህን ያለችው ግን ነብዩ ላይ ሥርኣት ለማጣት ሳይሆን የአላህን መብት ለርሱ ብቻ ከመስጠት አንጻር ነው። ይህ ተግባሯ ለሁሉም ሙስሊሞች እንደ ምርጥ ምሳሌ ሊቀርብ የሚችል ጉዳይ ነው። ምድራዊ ኃይላት የቱንም ያህል ቢሆኑ ከአላህ ጋር አይወዳደሩም። ለነገሩ ይህ አይነቱ ውስጣዊ ጥንካሬ ቀደምት ሙስሊሞች የነበራቸው ኃብት ነበር። አሁንም ለአዎንታዊ አመለካከቷ ምስጋና ይግባውና አዒሻ ኢ-ፍትሃዊነት፣ ኢ-ሞራላዊና ውሸት ያለችውን ነገር ከመጋፈጥ ወደ ኋላ ብላ አታውቅም። አንዳንዶች አቡበከር ሲዲቅ ከሞተ በኋላ እርሱ ላይ አቃቂር ለመፈለግ ሲሞክሩ ጠራቻቸውና አቡበከር በሕይወት ዘመኑ የፈጸማቸውን ተግባራት፤ ያደረጋቸውን ገድሎች እና ስኬቶቹን በመግለጽ ከርሱ ላይ ያገኙት ምን አይነት ሥህተት እንደሆነ ጠየቀቻቸው አንዳቸውም መልስ አልነበራቸውም።

በኸሊፋዎቹም ላይ (ሙዓውያን ጨምሮ) አንድ የፖሊሲ ስህተት ካየች ሳትናገራቸው አልፋ አታውቅም ነበር። አንዴ ሴቶች ቀብር ዚያራ እንዳያደርጉ እቀባ ነበር። እሷ ታዲያ መካ በሄደችበት የወንድሟን ቀብር ለመዘየር በቆመችበት አንድ ሠው መጣና “ነብያችን (ሰ.ዐ.ወ) ሴቶች ቀብር እንዳይዘይሩ ከልክለዋል” አላት። እሷም “ነብያችን ቀብር መዘየርን ለወንድም ለሴትም ከልክለው የነበረ ቢሆንም በኋላ አንስተዋል።” አለችው። በሷ ግንዛቤ መሠረት እቀባው ለሁለቱም ጾታ እኩል ተነስቷል። ለሴቶች አልተነሳም የሚባልበት አንዳችም ማረጋገጫ የለም። በሷ ጥንካሬም የእናታችን ሰፍያህ ፍላጎት ተሳክቷል። እናታችን ሰፍያህ ለአይሁዱ ወንድሟ የሃብቷን አንድ ሶስተኛ ለመስጠት ብትፈልግም ኸሊፋው ግን “ከነብዩ አስተምህሮ ውጪ ነው” በሚል ሊፈቅድላት አልቻለም። ሆኖም፤ በአዒሻ ያላሰለሰ ጥረት የእናታችን ሰፍያህ ፍላጎት ሊሳካ ችሏል። በውርስ ህግ ላይ የነበራት ከፍተኛ ብቃትና በራስ መተማመን በሌሎች ጉዳዮች ላይም እንድትሳተፍና ሴቶች በሙስሊም ማኅበረሰብ ውስጥ ስላላቸው ሚና ያለውን አስተሳሰብ የሚለውጥ ነው።

ለአብነት ያህል ሴቶች ከሶላተል ጀናዛ ስግደት እንዲታቀቡ መደረጉን መቃወሟ ነው። እንዲያውም አንዳንድ ጊዜ ጀናዛውን አስመጥታ መስጂድ በማስገባት የነብዩ ባለቤቶች እንዲሰግዱበት ታደርግ ነበር። በሁሉም የህይወት መስክ ተሳታፊ አዒሻ ለሴቶች ማኅበራዊ ተሳትፎ አቻ የማይገኝላት ድንቅ ምሳሌ ናት። ምክንያቱም፤ አዒሻ ከነብዩ ሞት በኋላ እንኳ በየትኛውም ኢስላማዊ ሕይወት ውስጥ ከመሳተፍ ወደ ኋላ ብላ አታውቅምና። በነብዩ የሕይወት ዘመን ደግሞ ጦር ሜዳ ድረስ በመሄድ የተሳትፎዋን ጥግ አሳይታለች። በዐሊይ ላይ በተካሄደው ፍልሚያም “የዑስማንን (ረ.ዐ) ገዳዮች ለመበቀል ዐልይ ቸልተኝነት አሳይቷል” በሚለው የተሳሳተ ድምዳሜዋ ምክንያት ዐሊይን ለመውጋት የተሠለፈውን ጦር መርታለች። በኋላ በዚህ አቋሟ ብትጸጸትም ዋናው ጉዳይ ግን ሴት ብትሆንም ሐሳቧን ለማሳካት እስከ ጦርነት ድረስ ለመሄድ እንደማትመለስ ማወቁ ነው። በሷ እይታ ሴት በኢስላም ያላት ሚና ቤት ውስጥ የታጠረ አይደለም።

ስትፀፀትም የተጸጸተችው በዐልይ ላይ በያዘችው አቋም እንጂ በነበራት ተሳትፎ አልነበረም። ከነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ጎን ሳይሆን ከእህቶቿ (ከሌሎቹ የነብዩ ባለቤቶች) ጎን በጀነት አል-ባቂ ለመቀበር የመረጠችውም ነብዩን በዐልይ ላይ በነበራት አቋም አፍራቸው ነው። እውቀት በማምረት ረገድ የነበራት ተሳትፎ አዒሻ ተፍሲር፣ ሐዲስ፣ ፊቅሂ እና ታሪክን በመሳሰሉ ኢስላማዊ የዕወቀት ዘርፎች እንዲሁም በዐረብኛ ቋንቋ እና በሕክምና የነበራት እውቀት በሶሃባዎችና በተከታዮቻቸው በሠፊው የሚታወቅ ጉዳይ ነው። ሌላው ቀርቶ ታላላቆቹ የነብዩ ባልደረቦች አቡበከርና ዑመር እንዲሁም የተቀሩት የነብዩ ባለቤቶች የአንድን ጉዳይ የመጨረሻ ውሳኔ አዒሻን ያማክሯት ነበር።

ከሰባቱ ታላላቅ የመዲና ቃዲዎች መካከል አንዱ የሆነው አቡ ሰለማህ ቢን አብዱራህማን “በሕይወቴ የአዒሻን ያህል ሠፊ የሐዲስ ግንዛቤ፣ ለሙስሊሞች አስፈላጊ በሆኑ አጀንዳዎች ላይም ጥልቅ የፊቅሂ ዕውቀት ያለው እና የቁርኣን አንቀጾችንም መችና ለምን እንደወረዱ አብጠርጥሮ የሚያውቅ በውርስ ህግጋት ላይም የሚወዳደራት ሠው አላየሁም” ሲል ምስክርነቱን ሰጥቷል።

አዒሻ ከአላህ መልክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ሞት በኋላ የመምህራን መምህርት (አሰልጣኝ) ሆና አገልግላለች። በነብዩ መስጂድ ውስጥ የሚያስተምሩ ሠዎችንም ሲሳሳቱ ስታይ ታርማለች ጥያቄ ሊጠይቃት የመጣውንም መልስ ትሠጠዋለች። ከሷ ትምህርት ከቀሰሙ ሠዎች ውስጥ ጥቂቶቹ አብደላህ፣ ቃሲም፣ ዑርዋህ እና ዑምራህ ቢንት አብዱራህማን አል-አንሳሪ ይገኙበታል። ጥልቅ የሆነው የፊቅሂ ዕውቀቷ ብቻዋን ኢጅቲሃድ እንድታደርግ አስችሏታል። አል-ቃሲም እንደዘገበውም ከራሷ ኢጅቲሃድም በመነሳት በአቡበከር፣ በዑመርና በዑስማን ዘመን ከዚያ በኋላም እስከ ሕይወቷ ፍጻሜ ትምህርቶችን ስትሰጥ ኖራለች።

ከላይ እንደተገለጸውም የአዒሻ ኢጅቲሃድ የተመሠረተው ባላት ጥልቅ የቁርኣን እውቀት ላይ የተመሠረተ ነው። አንድ ሠው ስለአለማግባት ሲጠይቃት “አግባ አላህ ‘በርግጥ ከአንተ በፊት መልክተኞችን ልከናል፤ ለሁሉም ሚስቶችንና ልጆችን ሠጥተናል’ የሚለውን የአላህ ቃል አልሰማህምን? ስለዚህ፤ ከማግባት ረስህ አታቅብ” አለችው።

ኢጅቲሃዷ ከማንምና ከምንም ነጻ መሆኑን የሚያሳየን አንዳንድ ጊዜ እይታዋ ከሌሎቹ ሶሃባዎች እይታ ጋር ቀጥታ የሚቃረን መሆኑ ነው። አንዱ መጣና “አንዲት ሴት ረጅም መንገድ ስትሄድ ሁሌ መህረም (ባል ወይም የቅርብ ዘመድ) ሊከተላት ይገባልን?” ሲል ጠየቃት። እሷም “ሁሉም ሰው ሙህረም ይኖረዋልን?” ስትል መለሠችለት።

ማጠቃለያ

በተለይም፤ የአዒሻ ሕይወት አስደማሚ የሚሆነው የነበረችበትን ዘመን በትኩረት ስናጤን ነው። በዚህ ዘመን የሚኖሩ ሴቶች እንኳ አላህ የሠጣቸውን ችሎታ መጠቀም በማይችሉበት ኹኔታ አዒሻ በ6ተኛውና በ7ኛው ክፍለ ዘመን ያን የመሠለ ሕይወት መምራቷ ልዩ ምሳሌና ፋና ያደርጋታል።

ገና ከልጅነቷ አንስቶ በንጹህ እስላማዊ አየር ውስጥ አደገች፤ ሆኖም እስረኛ አልሆነችም። ሐሳቧን በልበ-ሙሉነት ከመግለጽና በማኅበረሠቡ ጉዳዮች ከመሳተፍ የማህበረሰቧም መሪ ከመሆን ያገዳት አንዳችም ነገር አልነበረም። በቀላሉ ለማስቀመጥ አዒሻ ለአላህና ለመልክተኛው (ሰ.ዐ.ወ) የተሰዋ ክቡር ሕይወትን መርታለች። ይህን አጭር መጣጥፍ በራሷ በእናታችን ንግግር እንዘጋዋለን። ምን አለች? “ሠዎችን ለማስደሰት ብሎ አላህ ያስከፋ አላህ ለሠዎች አሳልፎ ይተወዋል፤ አላህን ለማስደሰት የፈለገ ግን አላህ ይበቃዋል።”


2. አቡበክር አስ-ሲዲቅ

ዐብደላህ ቢን አቡ ቁሐፋህ ኡስማን ቢን ዓሚር አል-ቁረይሽይ አት-ተሚሚይ ሲሆን የዝሆኑ ክስተት እውን በሆነ በሁለት አመት ከስድሰት ወሩ ተወለዱ። ነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) በነብይነት ከመላካቸው በፊት አቡበክር ባልንጀራቸው ነበሩ። ከነብይነት በኋላም ቀድመው ሰለሙ። በመካው የዳዕዋ ዘመን አብረዋቸው ሆኑ። ወደ መዲና ሲሰደዱ፣ በዋሻው ታሪክና ከዚያ በኋላ እስኪሞቱ ድረስ ከርሳቸው አልተለዩም።

በተቡክ ዘመቻ የሙሰሊሞችን አርማ ተሸካሚ ነበሩ። በዘጠነኛው ዓመተ ሂጅራ ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) በሕይወት እያሉ የሐጅ ሥርዓትን መርተዋል። ከርሳቸው ሞት በኋላም እርሳቸውን ተክተው የሙስሊሞች ኸሊፋ ሆነዋል። የነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) ምትክ (ኸሊፊቱ ረሱሊላህ) የሚል ማእረግም በሙስሊሞች አግኝተዋል።

ኢብን ኢስሐቅ “ሲረቱል ኩብራ” በተሰኘ መጽሐፋቸው እንዳወሱት አቡበክር (ረ.ዐ) በወገኖቻቸው ዘንድ ተወዳጅ እና ተግባቢ ሰው ነበሩ። በቁረይሽ የዘር ሐረግና ታሪክ እውቀትም አቻ አይገኝላቸውም። ጸባየ መልካም ነጋዴ ነበሩ። ሰዎች የርሳቸውን እውቀት፣ ተሞክሮና መልካም ባህሪ በመሻት በጣም ይቀርቧቸው ነበር። ከርሳቸው ጋር መቀማመጥንም ይወዱ ነበር።

አቡበክር ይበልጥ የሚቀርቧቸውንና የሚያምኗቸውን ሰዎች ወደ እስልምና ጋበዙ። በርሳቸው እጅ፣ ዑስማን፣ ጦልሐ፣ ዙበይር፣ ሰዕድ እና ዐብዱረህማን ኢቢን አውፍ ሰለሙ። የዕቁብ ኢቢን ሱፍያን በታሪክ ዘገባቸው እንዳወሱት፣ አቡበክር ሲሰልሙ አርባ ሺህ (የወርቅ ሳንቲሞች) ነበሯቸው። ወዲያውኑ በአላህ መንገድ መጸወቱት። ለአላህ ሲሉ ስቃይና መከራ ያስተናገዱ ሰባት ባሪያዎችን ገዝተው ነጻ ለቀቁ። እነርሱም ቢላል፣ ዓሚር ኢቢን ፋሀይራህ፣ ዚኒራህ፣ ነህዲያህንና ልጇን፣ የበኒ ሙእመል እንስት አልጋይና ኡምሙ ዓቢስ ናቸው።

ኡሳማ ኢቢን ዘይድ አባታቸውን ጠቅሰው እንዳስተላለፉት “አቡበክር እውቅ ነጋዴ ነበሩ። ነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) በነብይነት ሲላኩ አቡበክር አርባ ሺህ የወርቅ ሳንቲሞች ነበሯቸው። ባሪያዎችን እየገዙ በመልቀቅና የተቸገሩ ሙስሊሞችን በመርዳት ሐብታቸውን ወጭ አደረጉ። ወደ መዲና ሲሰደዱ 5 ሺህ (የወርቅ ሳንቲሞች) ብቻ ቀራቸው። እርሱንም መዲና ውስጥ መጸወቱት።”

ቡኻሪ እንደዘገቡት ዐምር ኢቢን አል-ዓስ (ረ.ዐ) እንዲህ ሲሉ አስተላልፈዋል፡- “የአላህ መልእክተኛ ሆይ! ከርስዎ ዘንድ ይበልጥ ተወዳጅ ሰው ማን ነው? በማለት ጠየቅኳቸው። ‘ዓኢሻ’ አሉኝ። ‘ከወንድስ?’ አልኳቸው። ‘አባቷ’ አሉኝ። ቀጥሎም ሌሎች ሰዎችን አወሱ።” ዐብደላህ ኢቢን ጃእፈር (ረ.ዐ) እንዲህ ብለዋል፡- “ወዳጃችን አቡበክር፣ መልካም፣ እጅግ ሩህሩህና አዛኝ ኸሊፋችን ናቸው።” ኢብራሂም አን-ነኸዒ እንዲህ ብለዋል፡- “አቡበክር በጣም አዛኝ ስለነበሩ ‘አውዋህ’ ተብለው ተጠሩ።” በ 11ኛው ዓመተ ሂጅራ በወርሃ ጀማዱል ኡላ ሰኞ ቀን በ63 ዓመት እድሜያቸው ይህችን ዓለም በሞት ተሰናበቱ።

ባህሪያቸውና ስብእናቸው

በጃሂልያ ዘመን ከቁረይሾች መሐል በዘር ሐረግና በታሪክ እውቀት ወደር አይገኝላቸውም። ውጤታማ ነጋዴም ነበሩ። በመልካም ባህሪና በችሮታ ይታወቃሉ። ወገኖቻቸው ይወዷቸዋል። አስካሪ መጠጥ አይጠጡም፣ ጣኦት አያመልኩም። ስብእናቸውን የሚያጎድፍ አንዳች ድርጊት ሲፈጽሙ አልተስተዋሉም። ቆዳቸው ነጭና አካላቸው ሸንቃጣ፣ የፊታቸው ስጋ መጠነኛ ነበር። ዓይኖቻቸው ገባ፣ ግንባራቸው ወጣ ያሉ ነበሩ። ጸጉረ ብዙ፣ የተስተካከለ ቁመና ባለቤት ነበሩ።

ሰዎች በጃሂልያ ዘመን የአቡበክርን መልካም ስብእና እና ታማኝነት በማወቃቸው “አስ-ሲዲቅ” (እውነተኛው) በሚል ቅጽል ስም ጠሯቸው። በታማኝነታቸው ቁረይሾችን በመወከል ይፈጣጠሙ ነበር። ቁረይሾች እርሳቸው ያጸደቁትን ያጸድቃሉ። ሌላ ሰው ያጸደቀውን ግን ተቀብለው ለመተግበር ያንገራግራሉ።

ኢስላምን መቀበላቸው

ከነብይነት በፊት የመልእክተኛው (ሰ.ዐ.ወ) ባልደረባ ነበሩ። አላህ ነቢዩን (ሰ.ዐ.ወ) በመልእክተኝንት ሲያልቃቸው ወደ እስልምና መጀመሪያ የጋበዙት አቡበክርን ነበር። እርሳቸውም ሳያመነቱ እስልምናን ተቀበሉ። የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ይህን በማስመልከት ሲናገሩ፡-

“የትኛውም ሰው ወደ እስልምና ስጋብዘው ይከብደዋል። ለመቀበልም ያመነታል። አቡበክር ሲቀር። እርሱ ግን ወዲያውኑ እንደጠራሁት ሳያመነታ ተቀበለኝ።” (ሲረት ኢቢን ሂሻም) በተለያዩ የዳዕዋው እርከኖች ውስጥ ከአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ሳይነጠሉ፣ አስፈላጊውን ሁሉ እገዛ እያደረጉላቸው፣ ለአምላክና ለነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ጥሩና አማኝ፣ ለሐይማኖታቸው ቀናኢ ሆነው ኖረዋል። በዚህ ሂደትም የነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) የስደት ጉዞ ተጋሪ፣ የዋሻ ውስጥ ባልደረባ እንዲሆኑ ያስቻሏቸውን በርካታ መከራዎች አስተናግደዋል። ገንዘባቸውን ሁሉ ለእስልምና ዳዕዋ ሳይሰስቱ ችረዋል።

ከአላህ መልእክተኛም (ሰ.ዐ.ወ)

“የአቡበክር ገንዘብ የጠቀመኝን ያህል በማንም ገንዘብ አልጠቀመኝም።” የሚል ምስክርነትአግኝተዋል። (አህመድ፣ አቡ ሐቲምና ኢቢን ማጃህ) የዚህ ሁኔታ የአላህን መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) እስከ እለተ ሞታቸው ድረስ ደግፈው ለቀልባቸውም ይበልጥ ቅርብና ለኸሊፋነትም ይበልጥ ብቁ ሶሐባ ለመሆን ታደሉ። በዚህ ረገድ ታላቁ ነቢይ (ሰ.ዐ.ወ) የሰጡት ምስክርነት ከበቂ በላይ ነው። እንዲህ ብለዋል፡- “በባልደረባነትና በገንዘብ ከማንም በላይ የደገፈኝ አቡበክር ነው። ከአምላኬ ውጭ የመጨረሻውን ፍጹማዊ ፍቅር የምለግሰው ሰው ቢኖር ኖሮ ያ ሰው አቡበክር ይሆን ነበር። ቢሆንም የእስልምና ወንድማማችነት እና ፍቅር አስተሳስሮናል።” (ቡኻሪ፣ ሙስሊምና ቲርሚዚ ዘግበውታል)

ልቅናቸውን የሚገልጹ ምስክርነቶች የአቡበክርን ልቅና ከሚያሳዩ ዘገባዎች መካከል አቡ ሰዒድ (ረ.ዐ) ያስተላለፉት ይገኝበታል። እንዲህ ብለዋል፡- “ከእለታት አንድ ቀን የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ)፡- ‘አላህ አንድን ባሪያውን ከዚህች ዓለም ሕይወትና ከርሱ ዘንድ ካለው ጸጋ ሲያስመርጠው ከአላህ ዘንድ ያለውን መረጠ።’ በማለት ሲናገሩ አቡበክር አለቀሱ። ለቅሷቸው አስገረመን። ለካስ ምርጫ የተሰጣቸው መልእክተኛው (ሰ.ዐ.ወ) ኖረዋል። አቡበክርም ከማንኛችንም ቀድመው ይህን ተረድተዋል:: መልእክተኛውም (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡-

ﺇﻥَّ ﻣﻦ ﺃﻣﻦِّ ﺍﻟﻨﺎﺱ ﻋﻠﻰَّ ﻓﻰ ﺻﺤﺒﺘﻪ ﻭﻣﺎﻟﻪ ﺃﺑﺎ ﺑﻜﺮ ، ﻭﻟﻮ ﻛﻨﺖ ﻣﺘﺨﺬﺍً ﺧﻠﻴﻼً ﻏﻴﺮ ﺭﺑﻰ ﻻﺗﺨﺬﺕ ﺃﺑﺎ ﺑﻜﺮ ﻭﻟﻜﻦ ﺃﺧﻮﺓ ﺍﻹﺳﻼﻡ ﻭﻣﻮﺩﺗﻪ ، ﻻﻳﺒﻘﻴﻦ ﻓﻰ ﺍﻟﻤﺴﺠﺪ ﺑﺎﺏ ﺇﻻ ﺳُﺪَّ ﺇﻻ ﺑﺎﺏ ﺃﺑﻰ ﺑﻜﺮ

‘በባልደረባነትና በገንዘብ ከማንም በላይ የደገፈኝ አቡበክር ነው። ከአምላኬ ውጭ የመጨረሻውን ፍጹማዊ ፍቅር የምለግሰው ሰው ቢኖር ኖሮ ያ ሰው አቡበክር ይሆን ነበር። ቢሆንም የእስልምና ወንድማማችነት እና ፍቅር አስተሳስሮናል። የአቡበክር በር ሲቀር ሁሉም የመስጂዱ በሮች ይዘጋሉ’። ” (ቡኻሪ፣ ሙስሊምና ቲርሚዚ ዘግበውታል)

በሌላ ዘገባ እንደተወሳው እንዲህ ብለዋል፡- “ከአምላኬ ውጭ ፍጹማዊ ፍቅር የምለግሰው ሰው ቢኖር ኖሮ ያ ሰው አቡበክር ይሆን ነበር። ይህም ሆኖ ወንድሜና ባልደረባዬ ነው። አላህ ባልደረባችሁን ፍጹማዊ ወዳጁ (ኸሊል) አድርጎታል።” (ቡኻሪ፣ ሙስሊምና ቲርሚዚ ዘግበውታል) በአላህና በመልእክተኛው (ሰ.ዐ.ወ) ማመን አቡበክር የመጀመሪያው ሙስሊም እንዲሆኑና የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) የሚናገሩትን ሁሉ ቅንጣት ሳይጠራጠሩና ሳያመነቱ እንዲቀበሉ የረዳቸው ይህ እምነታቸው ነው። በኢስራእ እና ሚዕራጅ ሐዲስ ውስጥ ያሳዩትን እጅግ አንጸባራቂ አቋም አስተውል። የአላህ መልእክተኛ ለባልደረቦቻቸውና ለቁረይሾች በዚያች ሌሊት ያጋጠማቸውን ክስተት ባጫወቷቸው ጊዜ እምነተ ደካሞች ከእስልምና እስከ መውጣት ደረሱ።

ቁረይሾችም በአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ተሳለቁ። አቡበክር ስለዚህ እንግዳ ክስተት የሚኖራቸውን አቋም ለማወቅም አቡ ጀህል ወደርሳቸው ሄደ። ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) የተናገሩትንም አጫወታቸው። እርሳቸውም በፍጹም መተማመንና በእርጋታ፡- “በእርግጥ ይህን ተናግረዋልን?” በማለት ጠየቁ። አቡ ጀህልም “አዎ” ሲል መለሰ። እርሳቸውም፡- “ሙሐመድ ይህን ከተናገረ እውነቱን ነው” አሉ። አቡ ጀህልና አብረውት የነበሩት ባልደረቦቹም፡- “በአንድ ቀን ሌሊት ወደ በይተል መቅዲስ ሄጄ ሳይነጋ በፊት ተመለስኩ ማለቱን አምነህ ትቀበላለህን?” አሏቸው። አቡበክር የሚከተለውን አስገራሚ መልስ ሰጡ፡-

ﺇﻧﻲ ﻷﺻﺪﻗﻪ ﻓﻴﻤﺎ ﻫﻮ ﺃﺑﻌﺪ ﻣﻦ ﺫﻟﻚ ،ﻣﻦ ﺧﺒﺮ ﺍﻟﺴﻤﺎﺀ ﻳﺄﺗﻴﻪ ﻓﻲ ﻏﺪﻭﺓ ﺃﻭ ﺭﻭﺣﺔ

“ከዚህ ይበልጥ እንግዳ የሆነ ነገር ተናግሮ አምኘዋለሁ። ጧት ማታ ከሰማይ መልእክት እንደሚወርድለት ነግሮኝ ተቀብየዋለሁ” አሉ። ወደ ነቢዩ (ሶ.ወ.ወ) በመሄድም የኢስራእን ታሪክ ሰሙ። “አንተ የአላህ መልክተኛ መሆንህን እምሰክራለሁ።” በማለትም የሰሙትን ሳያመነቱ መቀበላቸውን አረጋገጡ። (ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል)

የመጨረሻውን የምጥቀት ጫፍ የደረሰ ኢማን፣ የዚህ እምነት ባለቤት የኢስላም ታላላቅ ሰዎች ፈርጥ ቢሆኑ ምኑ ያስገርማል! መስዋእትነት አቡበክር ነፍሳቸዉንና ገንዘባቸውን ለእስልምና ዳዕዋ መሰዋታቸው የጽኑ እምነታቸው አይቀሬ ውጤት ነው። ኢማን ወደ ቀልብ ሲገባ ለመስዋእትነት ያነሳሳል። እንደ አቡበክር አይነት እጅግ ጽኑና ጥልቅ እምነት ከሆነስ?! አቡበክር ራሳቸውን ለመስዋእትነት አቅርበው የአላህን መልእክተኛ የታደጉባቸው አጋጣሚዎች ብዙ ናቸው።

አንድ ቀን ቁረይሾች ከካዕባ መስክ ላይ የአላህን መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ለማነቅ ሙከራ ሲያደርጉ አቡበክር ተከላከሉላቸው። በዚህ ጊዜ ነቢዩን (ሰ.ዐ.ወ) ትተው ከርሳቸው ላይ በመረባረባቸው ራሳቸውን ስተው እስኪወድቁ ድረስ ደበደቧቸው። አፍንጫቸውን ከዓይናቸው ወይም ከጉንጫቸው መለየት እስኪያዳግት ድረስ ክፉኛ ቆሰሉ። ሰዎች አንስተው ወደቤታቸው ወሰዷቸው። ራሳቸውን ሲያውቁ መጀመሪያ ያቀረቡት ጥያቄ፡- “የአላህ መልእክተኛ በምን ሁኔታ ውስጥ ናቸው?” የሚል ነበር። (ሲረቱ አን-ነበዊያህ ዘይኒ ደህላን፡፡)

ከመልእክተኛው (ሰ.ዐ.ወ) ጋር ወደ መዲና በተሰደዱ ጊዜም ተመሳሳይ መስዋእትነት ከፍለዋል። ቁረይሾች አግኝተው ሊገድሏቸው ብርቱ ጥረት አድርገዋል። በዚህ ጊዜ የአቡበክር አቋም እጅግ አስገራሚ ነበር። ቁረይሾች ከዋሻው በር ላይ ቆመው በነበረ ጊዜ የተናገሩትን ድንቅ ቃል እንመልከት።

“የአላህ መልእክተኛ ሆይ! አንደኛቸው ወደ እግሩ ስር ቢያይ ይመለከተናል።” መልእክተኛው ግን ባልደረባቸውን እንዴት እንደሚያጸኑ ያውቁ ነበር። እንዲህ አሉ፡- “አቡበክር ሆይ! አላህ አብሯቸው ባለ ሁለት ሰዎች ስጋት አይግባህ።” አቡበክር ገንዘባቸውን ሁሉ ለእስልምና ዳዕዋ መስዋእት አደረጉ።

ዓኢሻ እንዲህ ብለዋል፡- “አቡበክር 40 ሺህ (የወርቅ ፍራንክ) ለዳዕዋ መጸወቱ። የአላህ መልእክተኛ ለአስቸጋሪው የተቡክ ዘመቻ ጦርነት ትጥቅና ስንቅ እንዲዘጋጅ ባልደረቦቻቸውን በጠየቁ ጊዜ ሶሐቦች ገንዘቦቻቸውን እየያዙ መጡ። ኡስማን ብዙ ገንዘብ አመጣ። ዑመር ግማሽ ሐብታቸውን መጸወቱ። አቡበክር ደግሞ ሙሉ ገንዘባቸውን ሰጡ።

የአላህ መልእክተኛም (ሰ.ዐ.ወ)፡- ‘አቡበክር ሆይ! ለቤተሰቦችህ ምን አስቀረህ?’ ሲሏቸው። ‘አላህንና መልእክተኛውን’ ሲሉ መለሱ።” (ቲርሚዚ ዘግበውታል)

ብልህነትና ቆራጥነት

በጃሂልያ ዘመን ወገኖቻቸው ጣኦት ለማምለክ ሲጋፉ እርሳቸው አንድም ጊዜ እንኳ ለጣኦታት ለመስገድ ካለመፍቀዳቸው፣ ወገኖቻቸው በአስካሪ መጠጥ ሲነከሩ እርሳቸው ግን ኢምንት እንኳ ካለመጎንጨታቸው የበለጠ ብልህና አስተዋይ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ነገር የለም። ጣኦት አምልኮ ቂልነት እና ጥመት፣ አስካሪ መጠጥ መጠጣትም ውድቀትና ውርደት መሆኑን በብሩህ አእምሯቸው ተረድተዋል።

ምን ያህል ጀግናና ቆራጥ እንደሆኑ ለማሳየት የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) በሞቱና ከፊል ዐረቦች በኢስላማዊው ስርዓት ላይ ባመጹ ጊዜ ያሳዩአቸው አስደናቂ የጀግንነት አቋሞች በቂ ናቸው። ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) በሞቱ ጊዜ ሶሐቦች እጅግ ከማዘናቸው የተነሳ ከፊሎቹ አንደበታቸው ተሳሰረ። ሌሎችም ከተቀመጡበት መነሳት ተሳናቸው።

ዑመርም (ረ.ዐ) “ነብዩ አልሞቱም። ይመለሳሉ።” እስከማለት ደረሱ። አቡበክር ግን ሌሎች ሰዎች እንደሚሞቱት መልእክተኛውም መሞታቸውን አወጁ። የዑመርን ንግግር ሐየሱ። ሶሐቦችን አረጋጉ። የሚከተለውን የአላህ ቃልም አስታወሱ፡-

ﻭَﻣَﺎ ﻣُﺤَﻤَّﺪٌ ﺇِﻟَّﺎ ﺭَﺳُﻮﻝٌ ﻗَﺪْ ﺧَﻠَﺖْ ﻣِﻦ ﻗَﺒْﻠِﻪِ ﺍﻟﺮُّﺳُﻞُ

“ሙሐመድም ከበፊቱ መልክተኞች በእርግጥ ያለፉ የኾነ መልክተኛ እንጅ ሌላ አይደለም፡፡” (ኣሊ-ዒምራን 3፤144)

ሪዳህን ክስተትን የተቆጣጠሩበት ሁኔታም በወሳኝና ፈታኝ ሁኔታዎች ውስጥ የሚላበሱትን ፍጹም ጀግንነት ያሳያል። ያኔ አላህ የአቡበክርን ቀልብ በሐቅ ላይ ባያጸና እና የጽኑ ነብያትን ቆራጥነት ባያላብሳቸው ኖሮ ተከስቶ የነበረው ፈተና ገና ለጋ የነበረውን የእስልምና ሕንጻና መንግስቱን ባወደመው ነበር። ይህም ስለሆነ ነው አቡበክር ከአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) በኋላ ሁለተኛው የእስልምና መንግስት መስራች ተብለው የሚወደሱት።

ትህትናና ቁጥብነት

እንደ አቡበክር ያለ ታላቅ ስብእና ስልጣን አያታልለውም። ከኢስላማዊው አደብና ስነምግባር አያወጣውም። እናም በኸሊፋነት ዘመናቸው ልክ እንደ ቀድሞው ለስላሳና አዛኝ፣ ለሕዝባቸው ጉዳይም ቀናኢ ሆነው ቀጠሉ። ተከታዩ ታሪክ አቡበክር በኸሊፋነት ዘመን የነበራቸውን ትህትና ለማሳየት ጥሩ ምስክር ነው፡- አቡበክር ለአዛውንትና ረዳት አልባ እንስቶች ዘወትር ጠዋት ፍየል ያልቡ ነበር። ኸሊፋ በሆኑ ጊዜ አንዲት የመንደራቸው እንስት፡- “ከእንግዲህ አቡበክር ፍየሎቻችንን አያልብልንም” አለች። አቡበክር ይህን ማለቷን ሲሰሙ፡- “በአላህ እምላለሁ፣ እንደወትሮው ሁሉ ማለቤን እቀጥላለሁ። የኖርኩበትን መልካም ባህሪ አላህ እንደማይቀይርብኝ ተስፋ አደርጋለሁ።” አሉ። የዓለማችን ታላላቆች ለክብራቸው እንዲያጎበድዱ የሚያደርግ አንጸባራቂ አቋም ነው።፡ ከስጋዊ ስሜቶችና ዝንባሌዎች በላይ በመምጠቅ የኡምማውን መብትና አስፈልጎት የማስታወስ፣ ክብሩንና ገንዘቡን የሚጠብቅለት ታላቅነት ነው።

የአቡበክር ዙህድ

የአቡበክርን ዙህድ (ለዓለማዊ ጸጋና ድሎት አለመጓጓት) ከሚያሳዩ ክስተቶች መሐል ኢማም አህመድ፣ አኢሻን ጠቅሰው የዘገቡት ታሪክ ይገኝበታል። እንዲህ ብላለች፡- “አቡበክር ሲሞቱ አንዲት ዲናር ወይም ዲርሃም አልተውም። ከመሞታቸው በፊት ገንዘባቸውን በሙሉ ወደ በይተል ማል (የሙስሊሞች የገንዘብ ግምጃ ቤት) አስገብተውት ኖሯል።”

ዑርወት እንዳስተላለፉት አቡበክር ኸሊፋ በተደረጉ ጊዜ ያላቸውን እያንዳንዷን ዲርሃምና ዲናራቸውን ወደ ሙስሊሞች በይተል ማል አስገቡ። “በዚህ ገንዘብ እነግድ ነበር። አሁን ግን ኸሊፋቸው ሲያደርጉኝ መነገድ አልቻልኩም።” አሉም።

አጧእ ቢን ሳኢብን በመጥቀስ ቢን ሰእድ እንደዘገቡት አቡበክር ኸሊፋ በተደረጉ ማግስት ጠዋቱኑ በርካታ ኩታ በትከሻቸው ተሸክመው ሲሄዱ ዑመር ተመለከቷቸው። “የት እየሄድክ ነው?” ሲሉም ጠየቋቸው። “ወደ ገበያ” በማለት መለሱ። “የሙስሊሞች ሐላፊ ተደርገህ እያለ ኃላፊነትህን ትተህ ገበያ ውስጥ ምን ትሰራለህ?” ሲሉም ጠየቋቸው። “ቤተሰቦቼን ምን ላበላ ነው?” አሉ አቡበክር። “አቡ ዑደይዳህ ቀለብ ይወስንልሃል” አሏቸው። ተያይዘው ወደ አቡ ዑበይዳህ ዘንድ ሄዱ። እርሳቸውም፡- “አንድ ሙሃጅር የሚበቃውን ቀለብ፣ ሳይበዛም ሳያንስም፣ እቆርጥልሃለሁ። ለክረምትና ለበጋ የሚሆን ልብስም እገዛልሃለሁ። እርሱ ሲነትብ ትመልሰውና በልዋጩ ሌላ ትወስዳለህ” አሉ። በየቀኑ ግማሽ ፍየል ወሰኑላቸው። ገላቸውን የሚሸፍኑበት እራፊ ጨርቅም ሰጧቸው!

በበጎ ነገሮች ሁሉ ቀዳሚ

አቡ ሁረይራ እንዳስትላለፉት ነቢዩ (ሶ.ዐ.ወ)፡- “ከናንተ ውስጥ ጾም ይዞ ያነጋ ማን ነው? በማለት ጠየቁ። አቡበክርም፡- ‘እኔ’ አሉ። ከናንተ ውስጥ ጀናዛን የሸኘ ማን ነው? ሲሉም ጠየቁ። አቡበክርም፡- ‘እኔ’ አሉ። ዛሬ ምስኪንን ያበላ ማን ነው? አሉም። አቡበክርም፡- ‘እኔ’ አሉ። በሽተኛ የጠየቀስ ማን ነው? ሲሉ፣ አቡበክር ‘እኔ’ አሉ። የአላህ መልእክተኛም፡- እነዚህ በጎ ድርጊቶች በአንድ ሰው ላይ አይሰባሰቡም፣ ያ ሰው ጀነት የገባ ቢሆን እንጅ አሉ።” (ሙስሊም ዘግበውታል) “ጅብሪል መጣና እጄን ይዞ ተከታዮቼ የሚገቡበትን የጀነት በር አሳየኝ። አሉ። አቡበክርም፡- ‘ከርስዎ ጋር ሆኜ ባየው እወድ ነበር’ አሏቸው። ነቢዩም፡- አቡበክር ሆይ! ከኡመቴ (ሕዝቦቼ) ውስጥ መጀመሪያ ጀነት የምትገባው አንተ ነህ አሏቸው።” (አቡ ዳውድ ዘግበውታል)

የአላህ ፍራቻ እና ጥንቃቄ

አቡበክር አንድ ባሪያ ነበራቸው። ዘወትር ጠዋት እየወጣ ስራ በመስራት ገንዘብ ያገኛል። አንድ ቀን ምግብ ይዞ መጣ። አቡበክርም አንድ ጉራሽ ተመገቡለት። ባሪያውም በመሐይምነት ዘመን ለፈጸመው የጥንቆላ ተግባር ከተሰጠው ክፍያ ያገኘው ምግብ እንደሆነ ነገራቸው። አቡበክርም፡- “ልታጠፋኝ ተቃርበህ ነበር።” አሉና ጣታቸውን ወደ ጉሮሯቸው በመላክ እንዲያስመልሳቸው ሞከሩ። አልወጣ ብሎ አስቸገራቸው። “በውሃ እንጅ አይወጣም” ሲሏቸው በሳህን ውሃ እንዲቀርብላቸው አደረጉና እርሱን እየጠጡ የበሉትን ሁሉ አስመለሱ። “አላህ ይዘንልዎት። ለአንዲት ጉርሻ ይህን ያህል ራስዎን ያንገላታሉን?” ተባሉ። “ነፍሴ ከአካሌ ካልተነጠለች ይህች ጉርሻ የማትወጣ ቢሆንም እንኳ ነፍሴን ከማውጣት ወደኋላ አልልም። የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ)፡- ‘በሐራም ምግብ የበቀለ ስጋ እሳት ለርሱ ይበልጥ የተገባ፣ ነው’ ሲሉ በመስማቴ በዚህ ጉርሻ አማካይነት ከአካሌ አንዳች ነገር እንዳይበቅል ስለፈራሁ ነው” አሉ።

(በይሐቂ እንደዘገቡት አል ሒልያህ 2/31)

የአምላካቸውን ከለላነት መምረጣቸው ቡኻሪ እንደዘገቡት ዓኢሻ (ረ.ዐ) የሚከተለውን ተናግረዋል፡- “ወላጆቼ ሙስሊም ሆነው እንጅ አላውቃቸውም። የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ጠዋትና ማታ ከኛ ዘንድ የሚመጡ ሆነው እንጅ አንድም ቀን አላለፈም።” ሙስሊሞች መካ ውስጥ እንግልት ሲበዛባቸው አቡበክር ወደ ሐበሻ ለመሰደድ መካን ጥለው ወጡ። “በርከል ገማድ” ከተባለ ቦታ ሲደርሱ ኢብን ዱግነህ አገኛቸው። የጎሣ አለቃ ነው።

“የት እየሄድክ ነው?” ሲልም ጠየቃቸው። “ወገኖቼ ከሀገር አስወጡኝ፤ ሀገር ላገር እየተዘዋወርኩ አምላኬን ማምለክ እፈልጋለሁ” ሲሉ መለሱ። ኢብን ዱግነህም፡- “አቡበክር ሆይ! አንተን የመሰለ ሰው ሀገር ጥሎ አይወጣም። እንዲወጣም አይደረግም። አንተ ችግረኛን የምትረዳ፣ ዝምድናን የምትቀጥል፣ ችግርን የምትጋራ፣ እንግዳ የምታስተናግድ፣ ከባለመብት ጎን የምትቆም ሰው ነህ። ስለዚህ እኔ ከለላ እሆንሃለሁ።

ተመለስና እዚያው ሀገርህ ውስጥ ጌታህን አምልክ” አላቸው። ወደ መካ ተመለሱ። ኢቢን ዱግነህም አብሯቸው ሄደ። ማታ ላይ የቁረይሽ ባላባቶችን በየቤታቸው እየዞረ፡- “አቡበክር ከሀገር የሚወጣ ወይም እንዲወጣ የሚደረግ ሰው አይደለም። ችግረኛን የሚታደግን፣ ዝምድናን የሚቀጥልን፣ ችግርን የሚጋራን፣ እንግዳ የሚንከባከብንና ከተበዳይ ጎን የሚቆምን ሰው ከሀገር ታስወጣላችሁን?” ሲል ወቀሳቸው። 

ቁረይሾች ለአቡበክር ከለላ መሆኑን ተቀበሉ። ግና እንዲህ ሲሉ አስጠነቀቁት፡- “ለአቡበክር አምላክን ቤቱ ውስጥ ብቻ እንዲያመልክና እንዲሰግድ ንገረው። በቤቱ ውስጥ ያሻውን ነገር ያንብብ። እኛን እያወከን ግን፣ እነዚህን ነገሮች በይፋ ከፈጸመ ሴቶቻችንና ልጆቻችን እንዳይፈተኑ እንሰጋለን።” ኢብን ዱግነህ ለአቡበክር ይህንኑ ነገራቸው። አቡበክር ጌታቸውን በቤታቸው ውስጥ ማምለካቸውን ቀጠሉ። ሶላት በይፋ አይሰግዱም፤ ቁርአንም ከቤታቸው ውጭ አይቀሩም።

በኋላ ግን ከካዕባ ግቢ ውስጥ የመስገድ ሐሳብ መጣላቸው። ይህንኑ አደረጉ። ከርሱ ውስጥም መስገድና ቁርአን መቅራት ጀመሩ። የጣኦታውያን እንስቶችና ሕጻናትም በአግራሞት ይመለከቷቸው ጀመር። አቡበክር አልቃሽ ሰው ነበሩ። ቁርአን ሲቀሩ በለቅሶ ይንፈቀፈቃሉ። ይህ ድርጊታቸው የቁረይሽ ባላባቶችን አስደነገጠ። ለኢቢን ዱግነህም እንዲህ የሚል መልእክት ላኩ፡-

“አቡበክር አምላኩን ከቤቱ ውጭ ላያመልክ ቃል አስገብተን ከለላ ትሆን ዘንድ ፈቅደን ነበር። እርሱ ግን ቃሉን ጥሶ በካዕባ ግቢ ውስጥ መስገድ እና መቅራት ጀምሯል። ሴቶቻችንና ልጆቻችን እንዲፈተኑ ስለማንሻ ከልክለው። ቤቱ ውስጥ ብቻ ማምለክ ከፈለገ ይችላል። አምልኮውን ይፋ ማድረግ የሚፈልግ ከሆነ ግን ከለላነትህን መልስለት፤ የሰጠንህን ቃል ማፍረስ አንሻም። በይፋ እንዲያመልክም አንፈቅድለትም።” ዓኢሻ እንዳስተላለፉት ኢቢን ዱግነህ ወደ አቡበክር ዘንድ መጣና፡- “እኔና አንተ የተጋባነውን ቃል ታውቃለህ። ስለዚህም በቃልህ መሠረት ቤትህ ውስጥ ብቻ አምልክ፤ ካልሆነ ከለላነቴን መልስልኝ።

ከለላዬ እንዲጣስና ዐረቦችም ይህን ጉድ እንዲሰሙ አልሻም” አለ። አቡበክርም፡- “ከለላነትህን መልሸልሃለሁ። ከእንግዲህ የአላህን ከለላነት ብቻ እሻለሁ።” አሉ። ከአቡበክር ሌላ ይህን የጀግንነት አድራጎት ማን ሊፈጽም ይችላል። በዚህ ድንቅ አቋም ሊዋብ የሚችለው የአቡበክር ስብእና ብቻ ነው። በአላህ ላይ የነበራቸው እምነት ይህን ያህል ጽኑና ጠንካራ ነበር። የክህደት ሐይሎች ዙሪያውን ከበው ሊያጠፏቸው ባሰፈሰፉበት ወቅት አላህ ከየትኛውም ፍጡር የላቀ፣ ከለላው የሚከጀል፣ ተስፋ የሚጣልበት ብቸኛ ሐይል መሆኑን፣ አላህ የረዳውን የሚያሸንፈው እንደሌለ በጥልቅ ተረዱ።

በኸሊፋነት ዘመን

አቡበክር ኸሊፋ የሆኑት ሙስሊሞች በነብያቸው (ሰ.ዐ.ወ) ሞት ምክንያት ግራ በተጋቡበት አስፈሪ ወቅት ነው። በወቅቱ ከፊል ዐረቦች ከኢስላም አፈንግጠዋል። ሌሎች ከመልእክተኛው (ሰ.ዐ.ወ) በኋላ ለማንም ላለማደር ወስነዋል። ሮሞች ሂጃዝን ለመውረር በዝግጅት ላይ ናቸው። የሮሞችን ጥቃት ለመመለስ የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ያዘጋጁት የኡሳማ ኢቢን ዘይድ (ረ.ዐ) ጦር ጉዞውን ለመቀጠል ከመዲና አፋፍ ላይ ሆኖ ትእዛዝ ይጠባበቃል። በዚህ ሁሉ ፈታኝ ሁኔታ ውስጥ ኸሊፋ የተደረጉት አቡበክር ሐላፊነታቸውን በሚገባ ተወጡ።

አፈንጋጮችን (አል-ሙርተዲን) አደብ (ሥርዓት) ለማስያዝ ቆራጥ ውሳኔ ወሰኑ። ሌሎች ሶሐቦች የጦርነቱን ሐሳብ ባይደግፉም እርሳቸው ግን በዚሁ ሐሳባቸው ጸኑ። በኋላ ላይ ግን ሶሐቦች የርሳቸውን ሐሳብ ደገፉ። በአላህ በረከትም እስልምናን በዐረቢያ ውስጥ እንደ አዲስ ለማጽናት ተመሙ። አላህ የለገሳቸው ድል ታላቅ ነበር። የአመጽ እንቅስቃሴውን በእንጭጩ ቀጩት። የኡሳማንም ጦር የአላህ መልእክተኛ ወዳሰማሩት ግንባር አዘመቱ። ይህ ጦር እስልምናን ለማስፋፋትና ሕዝቦችን ነጻ ለማውጣት የተገኙ ድሎች ሁሉ መነሻ ሆነ። የአስተዳደር ፖሊሲያቸው ኸሊፋ በተደረጉ ጊዜ ያሰሙት ተከታዩ ታሪካዊ ንግግር ነበር፡-

ﺇﻧﻰ ﻗﺪ ﻭﻟﻴﺖ ﻋﻠﻴﻜﻢ ﻭﻟﺴﺖ ﺑﺨﻴﺮﻛﻢ ، ﻓﺈﻥ ﺃﺣﺴﻨﺖ ﻓﺄﻋﻴﻨﻮﻧﻲ ، ﻭﺇﻥ ﺃﺳﺄﺕ ﻓﻘﻮﻣﻮﻧﻲ ، ﺍﻟﺼﺪﻕ ﺃﻣﺎﻧﺔ ﻭﺍﻟﻜﺬﺏ ﺧﻴﺎﻧﺔ ، ﻭﺍﻟﻀﻌﻴﻒ ﻓﻴﻜﻢ ﻗﻮﻯ ﻋﻨﺪﻯ ﺣﺘﻰ ﺁﺧﺬ ﻟﻪ ﺍﻟﺤﻖ ، ﻭﺍﻟﻘﻮﻯ ﻓﻴﻜﻢ ﺿﻌﻴﻒ ﻋﻨﺪﻯ ﺣﺘﻰ ﺁﺧﺬ ﺍﻟﺤﻖ ﻣﻨﻪ ، ﻻ ﻳﺪﻉ ﻗﻮﻣﺎً ﺍﻟﺠﻬﺎﺩ ﻓﻰ ﺳﺒﻴﻞ ﺍﻟﻠﻪ ﺇﻻ ﺿﺮﺑﻬﻢ ﺍﻟﻠﻪ ﻋﺰ ﻭﺟﻞ ﺑﺎﻟﺬﻝ ، ﻭﻻ ﺗﺸﻴﻊ ﺍﻟﻔﺎﺣﺸﺔ ﻓﻰ ﻗﻮﻡ ﻗﻂ ﺇﻻ ﻋﻤﻬﻢ ﺍﻟﻠﻪ ﺑﺎﻟﺒﻼﺀ ، ﺃﻃﻴﻌﻮﻧﻲ ﻣﺎ ﺃﻃﻌﺖ ﺍﻟﻠﻪ ﻭﺭﺳﻮﻟﻪ ، ﻓﺈﺫﺍ ﻋﺼﻴﺖ ﺍﻟﻠﻪ ﻭﺭﺳﻮﻟﻪ ﻓﻼ ﻃﺎﻋﺔ ﻟﻰ ﻋﻠﻴﻜﻢ

“እኔ በናንተ ላይ ተሹሚያለሁ። ይህ ማለት ግን ከናንተ ብልጫ አለኝ ማለት አይደለም፤ በጎ ከሰራሁ አግዙኝ። ክፉ ከሰራሁ አስተካክሉኝ። እውነት መናገር አደራን መጠበቅ ሲሆን፣ መዋሸት ደግሞ ክህደት ነው። ከናንተ መካከል ደካማው መብቱን እስካሟላለት ድረስ ከኔ ዘንድ ጠንካራ ነው። ከናንተ ዘንድ ጠንካራው ግዴታውን እንዲወጣ እስካደርገው ድረስ ከኔ ዘንድ ደካማ ነው። ሰዎች በአላህ መንገድ መፋለምን ሲተው አላህ ውርደትን ያከናንባቸዋል። በአንድ ሕዝብ ውስጥ ዝሙት ከተስፋፋ አላህ ሁሉንም በቅጣቱ ያጠቃልላቸዋል። አላህንና መልእክተኛውን እስከታዘዝኩ ድረስ ታዘዙኝ። የአላህን እና የመልእክተኛውን ፈቃድ ስጥስ ግን ልትታዘዙኝ አይገባም።”

አቡበክር የአስተዋይ ልቦና፣ የሩቅ አሳቢ አእምሮ ባለቤት ነበሩ። በዘመናቸው ያሉ ሁኔታዎችን በጥንቃቄ ከማየት፣ በጥልቀት ከማስተዋል የመነጨ ንግግራቸው የልብ ብርታትን፣ ፍጹም መተማመንና ጽኑነትን የተላበሰ ነው። የኸሊፋነት ዘመናቸው ጥቂት ቢሆኑም እጅግ አስደናቂና ታላላቅ በሆኑ ስኬቶች የተሞሉ ናቸው። የአቡበክር ብልህነት በበርካታ አጋጣሚዎች ተስተውሏል። በተለይም እጅግ ፈታኝ በሆኑ ሁኔታዎች። ታላቅ ሰው ታላላቅ አቋሞችን ያስመዘግባል።

ቁርኣንን የመሰብሰብ ድንቅ ተግባር በየማማህ ጦርነት ወቅት በርካታ የቁርአን አዋቂዎች የመገደላቸውን ዜና አቡበክር በሰሙ ጊዜ ዑመር አብረዋቸው ነበሩ። በዚህ ጦርነት በርካታ የቁርአን አዋቂዎች ተገድለዋል።

“በሌሎች ጦርነቶችም ተመሳሳይ ሁኔታ ተፈጥሮ አዋቂዎቻችን እንዳያልቁ እሰጋለሁ። ስለዚህም በነቢዩ ዘመን የተጻፉ የቁርኣን ጽሑፎች እንዲሰበሰቡ ብታደርግ መልካም ይመስለኛል” አሉ።

አቡበክርም፡- “የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ያላደረጉትን ነገር እንዴት እኔ አደርገዋለሁ?” ሲሉ ጠየቁ። ዑመርም፡- “በአላህ እምላለሁ! ይህን ብታደርግ መልካም ነው” አሉ። ዑመር አቡበክርን ደጋግመው ጎተጎቱ። በመጨረሻም አቡበክር በሐሳቡ ተስማሙ። ዘይድ እንዲህ ሲሉ አስተላልፈዋል አቡበክር እንዲህ አሉኝ፡- “አንተ አስተዋይ ወጣት ነህ በመጥፎ ነገር አንጠረጥርህም።

ለአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ቁርኣን ሲወርድላቸው እየተከታተልክ ትጽፍ ነበር። ስለዚህም የተጻፉ የቁርኣን መልእክቶችን በአንድ አሰባስብ” አሉኝ። በአላህ እምላለሁ! ይህን ሐላፊነት ከሚያሸክሙኝ ተራራ እንድገፋ ቢያዙኝ እመርጥ ነበር።

“የአላህ መልእክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ያላደረጉትን እንዴት እናንተ ታደርጋላችሁ?” አልኳቸው። አቡበክርም “በአላህ እምላለሁ! በጎ ነገር ይመስለኛል” አሉኝ። ደጋግመውም ጎተጎቱኝ። በመጨረሻ በሐሳባቸው ተስማማሁ። በተለያዩ ቁሳቁሶች ላይ ተጽፎ የነበረውን ቁርአን ከያለበት ተከታትዬ ሰበሰብኩት። የአት-ተውባህን የመጨረሻ አናቅጽም ከኹዘይማህ ቢን ሳቢት ዘንድ አገኘሁት።

ﻟَﻘَﺪْ ﺟَﺎﺀَﻛُﻢْ ﺭَﺳُﻮﻝٌ ﻣِّﻦْ ﺃَﻧﻔُﺴِﻜُﻢْ ﻋَﺰِﻳﺰٌ ﻋَﻠَﻴْﻪِ ﻣَﺎ ﻋَﻨِﺘُّﻢْ ﺣَﺮِﻳﺺٌ ﻋَﻠَﻴْﻜُﻢ ﺑِﺎﻟْﻤُﺆْﻣِﻨِﻴﻦَ ﺭَﺀُﻭﻑٌ ﺭَّﺣِﻴﻢٌ ﻓَﺈِﻥ ﺗَﻮَﻟَّﻮْﺍ ﻓَﻘُﻞْ ﺣَﺴْﺒِﻲَ ﺍﻟﻠَّﻪُ ﻟَﺎ ﺇِﻟَٰﻪَ ﺇِﻟَّﺎ ﻫُﻮَ ﻋَﻠَﻴْﻪِ ﺗَﻮَﻛَّﻠْﺖُ ﻭَﻫُﻮَ ﺭَﺏُّ ﺍﻟْﻌَﺮْﺵِ ﺍﻟْﻌَﻈِﻴﻢِ

“ከጎሳችሁ የሆነ ችግራችሁ በእርሱ ላይ ጽኑ የሆነ፣ በእናንተ (እምነት) ላይ የሚጓጓ፣ በምእምናን (ላይ) ርኅሩኅ አዛኝ የኾነ መልክተኛ በእርግጥ መጣላችሁ፡፡ ቢያፈገፍጉም አላህ በቂዬ ነው፡፡ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም፡፡ በእርሱ ላይ ተጠጋሁ እርሱም የታላቁ ዐርሽ ጌታ ነው በላቸው፡፡” (አል-ተውባህ 9፤ 128-129) (ሐዲስ ሐሰኑን ሶሂህ) ዘመን ተሻጋሪ መልእክቶቻቸው።

ﺃﻳﻬﺎ ﺍﻟﻨﺎﺱ : ﺇﻥ ﻛﺜﺮ ﺃﻋﺪﺍﺅﻛﻢ،ﻭﻗﻞ ﻋﺪﺩﻛﻢ، ﺭﻛﺐ ﺍﻟﺸﻴﻄﺎﻥ ﻣﻨﻜﻢ ﻫﺬﺍ ﺍﻟﻤﺮﻛﺐ؟ ﻭﺍﻟﻠﻪ ﻟﻴﻈﻬﺮﻥ ﻫﺬﺍ ﺍﻟﺪﻳﻦ ﻋﻠﻰ ﺍﻷﺩﻳﺎﻥ ﻛﻠﻬﺎ، ﻭﻟﻮ ﻛﺮﻩ ﺍﻟﻤﺸﺮﻛﻮﻥ، ﻗﻮﻟﻪ ﺍﻟﺤﻖ، ﻭﻭﻋﺪﻩ ﺍﻟﺼﺪﻕ ﺑَﻞْ ﻧَﻘْﺬِﻑُ ﺑِﺎﻟْﺤَﻖِّ ﻋَﻠَﻰ ﺍﻟْﺒَﺎﻃِﻞِ ﻓَﻴَﺪْﻣَﻐُﻪُ ﻓَﺈِﺫَﺍ ﻫُﻮَ ﺯَﺍﻫِﻖٌ ﻭَﻟَﻜُﻢُ ﺍﻟْﻮَﻳْﻞُ ﻣِﻤَّﺎ ﺗَﺼِﻔُﻮﻥَ ٢١ : ١٨

“ሰዎች ሆይ! በአላህ እምላለሁ! ጠላቶቻችሁ ቢበዙ፣ ወዳጆቻችሁ ቢያንሱና ሰይጣን በሙሉ ኃይሉ ቢዘምትባችሁም እንኳ አላህ ይህን ሐይማኖት የሐይማኖቶች ሁሉ የበላይ ያደርገዋል።

ጣኦታውያን ይህን ቢጠሉም። ንግግሩ እውነት፣ ቃል ኪዳኑም የማይታብል ቅል ነው።

አህባሽ ማን ነው የሀበሺ (አህባሽ) መንገድ የጀመረው አብደላ አል-ሐረሪ የተባለ ግለሰብ ነበር፡፡ ግለሰቡ ሐረር የተወለደ ሲሆን የሀይለ ስላሴ መንግስት ቀኝ እጅ ነበር፡፡ ከሃይለስላሴ አማች አንደርጌ ጋር ሆኖ ዓሊሞችን ሲያሳስር፣ መብትና እኩልነትን የሚሉትን ሙስሊሞችን ሲያጠቃ እና ሲሰልል ቆየ፡፡እ.ኤ.አ በ1940 (1367 ሂጅራ) ላይ በሐረር የቁርኣን ሂፍዝ ማዕከል መምህራንን አሳስሮ መርከዙን አስዘጋ፡፡ የመርከዙን ዳይሬክተር ሼህ ኢብራሁም ሀሰንን አሳስሮ 23 ዓመታት አስረፈደባቸው፡፡ አብደላ አል-ሐረሪ የፈጠረው ፊትና ‹‹ፊትነተልኩሉብ›› ተብሎ ይታወቃል፡፡ ከዚያም ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በሀደሬ ሰፈር ሙስሊሙን ሲያጋጭ ቆይቶ በ1948 ወደ እስራኤል ተጓዘ፡፡ ለዓመት በዚያ ቆይቶ በ1949 ወደ ሶሪያ ገባ፡፡ ከዚያም በ1950 ወደ ሊባኖስ ተጓዘ፡፡ በሊባኖስ ቁርአን በማቅራት ህፃናትን ማሳደን ቀጠለ፡፡ ቀስ እያለ በመቶዎች የሚቆጠሩ ተማሪች አፈራ፡፡ ከአገር ከወጣ በኋላ ከየሁዳዎች ጋር በሚስጢር ይገናኝ ጀመር። ከፍተኛ ገንዘብ ተመድቦለት እ.አ.አ በ1982 የሊባኖስ የርስ በርሱ ጦርነት ጊዜ ድምፁን አጥፍቶ ሀይሉን አጠናከረ፡፡ ከዚያ በ1980ዎች እስራኤል ሊባኖስ ስትወርና ስታጠቃ የሙስሊሞች ጀመዓ ስትወጋ አህባሾችን ግን ተወቻቸው፡፡ ምክንያቱም የርሷ ወዳጅ ናቸውና ነው፡፡ በ1990 አህባሾች በእስራኤል ተረድተው ወደ ፖለቲካ ገቡ፡፡ በ1992 የሊባኖስ ምርጫ ጥቂት ወንበር አሸንፈው ፓርላማ ገቡ፡፡ ቀስ በቀስ የራሳቸውን ሚሊሻ ጦር መለመሉ፡፡ ሙስሊሙን ማበጣበጡን ገፍተው ቀጠሉ፡፡ ከነርሱ ውጭ ያለውን ሁሉ ‹‹ካፊር›› እያሉ መፈረጁ ተያያዙት፡፡ ለመንግስትና ለእስራኤል መረጃ እየሰጡ ሙስሊሙን ማስመታት ጀመሩ፡፡ ራሳቸውን በውሸት ‹‹የሻፊዒ መዝሀብ እንከተላለን›› እያሉ ያስወራሉ፡፡ አህለል ሱንና ነው። አሻዓሪና ማቶረዲ ነን ይላሉ፡፡ ሱፊያም ነን ይላሉ። ሆኖም የሶፊያ ዓሊሞች በሊባኖስ በሌሎች ሀገራትም መጀመሪያ እውነት ሱፊያ ናቸው ብለው ተሸደውደው ነበር። ሆኖም በሗላ በዝርዝር ሲያውቋቸው አጋልጠው ምላሽ ጻፉባቸው። ሰዉም እንዲያውቃቸውን እና እናዳይከተሏቸው አስጠነቀቁ።እውነታው ግን እነርሱ የእስራኤል ቀኝ እጅ ናቸው፡፡ ቀሰ በቀስ አል-ሀበሺ የሱንና መንገድ እየበከለ ሺዓ፣ ሪፋኢ፣ ሙርጂአ፣ተክፊር፣ሱፊ፣አል-ጀበሪ፣ ቃዲሪያና ጃህሚያ ወዘተ መንገዶችን ቀይጦ(ስፕሪስሪስ) አድርጎ የራሱን አዲስ መንገድ ፈጠረ፡፡ የዓለም ሙስሊሞችን ማክፈር ያዘ፡፡ አብደላ አል-ሐረሪ ‹‹ሳዑዲ እንዴት ከፈረች?›› ብሎ ሁሉ መጽሀፍ ጽፏል፡፡ የነብዩ (ሶ.አ.ወ) አገር መካና መዲና የካፊር አገር ብሎ ጽፏል፡፡ ይህ ብቻ የየሁዳ መሳሪያ መሆኑን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል፡፡ ለመሆኑ አቋማቸው ምንድነው? ቀጥሎ ጥቂቶችን ብቻ እናያለን፡- 1. ከካፊር ጋር ቁማር መጫወት፣ የካፊርን (ክርስቲያን) ጎረቤት መስረቅና ማጭበርበር ይቻላል ብሎ ያስተምራል።ዋናው እንዳይነቃ በድብቅ ማድረግና ዋናው መጠንቀቅ ነው ብሎ ያስተምራል፡፡ (መጽሐፉ ሰሪህ አል-በያን፣ገጽ 133) 2. ሰሀቦችን ይሳደባል፡፡ አንዳንዶቹን ሰሀቦች ካፊር ናቸው የጀሀነም ናቸው ብሎ ጽፏል፡፡ ለምሳሌ ታላቁን የነብዩ (ሶ.ዐ.ወ) ሆሃባ ሙአዊያ ኢብኑ አቢሱፍያን ካፊር የጀሀነም ሲል ገልጿል፡፡ የነብያችን (ሶ.ዐ.ወ) ባለቤት አዒሻን ተሳድቧል፡፡ 3. በነጃሳ መስገድ ይፈቀዳል ይላል፡፡(መጽሐፉ ቡግየቱ ጧሊብ፣ገጽ 99-100) 4. ዘካ የለም ይላል፡፡ ዘካ ከእስልምና ማዕዘናት አንዱ ነው፡፡ አህባሾች ግን ሰው ዘካ እንዳያወጣ ከወረቀቱ ብር(ኖት) ላይ ዘካ የለበትም ይላሉ፡፡ ይህ ማለት በባንክም ይሁን በቤትዎ ቢሊዮን ብር እንኳ ካለዎ ዘካ አይስጡ ብሎ ይቀሰቅሳሉ፡፡ 5. ሪባ (ወለድ) መውሰድን ያበረታታሉ፡፡ ባንክ ገንዝ አስቀምጠው ባንኩ የካፊሮች(ወይም ስራ አስኪያጁ ካፊር(ክርስቲያን) ከሆነ ጠላታችን ስለሆኑ ወለዱን መውሰድ ይቻላል ብለው ያስተምራሉ። 6. ሴቶቻቸው ሻሽ ብቻ አድርገው ሱሪ ማድረግ ይችላሉ ይላሉ። ጂንስና ፋሽንንም ያበረታታሉ፡፡ 7. በሊባኖስ አገር የሙዚቃ ባንድ አላቸው ይህ ባንዳቸው ‹‹James last›› ይባላል፡፡ ዓመታዊ የሙዚቃ ድግስ ያደርጋሉ:: በዛ ላይ ሴቶችና ወንዶች በጋራ ይጨፍራሉ፡፡ 8. የአጅነቢ ሴትን ፎቶ፣ ቪዲዮ አልያም በመስታወት ውስጥ ራቁቷን እንኳ ብትሆን በስሜትም ቢሆን ማየት ይቻላል:: ከቁርአንና ሱና ተቃራኒ ሆነው የተከለከለው በዓይን በቀጥታ ማየት ብቻ ነው ብለው ያስተምራሉ፡፡ 9. ‹‹ሪፋዒ›› የተሰኘ ጦሪቃን ያስፋፋሉ:: በኢትዮጵያ ጀምረዋል ይህ ጦሪቃ ከሺዓ ጋር የሚያመሳስለው ብዙ እምነት አለው፡፡ የኢትዮጵያ ሙስሊም ግን ሱኒ ነው፡፡ 10. እምነት በልብ ነው ባይሰግዱም ኢባዳ ባይሰራም አንዴ አመንኩ ማለት በቂ ነው ብለው ያስተምራሉ:: (መጽሀፍ አ-ደሊል አልቀዊም፣ ገጽ 7) 11. ተከታዮቻቸው በአሜሪካና ካናዳ የቂብላ አቅጣጫ ካልተቀየረ ብለው ረብሻ ፈጥረዋል፡፡ በመጨረሻም ከመስጊድ ሲባረሩ የራሳቸው መስጊድ በተለየ ቂብላ ላይ ሰሩ። አሁን ከሙስሊሙ በተለየ ቂብላ ነው መስጊዳቸው፡፡ 12. ድግምትን አይቃወሙም። ራሳቸውም ይፈፅማሉ፡፡ ለሲህር የሚጠቀሙበት ‹‹ሁቡብ አል-አሀብ›› ብለው የሚጠሩት ነገር አላቸው፡፡ 13. ቁርኣን የጂብሪል ቃል እንጂ የአላህ ቃል አይደለም ብለዋል። የአላህ ቃል አይፃፍም ይላሉ፡፡ 14. የሚገርመው ይህን ሁሉ የጥመት መንገድ እየተከተሉ ሱፊያ ነን፣ ሻፊዒ መዝሀብ ተከታይ ነን ይላሉ፡፡ 15. ከነርሱ እምነት ዉጭ ያሉ ዓሊሞችን እንደያስተምሩ ሆን ብለው ያስተጓጉላሉ፣ ይደበድባሉ፣ ያሳስራሉ፣ ያውካሉ፣ በአንድ ወቅት በሊባኖስ ይህ ችግር በስፋት ፈጥረው ‹‹ሸሪዓ መጽሔት›› በቁጥር 574 እትሙ ‹‹ሊባኖስ ጦርነት በመስጂዱ ውስጥ›› በሚል ርዕስ ጽሑፍ አስነበቦ ነበር፡፡ 16. ዓመታዊ የሴቶቻቸው የሂጃብ ፋሺን ሾው አላቸው፡፡ በዚያ ላይ ሂጃብ ከሚለብሱት ሴቶች ጋር በጋራ ይጨፍራሉ፡፡ የአህባሽ ስውር አጀንዳዎችPosted: October 9, 2011 in መግቢያ የአህባሽ ጉዳይ በኢትየጲያችን አነጋጋሪ አጀንዳ ከሆነ ሰንበትበት ብሏል ። በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃንም ስለዚህ ጀመዓ ብዙ ብዙ ተብሏል ። አነጋጋሪነቱም ያለምክኒያት አይደለም ። ከአስተሣሠብ እስከ ሥነምግባር ፤ ከእምነት እስከ ማህበራዊ ኑሮ ግንኙነት በእጅጉ የወረደ አመለካከትና አስተምህሮ ያለው አህባሽ በህዝቡ መካከል ማረፊያ ቢያገኝ ሊያደርሰው የሚችለው ጥፋት ከፍተኛ ይሆናል የሚለው የብዙዎች ስጋት ነው ። አህባሽ እንከኖቹ ብዙ ናቸው ። ትኩረቱና መሠረቱ ከተውሂድ ይልቅ ወደ ሽርክ ( በአላህ ማጋራት ) እና ወደ ሸርክ የሚያደርሱ መንገዶች ያዘነበለ ነው ፤ ጥርት ካለው የቁርኣንና የሀዲስ ትምህርት በበለጠ ወደ ፍልስፍና እና መሠረት አልባ ቂሣዎች (ትረካዎች) ያደላል ፤ ከፍቅርና ከመደጋገፍ ይልቅ በማህበረሰቡ መካከል ጥላቻን ፣ ምቀኝነትንና ውጥረትን ያራምዳል ፤ ከሱ ውጭ ያሉትን ሁሉ የማክፈር (ከእስልምና የማስወጣት) ፖሊሲውና ‘ ለመቻቻል ወኔ የከዳው ስብስብ ’ መሆኑ ሲታሰብ ደግሞ የአህባሽ ጀመዓን አደገኛነትና የአስተሣሣቡን መርዛማነት አጉልቶ ያሣያል ። በመሆኑም ይህ ጉዳይ እጅግ አሣሣቢ ነው ስላመንበት በዛሬው የአጀንዳ አምዳችን የተለያዩ መረጃዎችን በማገላበጥ ስለዚህ ጀመዓ ምንነት በሚከተለው መልኩ አጠናቅረናልና ተከተሉን ። የኋላ ታሪክ ዛሬ የምናነሣት የዐብደላህ አልሀረሪ (አልሀበሺ) ጀመዓ የቅርብ ጊዜ ታሪክ ነው ያላት ። በምድር ላይ የሃምሣ አመት እድሜ እንኳን አልሞላትም ። የተመረሠተችው በሊባኖስ ሲሆን መሥራቹም የኛው ሰው ናቸው ። ሙሉ ሥማቸው ዐብደላህ ኢብኑ ሙሀመድ አልሀረሪ (አልሀበሺ) ይባላል ። በሀረር ከተማ ከአደሬ ብሄረሰብ ነው የተወለዱት ። አልሀበሺ የዘር ሀረጋቸው ከቁረይሽ ጎሣዎች አንዷ ከሆነችው ከበኒ ሸይባህ እንደሚመዘዝ ይነገራል ። ተከታዮቻቸው እሣቸው ይዘው የመጡትን ዐቂዳ / እምነት / ታላቅነት ለማመልከት የዘራቸውን ታላቅነት ይጠቅሣሉ ። በሌላ በኩል ግን ይህንን ጉዳይ የማይጋሩ በርካቶች ናቸው ። ናቸው ቢባል እንኳ ከተከበረ ዘር መሆንንና መልካምነትን የሚያገናኛቸው ነገር አለመኖሩን በርካታ ምሣሌዎችን በመጥቀስ ማስረዳት ይቻላል ። የዚህ ኡመት ፈርዖውን በመባል የሚታወቀውና በነቢያችን ሰለላሁ ዐለይህ ወሠለም ዘመን ዋና የኢስላም ጠላት የነበረው አቡጀህል ከቁረይሽ ጎሣ መሆኑን ልብ ይሏል ። በቁርኣን ከባድ እርግማን የወረደበት አቡለሀብም ቢሆን የነቢያችን ሰላላሁ ዐለይህ ወሠለም አጎት የነበረ ስለመሆኑ አንዘንጋ ። ዐብደላህ አልሀበሺ በልጅነታቸው በሀረር ገጠራማ አካባቢዎች የዐረብኛ ቋንቋና የሻፊዒይን ፍቅሂ ተምረዋል ። ሌሎች ሃይማኖታዊ ትምህርቶችንም ከተለያዩ መሻኢኮች ቀስመዋል ። የማይጨበጠው አቋማቸው ዐብደላህ አልሀበሺ ከወጣትነት እስከ ሽምግልና በዘለቀው የህይወት ዘመናቸው አንድ አይነት አቋም ይዘው ሲጓዙ አልተስተዋሉም ። ለበርካታ ጊዜያት በሱፊያ አመለካከቶችና መንገዶች ውስጥ ሲወጡና ሲገቡ ቆይተዋል ። ሀረር እያሉ ቃዲሪያ የሚባል ጠሪቃ መንገድ ተከታይ ነበሩ ። ወደ ጅማ ሲሄዱ ደግሞ ቅልጥ ያሉ ቲጃኒ እንደነበሩ ይነገራል ። ከዚህም በተጨማሪ በየጊዜው የሚፈፅሟቸው ድርጊቶች ለብዙዎች ግራ የሚያጋቡ ነበሩ ። ሼክ አህመድ አድደውለዊ ስለሣቸው ያዩትን ሲናገሩ ‘ይህ ሰው በአንድ ወቅት ጅማ ሄዶ ሲመለስ በቲጃኒ ጠሪቃ ላይ ተመስርቶ አላህን የሚያወሣበት መስገጃው ላይ ተቀምጦ በዙሪያው ስድስት ሲጃዳዎች አንጥፎ አየሁት ። ስለዚህ ሁኔታ ተጠይቆም አንደኛዋ ሲጃዳ ለነቢዩ ናት ፤ ሁለተኛዋ ደግሞ ለኢማም አህመድ አትቲጃኒ ስትሆን የቀሩት አራቱ ደግሞ አውራዱ (አላህን ማውሣቱ) ላይ ይገኛሉ ተብለው ለሚጠበቁት ለአራቱ ኸሊፋዎች እንደሆኑ ተናግሯል ። አልሀበሺ ሀረር ተመልሰው ጥቂት እንደቆዩ ግን ይህን ጠሪቃ ተው ። ቲጃኒዎችንም ማክፈር ጀመሩ ። ወደ ሊባኖስ ሲሻገሩ ደግሞ የሪፋዒ ጠሪቃ ተከታይ እንደሆኑና ከሌሎች የሚሻለውም ይሀው መንገድ እንደሆነ ያስተምሩ ነበር ። በሊባኖስ ቆይታቸው ጥመትና አልባሌ ነገሮች ከሞላባቸው ከተለያዩ የፍልስፍና መንገዶች የተለያዩ አመለካከቶች መቅዳትና መገልበጥ ያዙ ። ውርሣቸውም ይህን ይመስላል – በኢማን / እምነት/ ጉዳይ ላይ ከኸዋርጆች (አፈንጋጮች) ጋር በማበር ሙስሊሞችን ማክፈር ጀመሩ ። ጀህሚያ እና ሙዕተዚላ ከሚባሉ ጀመዓዎች ደግሞ ደግሞ የአላህን መልካም ሥሞችና ባህሪዎች በመቁረጥ አሊያም በመቀጠል ለቁርኣን አንቀፆች ያልሆነ ትርጉም መስጠትን ወረሡ ። ከሺኣዎች ደግሞ እነ ሙዓዊያን እና ዐምር ኢብኑልዓስን ጨምሮ ታላላቅ ሰሃቦችን የመስደብ ትልቅ ወንጀል ተጋሩ ። ከአህለልኪታቦች ደግሞ በተወሱል ሰበብ መቃብር ለመቃብር አማላጅ ፍለጋ መንከራተትን በትምህርታቸው ውስጥ አካተቱ ። ሸኹ እንዲህ የተሠባጠረ አካሄድ የሚከተሉ ከመሆናቸው የተነሣ የሣቸው መንገድ ይህ ነው ብሎ በግልፅ ለማስቀመጥ ይቸግራል ። አመለካከታቸው ሸኽ ዐብደላህ አልሀበሺ ከትንሽነታቸው ጀምሮ በባህሪያቸው አስቸጋሪ ሰው እንደነበሩ ይነገርላቸዋል ። ትክክል ነኝ ብለው ባመኑበት ነገር ከሸኾቻቸውና አስተማሪዎቻቸው ጋር ክርክር በመውደድ ይታወቃሉ ። በዚህም የተነሣ በየጊዜው ከሚያስተምሩዋቸው ሸኾች ጋር ውዝግብ ውስጥ ይገቡ ነበር ። ሰላትን ማንንም ተከትሎ ለመስገድ ፈቃደኛ አይደሉም ። ከሰዎች ጋር ላለመስገድ ሲልም ሰላታቸውን ያዘገዩ ነበር ። ከዚህም በላይ ሰዎች በሰላትና በቂርኣት በጥንቃቄ እንዲጨናነቁ ያስገድዳሉ ። የገዛ ሸኻቸውን ጭምር ተከትለው የማይሰግዱ ሲሆን ክስተቱም አንድን ሙስሊም ለማነወርና ለማክፈር ዳርዳርታውን የጀመሩበት ወቅት ነበር ። ላለመስገድ እንደምክኒያትነት ያቀርቡ የነበረውም ኢማማቸው በዐረቢኛ የፊደል አወጣጥ (መኻሪጀልሁሩፍ ) ላይ ችግር አለባቸው የሚል ነበር ። በወቅቱ ከተማሪያቸው ይህን ያስተዋሉት ሸህም ‘ ይህ ሰው ወደፊት የፊትና ሰው ( ሰዎች በሱ የተነሣ የሚወዛገቡበት ) ነው የሚሆነው ።’ እስከማለት ደርሰዋል ። ዘግይቶም ቢሆን የሸኹ ትንበያ የሠመረ ይመስላል ። ዛሬ ዓለማችን እሣቸው ባመጡትና ከአራቱም መዝሀብ ውጭ በሆነው አዲስ አመለካከት ችግር ውስጥ የገባች ስትሆን በዋናነት ደግሞ ያደጉባት ሀገር ሊባኖስ ትልቅ ፈተና ውስጥ ናት ። ሸሁ የዛሬ ሁለት አመት አካባቢ ይህችን ዓለም በሞት ቢሰናበቱም የለኮሱት ፊትና ግን ዛሬም ከሀገር ሀገር እየዘለለ ነው ። ሸኹና ተከታዮቻቸው ብዙ ክርስቲያኖች ሺዓዎችና የተለያዩ አልባሌ እምነት ተከታዮች በሚገኙባት በዚህች ሀገር እግራቸውን ሊያቆሙ የቻሉት ለሱና ሰዎች ባላቸው ጥላቻ የተነሣ ከምእራባውያን ፣ ከሺዓዎችም ሆነ ከሌሎች የኢስላም ጠላቶች ከፍተኛ ድጋፍ ስለሚደረግላቸው ነው ይባላል ። ማክፈር … ትልቁ መፈክር ዐብደላህ አልሀበሺ ለማንኛውም ‘ ይቃወመኛል አሊያም አመለካከቴን አይጋራም ’ ብለው ባመኑት ሰው ላይ ረጅም ምላሣቸውን ለመልቀቅ ወደኋላ አይሉም ። እሣቸውም ሆኑ ተከታዮቻቸው አንድን ሰው ለማክፈር እጅግ ሲበዛ ችኩሎች ናቸው ። በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የሚገኙ ሱፊዮች እስከዛሬ ድረስ ሰውን ሲያከፍሩ አልተስተዋለም ። አሁን የአህባሽ አመለካከት ከመጣ ወዲህ ግን እነሱም ወደማክፈር ገብተዋል ። ዐብደላህ አልሀበሺ ‘ አትተዓዉን ዐላ ነህይ ወልሙንከር ’ ( በመጥፎ ነገር ላይ መረዳዳት ) በሚለው ኪታባቸው ላይ እንደፃፉትም ከትላልቅ ዓሊሞች ውስጥ የሚያስቀሩት ጥቂቶችን ብቻ ነው ። ኪታባቸው ከመጀመሪያ እስከመጨረሻ ተህዚር ! ተህዚር… ! ተጠንቀቁ ተጠንቀቁ .. ! በሚል ማስፈራሪያ የተሞላ ነው ። ካለፉትም ይሁን በህይወት ካሉት ዑለማኦች ፣ ዳዒዎችና የኢስላም ተንታኞች ውስጥ ሰዎች ሊሸሿቸው የሚገባቸውን አንድ በአንድ ይዘረዝራሉ ። ዓሊሞቹ የተናገሯቸውን ቃላት በመምዘዝም ‘ እገሌ በአንድ ወቅት እንዲህ ብሏል እገሌም እንዲህ ብሏል … እያሉ እራሣቸውን የዚህች ዓለም ብቸኛ ነቢይ አድርገው የማስቀመጥ ያህል ይፈርዳሉ ። ሲሻው ይሣደባሉ ፤ ካልሆነም ይራገማሉ ፤ ባስ ካለም ያከፍራሉ ። ስድባቸውን የሚጀምሩት ከታላቁ ሰሃባ ከሙዓዊያ ኢብኑ አቢሱፍያን ነው ። ስለ ዐምር ኢብኑል ዓስና ስለ እናታችን ዓዒሻም የሚሉት አላቸው ። ይህም ያለ አንዳች ኤዲቲንግ (ማስተካከያ) ከሺዓዎች የገለበጡት ቀጥተኛ የሆነ አቋማቸው እንደሆነ ብዙዎች ይስማሙበታል ። ከሰለፍ ዑለማኦች እነ ዳርሚይንና ኢብኑ ኹዘይማህን ወርፈዋቸዋል ። የተውሂድ አቀንቃኙ ኢብኑ ተይሚያህ ዋና ጠላታቸው ሲሆኑ ‘ ካፍር (ከሀዲ) ፤ ሙርተድ (ከኢስላም ወደ ክህደት የተመለሠ )’ በማለት ይገልጿቸዋል ። በተገኙበት ሁሉ ኪታቦቻቸው እንዲቃጠሉ አዘዋል ። የኢብኑ ተይሚያን ተማሪ ኢማም ኢብኑ አልቀይም አልጀውዚን እና ታላቁን ሙፈሲር (የቁርኣን ተንታኝ) ኢብኑ ከሲርንም አክፍረዋል ። ኢማም ዘሀቢን ኸቢስ (መጥፎ) ሲል ይዘልፏቸዋል ። ታላቁ የሀዲስ ሰው ሸይኸ አል አልባኒ ፣ የሳዑዲ ሙፍቲ የነበሩት ሸኽ ኢብኑ ባዝና ታላቁ ዓሊም ኢብኑ ዑሰይሚን እንዲሁም የወቅቱ የዓለም ሙስሊም ዑለማኦች ዋና ፀሃፊ የሆኑት ሸኽ ዶ/ር ዩሱፍ አል ቀርዳዊም በካፍርነት ከተፈረጁ መካከል ናቸው ። ሰዎች እንዲጠነቀቋቸው ከፃፉባቸው ሌሎች ሰዎች መካከል ታዋቂው ዳዒ ዶክተር ዐምር ካሊድ ፣ ፈይሰል መውለዊ ፣ ፈትሂ የኩን የመሣሠሉት ሲገኙ ዓለም አቀፍ እውቅና ያላቸው ምሁራን ይገኙባቸዋል ። የሱፊያው መሪ ሸኽ ሙሀመድ ሰዒድ አልቡጢ ውግዘቱ ተርፎአቸዋል ። ዶክተር ዛኪር ናይክና የፒስ ቲቪ ባልደረቦቹም በክህደት ከተወነጀሉት ውስጥ ናቸው ። አልሀበሺ ታላቁን የፍቅሂ ሰው ሰይድ ሳቢቅን መጁሲ /እሣት አምላኪ/ ሲል ይገልጿቸዋል ። ሰይድ ቁጥብን ከመራገም አልፈው እሱንና ተከታዮቹን በስቅላት በመግደሉ ለጀማል አብዱናስር ታላቅ አድናቆት አላቸው ። የስደቱ ምክኒያት ‘ አልሀበሺ አክጣኡሁ ወሹዙዙሁ /አልሀበሺ ስህተቶቹና ድልጠቶቹ / ’ የምትለውና በዐብዱረህማን አድ ድመሽቂያህ የተዘጋጀችው ትንሽ መፅሃፍ አንደምታትተው ከሆነ አልሀበሺ ከትውልድ ሀገራቸው ኢትዮጰያ ሸሽተው የወጡት በሀረር ሙስሊሞች መካከል ውዝግብ በማስነሣታቸው ነበር ። በወቅቱ የሀረር ገዠ ከነበሩት የሃይለሥላሴ አማች አንዳርጌ ጋር በመተባበር በሀረር የሚገኙ የቁርኣን ሂፍዝ ማዕከላትን ማስዘጋታቸውም ተነግሯል ። ጊዜውም በ1940 ዓ.ል ነበር ። በወቅቱ ወደ ተውሂድ ጥሪ የሚያደርጉ ዑለማኦች በአልሀበሺ ውንጀላ ከፍተኛ መንገላታታ የደረሠባቸው ሲሆን በርካቶች ወደ ግብፅና ሳዑዲ ዐረቢያ በመሰደድ ህይወታቸውን ሲያተርፉ የተቀሩት ደግሞ እንዲታሰሩና በጨቋኙ መንግስት እንዲዋረዱ ተደርጓል ። ሰዎችንም የሚያሣስሩበት ዋና ምክኒያትም ዛሬም ተከታዮቹ እንደሚወነጅሉት ‘ ወሃቢያ ነው ’ በማለት ነበር ። ሆኖም ግን ኋላ ላይ ተነቅቶባቸው እራሣቸው የለኮሱት እሣት ሊፈጃቸው እንደሆነ ሲረዱ የታሠሩና የተገደሉ ሰዎች ቤተሰቦችን በቀል በመፍራት ከሀጃጆች ጋር በመሆን በሶማሊያ በኩል አድርገው ሣዑዲ ሊገቡ ችለዋል ። ሸሁ ቀጥለውም ወደ ሀገረ ኢስራኤል ኋላም ወደ ሶሪያ በመሻገር በመጨረሻም ሊባኖስን ማረፊያቸው አደረጉ ። በሊባኖስ ቆይታቸውም ዓሊም መስለው በመቅረባቸው ብዙዎች በሣቸው ተታለዋል ። መጀመሪያ አካባቢ የተለያዩ አንዳንድ መፅሃፎችን በማረም ወደ ማህበረሰቡ ውስጥ ገቡ ። ቀጥሎም ለየት ያለ አዲስ አመለካከታቸውን ማስተዋወቅ ያዙ ። ተውሂድ ይዞ የነበረውን ህዝብም ወደኋላ አንሸራተቱ ፤ በፍቅር ይኖር በነበረው ማህበረሰብ መካከል ፍትናን በማሠራጨት ጥላቻን በመንዛታቸውም አንድነታቸው ተበተነ ። ሀይላቸውም ተዳከመ ። ቁጥራቸው ስንት ይሆን በዓለም ላይ የአህባሽ ተከታዮች ቁጥር ከ250 ሺህ እንደማይበልጥ ይገመታል ። የዓለም ሙስሊሞች ቁጥር ወደ ሁለት ቢሊዮን የተጠጋ ሲሆን በነሱ እይታ ከነሱ ውጭ የሆነው ሙስሊም ሁሉ ካፍር በአላህ ያላመነ ከሀዲ ነው ማለት ነው ። እስልምናቸውም ትክክል ስላልሆነ እንደገና ሸሃዳ እንድይዙ ይመክራሉ ። አህባሾች በእምነት ጉዳይ ከሺዓዎች የሚጋሯቸው በርካታ አመለካከት ያሏቸው ሲሆን ህዝቡላህን ከመሣሠሉ በኢራን ከሚደገፍ ፓርቲም ትልቅ ድጋፍ ያገኛሉ ። የሱና ጀመዓዎችን ለመቃረን ሲሉ ብቻ ከጥመትና ከኩራፋት ጀመዓዎች ጋር ፍቅራቸው እጅግ የጠነከረ ነው ። መሪዎቻቸውም ሆኑ ተከታዮቻቸው በስሜት የሚነዱ ፣ ለጥቅም ያደሩ ፣ ሥነምግባርና ዘመናዊ እውቀት የጎደላቸው ናቸው ። የሚያንቀሳቅሷቸው ድብቅ የሆኑ የሙስሊሙ ጠላት እጆች እንዳሉባቸው የብዙዎች ግምት ነው ። ሱፍያ ፣ አል አሽዐሪይ ፣ ኢማሙ ሻፊዒይና አህባሽ አህባሾች ‘ ሱፊዮች ነን የኢማም አሽ ሻፍዒና የአሽዓሪይ መዝሀብ ተከታዮች ነን ቢሉም አመለካከታቸው በብዙ መልኩ ከነሱ የተለዩ ነው ። ሱፊዮች ሙስሊሙን ሲያከፍሩ በታሪክ አልታየም ። ‘ ቁርኣን የአላህ ንግግር አይደለም ’ አይሉም ። ከመካና መዲና ኢማሞች ኋላ እንዳይሰገድም ብይን አያስተላልፉም ። ከካፍሮች (ከሀዲያን ) ጋር አብረውም ሙስሊሙን አይበድሉም ። ከነቢዩ ሰለላሁ ዐለይህ ወሠለም ሰሃቦች አንዱን እንኳ አይሰድቡም ። እነሱ ‘ እንከተላቸዋለን ’ የሚሏቸው ኢማሙ ሻፊዒይም ከአካሄዳቸው ፍፁም የጠሩ ናቸው ። ኢማሙ በቀደምት ሰሃቦች መካከል ስለተፈጠረው ልዩነት ደፍረውና አፋቸውና ሞልተው ለመናገር አላህን ይፈራሉ ፤ ኢማሙ ሻፊዒይ ‘ ያች በርግጥም ትልቅ ፈተና ናት ። አላህ ሱብሃነሁ ወተዓላ ከሷ እጃችንን አጥርቶልናል ። ታዲያ ምላሣችንን ማጥራት አይጠበቅብንም ’ ሲሉ በቀደምት ሰሃቦች ውስጥ የተከሰተውን ነገር ከመተንተን ይቆጠባሉ ። ኢማሙ ሻፊዒይ ሪባን /ወለድን / ም ሆነ ሰው ማጭበርበርን አይፈቅዱም ፣ ዘካን ከእስልምና አላስወጡም ፣ ለአላህ ባህሪያት ያለትርጉማቸው ትርጉም አልሠጡም ። ዋና ዋና አመለካከት v ቁርኣን የመልአኩ ጅብሪል እንጂ የአላህ ንግግር አይደለም ይላሉ ። ቁርኣን የአላህ ንግግር ስለመሆኑ የሙስሊሞች ሁሉ እምነት ነው ። v በነሱ ጥላ ሥር ያልተጠለለውን ማንኛውንም ሙስሊም ሁሉ ካፊር ነው ይላሉ ። እውነተኛ ሙስሊም ማለት የነሱን አካሄድ የተከተለ አመለካከታቸውን የተጋራ ነው ። ከሀዲ ማለትም ከነሱ መንገድ የወጣ ነው ። አመለካከታቸውን ያልተቀበለውን ሙስሊም ስለሚያከፍሩ ተከትለውት አይሰግዱም ። ማክፈር በነሱ ዘንድ እጅግ ቀላል ነገር ነው ። አንድ ካፊር ያልሆነውን ሙስሊም ወንድሙን ካፊር ያለ ሰው ንግግሩ ወደሱ ተመላሽ እንደምትሆን ነበያችን አስተምረውናል ። v ‘ የሀረም ( የመካና መዲና ) ኢማሞችን ተከትሎ መስገድ ሀራም ነው’ ይላሉ ። ለሀጅ የሚሄድ ሰው እነሱን ተከትሎ መስገድ የለበትም ቢሰግድም ሰላቱ ትክክል አይደለም ብለው ያምናሉ ። ኢማማቸው አልሀበሺ ይህንን ያደረጉ እንደሆነ ደግመው እንዲሰግዱ ያዛቸዋል ። ለምን ቢባል በነሱ አመለካከት የሀረም ኢማሞች ከሀዲዎች ናቸውና ነው ። በዚህ አይነት በርካቶችን የሀረም ተስግዶ የሚገኘውን ከፍተኛ አጅር አሣጥተዋል ። v የአላህን መልካም ባህሪያትና ሥሞች መካዳቸው ሌላው ነው ። አላህ ስለራሱ የተናገራቸውን ነገሮች ትርጉሙን በማጣመም ይተረጉማሉ ። ሲሻቸው ይቀንሣሉ ባሰኛቸውም ጊዜ ይጨምራሉ ። ቀደምት ሰለፎችና በተዋረድ እነሱን የሚከተሉ ሙስሊሞች ግን አላህ ሱብሃነሁ ወተዓላ ስለራሱ በተናገረው መልኩ ያምናሉ ። እርሱ ለራሱ ያፀናውንም ባህሪ በሚገባው መልኩ ያፀናሉ ። v ሀጃቸውን ለማስፈፀም መቃብር አካባቢ ይመላለሣሉ ። ሙታኖች ሰዎችን ይረዳሉ ፣ ያግዛሉ ፣ ከጭንቅም ያላቅቃሉ የሚል እምነት አላቸው ። ከዚህም የተነሣ የአላህን በር ችላ በማለት ውሎአቸውን ደሪህ ካባቢ ያደርጋሉ ። የአላህ ወሊዮች ከመቃብር ወጥተው የሰውን ጉዳይ ፈፅመው የመመለስ ብቃት አላቸው የሚል እምነት አላቸው ። ከአላህ ሱብሃነሁ ወተዓላ ሥምም በላይ የወሊዮቹ ሥም ሲጠራ ይበረግጋሉ ። v በዲን ውስጥ አዲስ ፈጠራን /ቢድዓን/ ያበረታታሉ ። ‘ መልካም ነገር እስከሆነ ድረስ ቢጨመርበት ግድ የለውም ’ በማለት ከሃይማኖት አስተምህሮ ውጭ የሆኑ ነገሮችን ይጨማምራሉ ። በዚህም የተነሣ አምልኮአዊ ተግባራቶቻቸው ከነቢዩ ሱናዎች ይልቅ በሌሎች መጤ ፈጠራዎች የተጥለቀለቁ ናቸው ። v ኢማን ማለት የውስጥ እምነት ነው በሥራ ባይገለፅም ችግር የለውም የሚል አቋም አላቸው ። በመሆኑም በሸሪዓ ህግጋት ለመሥራት የተሠላቹ ናቸው ። ለሀላል ሀራሙም ነገር ግድ የላቸውም ። ይህም በመሆኑ በምድር ላይ የአላህ ህግ ተግባራዊ እንዳይሆን የሚፈልጉ በእጅጉ ይደግፏቸዋል ። ትክክለኞቹ ሙስሊሞች ግን ኢማን ማለት በቀልብ ውስጥ የሰረፀና በተግባርም የሚረጋገጥ ጉዳይ እንደሆነ ያምናሉ ። v ከአራተኛው ኸሊፋ ዐሊ ኢብኑ አቢጣሊብ ጋር በሀሣብ የተለያዩትን ሰሃቦችን እነ ሙዓዊያን እና ዐምር ኢብን አልዓስን ‘ ከአላህ ተእዛዝ የወጡ ናቸው ’ በማለት ይወርፏቸዋል ። ይህም የሺዓን አመለካከት የሚጋሩ መሆናቸውን አመላካች ነው ። በሊባኖስም ከሺዓዎች ጋር በመተባበር የሱና ጀመዓዎችን ሲያሣድዱ ይስተዋላል ። v አልሀበሺና ተከታዮቻቸው ከአመለካከታቸው ውጭ የሆኑትን ሙስሊሞች በመጥላት በመመቅኘትና እንዲሁም ሰሃቦች በመዳፈርና በመሣደብ ይታወቃሉ ። ይህም በመሆኑ በሊባኖስ ውስጥ ተስማምቶ ለመኖር የማያመች ወጣ ያለ የቁጣ ባህሪ ያለው ሰው ካጋጠመ የአል ሀበሺ ተከታይ እንደሆነ ይገመታል ። በሀገራችንም ውስጥ የምናየውም ሥራቸው ሰዎች ያላሉትን አሉ በማለት ትናንሹን ጉዳይ በማካበድ አንዳቸውን በሌሎች ላይ በማነሣሣት ነው ። ከአስገራሚ ፈትዋዎቻቸው በነጃሣ መስገድ ችግር የለውም ። ወለድ መብላት ይበቃል ። ሙስሊም ካልሆነ /ካፍር/ ጋር ቁማር ተጫውቶ መብላቱ ችግር የለም ። ችግር እስካልተፈራ ድረስ ። ሴትን ልጅ በተደጋጋሚ ማየቱ ነው እንጂ የሚከለከለው በመጀመሪያ እይታ ለረጅም ጊዜ ማየቱ ይበቃል ። ሴት ልጅ በየትኛውም ጊዜ ያለባሏ ፈቃድ ሽቶ ተቀብታና ተኳኩላ መውጣት ትችላለች ። ኢክቲላጥ /የሴቶችና ወንዶች ቅልቅል/ ችግር የለውም ። ለዚህም ሲባል ተከታዮቻቸው የሆኑ ወንድና ሴቶች ተቀላቅለው ይጨፍራሉ ። ሙስሊም ወዳልሆኑ ሀገሮች የሚሄድ ሰው ችግር ይገጥመኛል ብሎ የሚፈራ ከሆነ መስቀል ማንጠልጠል ይችላል ። ዘካ በወርቅና ብር እንጂ በወረቀት ገንዘብ ግዴታ አይሆንም ። ሆን ብሎ መዘግየትና መስነፍ ችግር የለውም ። ለምሣሌ ጁሙዓና ጀመዓ ላለመምጣት የፈለገ ሰው ነጭ ሽንኩርት መብላት ይችላል ። መኻሪጀልሁሩፍ /የዐረብኛ ቃላትን በትክክል ማንበብ ማይችሉ/ አሰጋጆችን ተከትሎ መስገድ አይበቃም ። ለሴት ልጅ ከላይ ሂጃብ እስከለበሠች ድረስ ከታች ጠባብ ጂንስ ብትለብስም ችግር የለውም ። በአንድ ወቅት በአህባሽ ብይን የተነሣ በአሜሪካና ካናዳ የሚገኙ ሙስሊሞች ከከዕባ አቅጣጫ 90 ድግሪ ያህል ዞረው ሰግደው ነበር ። ይህ ነው እንግዲህ ከእስልምና አስተምህሮ ወጣ ያለው ጥፋታቸውና አስቀያሚ አካሄዳቸው ። ልብ ያለው ልብ ይበል ። አደገኝነታቸው የአህባሽ አመለካከት ወደ አንድ ሀገር አይደርስም የሚከተሉት ነጥቦች ቢከተሉት እንጂ የሰዎች ለሰዎች ማህበራዊ ግንኙነት ይበላሻል ፣ የሙስሊሙ አንድነት አደጋ ውስጥ ይገባል ፣ ሽኩቻ ጥላቻና ውጥረት በመካከላቸው ይነግሣል ። ሙስሊሞች መሣቂያ መሣለቂያ ይሆናሉ ። በምእመናን መካከል መተሣብና መተዛዘን ይጠፋል ፣ አሉባልታና የውሸት ወሬ ይስፋፋል ። ከሱና ይልቅ ቢድዓ ቦታ ያገኛል ፣ ከቁርንና ሀዲስ በበለጠ መሠረተ ቢስ ታሪኮችና ትረካዎች /ቂሳዎች/ ይገናሉ ፣ ከታላቁ ነቢይ ሥም በላይ የወሊዮችና የሸሆች ሥሞች ይዘወተራሉ ። የአላህ የአንድነት ትምህርት ይሸረሸራል ሽርክና ወደ ሽርክ የሚያደርሱ መንገዶች ክፍት ይሆናሉ ፤ ተውሂድ በሽርክ ይተካል ፣ ንቃት በመሃይምነት ይተካል ፣ ብስለት በስሜታዊነት ፣ እዝነት በጭካኔ ፣ መተማመን በጥርጣሬ ፣ መቻቻል በብጥብጥ ይተካል ፣ ሚዛናዊነት በአክራሪነት ፣ አርቆ አስተዋይነት በችኩልነት ይተካል ። ከዚህም ባለፈ ሂጃብ በሱሪ ይተካል ፣ ቁርኣን በተለያዩ ሀድራዎችና ሙዚቃዎች ይተካል ። መናፍቃን ቦታ ያገኛሉ ፣ የሱና ሰዎች ይጠላሉ ፣ በኢስላም ሀግጋት ለመሥራት ደፋ ቀና የሚሉ ‘ አክራሪ ፣ አሸባሪ ’ ይባላሉ። አለማቀፍ ዓሊሞች ምን ይላሉ ከተለያዩ ሀገራት የተውጣጡ ከሱፊያም ሆነ ከሌላ ጀመዓ የሆኑ የአራቱ መዝሀብ አለማቀፍ እውቅና ያላቸው የዘመናችን ዓሊሞች ከዚህ ጀመዓ በማስጠንቀቅ ረገድ አንድ ሆነዋል ። v አብዛኛዉ ዓሊሞቹ በሱፊያ መዝሀብ ላይ የሚገኙት የግብፁ ታላቁ ኢስላማዊ ተቋም አል አዝሀር እነሱን አላውቃቸውም ብሏል ። ጠማሞች ስለመሆናቸውም በተደጋጋሚ ገልጿል ። የአዝሀር ዩኒቨርስቲ ዳይሬክተር አህመድ ዑመር ሃሽም ‘ ይህ ጀመዓ በቁርኣንም ሆነ በሀዲስ የማይመራ ነው’ ብለውታል ። v የሊባኖሱ ሙፍቲ ሸኽ ኻሊድ ሀሠን ከሀገሪቱ መንግስት ርእሰ ብሄር ረሺድ ከራሚ በአንድ ወቅት ዐብደላህ አልሀረሪ ከሀገር ወጥቶ በነበረበት ወቅት በሱና ሰዎች ላይ በሚያደርገው አደገኛ አካሄድ የተነሣ ወደ ሀገር ወስጥ እንዲገባ እንዳይፈቀድለት ጠይቀው የነበረ ሲሆን ለጥቂት ጊዜ ታግዶ ነገር ግን በተለያዩ ምእራባውያን ሀገራት ግፊት የተነሣ ሊገባ ችሏል ። v የግብፁ ሙፍቲ ዶክተር ዐሊ ጁሙዓ ‘ ሥሙ ዐብዱላህ አልሀረሪ አልሀበሺ የሚባል ሰውየመሠረታት ይህች ጀመዓ ውስጣዊና ውጫዊ ገፅታም አላት ። ውጫዊ ገፅታዋን ስናይ በፍቅሂ የሻፊዒይ መዝሀብ ተከታይ ፣ በዐቂዳ ደግሞ አሽዐሪን ይመስላሉ ። ውስጣዊ ተልእኮዋ ግን ያላግባብ ሙስሊሞችን ማክፈር፣ ምእመናን ያላግባብ መወንጀልና በሀዝቦች መካከልል ውጥረትና ውዠንብር መፍጠር ነው ። ለዱኒያዊ ጥቅም ሲሉም ለኢስላም ጠላቶች ይሠራሉ ። ብለዋል ። v በአውሮፓ የሙስሊም ኮሙኒቲ ሙፍቲ የሆኑት ዶክተር ፈይሰል መውለዊ ‘ የዐብደላህ አልሀረሪ ተከታዮች የሆኑት አህባሾች በጥቃቅን ነገሮች ሙስሊሙን ዑለማ የሚያከፍሩ ፤ አብዛኞቹ የሰለፍ ዑለማኦች የማይጋሯቸው የሆኑ የራሣቸው የሆነ አመለካከት /ዐቂዳ / ያላቸው ቡድኖች ናቸው ። ከሸኻቸው ውጭ ስለማይቀበሉ ከነሱ ጋር መነጋገር ጥቅም የለውም ። ከነሱ ጋር ላለመከራከር መስጅዳቸውን መሸሽ ይገባል ። ። እነሱ ከነሱ ውጭ የሆነውን ‘ ከሀዲ ነው ከነሱ በኋላ መስገድ አይበቃም ’ ብለው ቢያምኑም እኛ ግን ሙስሊሞች እንደሆኑና ከነሱ ጋርም ሆነ ተከትለዋቸው መስገዱ ይበቃል የሚል እምነት አለን ። v የዓለም ሙስሊም ዑላማኦች ፕሬዚዳንት የሆኑት ዶክተር ሼከ ዩሱፍ አልቀረዷዊም ‘ እነሱ የሚወክሉት የተወሰነ የማህበረሰብ ክፍል ብቻ ነው ። የሙስሊሙን የጋራ አቋም /ኢጅማዕ/ በመጣል ተለይተው የወጡ ናቸው ። የሙስሊም ዑላማኦችን አክፍረዋል ። አህባሾች በጥመት ውስጥም በጣም የሰጠሙ ናቸው ። ኢማም ዘሀቢን ፣ ኢብኑ ተይሚያን ፣ ኢብኑልቀይምን ፣ ኢማም ገዛሊን ፣ ኢብኑ ዐብዱልወሃብን ፣ ኢብኑ ባዝን ፣ ሰይድ ቁጥብን አንዱንም ሣይተው አክፍረዋል ። መሃይማን ብቻ ሣይሆኑ ድርብ ድርብርብ መሃይሞች ናቸው ። ሁኔታቸው አላህ እንዳለው ነው “ ሰዎች እንዳመኑት እመኑ በተባሉ ጊዜ ሞኞች እንዳመኑት እናምናለን እንዴ! ” ይላሉ ። v የሶሪያው የሱፊያ ዓሊም የሆኑት ዶክተር ሙሀመድ ሰዒድ አልቡጢም ‘በበይሩት ዐብደላህ አልሀረሪ የሚባል ኢማም ያላቸው አህባሾች ወሃቢያን ተከትሎ መስገድ አይበቃም ፣ ኢብኑ ተይሚያ ካፊር ነው ይላሉ ። በመሠረቱ ወሃቢን ተከትሎ መስገድ ሀራም አይደለም ። ተከትሎ የሰገደም ሰላቱ ትክክል ናት ። አንድን ሙስሊም ማክፈር ይበቃም ሲሞት በኩፍር ላይ ሆኖ ስለመሞቱ ማረጋገጫ እስካልተገኘ ድረስ ። ስለሷ የምታነሱልኝ ጀመዓ ብዙ ሙስሊሞችን ያከፍራሉ ። ሙተወሊ ሸዕራዊን ቀርዷዊን እኔንም ያከፍራሉ ። ምናልባት ሙስሊሞች እነሱ ብቻ ሣይሆኑ አይቀሩም ።’ ብለዋል ። v በሊባኖስ የሙስሊም ጀመዓዎች ተጠሪ የሆኑት ፈትሂ የኩን ‘ ዐብደላህ አልሀረሪም ሆነ ድርጅቶቹ ቀደምት ሰለፎችና የዚህ ኡመት ሚዛናዊ አመለካከት ያላቸው ምሁራን የጋራ አቋም የያዙበትን ነገር የሚቃረኑ ናቸው ።’ ብለዋል ። v በኢስላማዊ ብይኖች የበላይ የሆነው የሰኡዲ ቋሚ የሆነው የእውቀትና የፈትዋ ኮሚቴ በአንድ ወቅት ‘ ዐብደላህ አልሀረሪ ኢስላምን አገለገለ ወይንስ አወደመው ? ’ ተብሎ በተጠየቀ ጊዜ እንዲህ በማለት መልስ ሰጥተዋል ። ‘ በሥም ተጠቃሹ እጅግ መጥፎ ሰው ነው ። በዘመኑ ካሉ የቢድዓና የጥመት መሪዎችም አንዱ ነው ። እሱም ሆነ ተከታዮቹ ሆንብሎ ነቢያችን ሰለላሁ ዐለይህ ወሠለም ሰሃቦችና ታቢዒዮች ያስተላለፉልን የሙስሊሞችን ቀደምት አመለካከት /ዐቂዳ / ለማጥፋት ቆርጦ የተነሣ ሰው ነው ። በፍቅሂ ዙሪያ የራሣቸው የሆነ አካሄድ አዘጋጅተዋል ከቁርኣንም ሆነ ከሱና ሰንሰለት በሌላቸው ለየት ባሉ እና በዘቀጡ አመለካከቶች የተሞሉ ናቸው ። በዐቂዳና በሥራ በኩል ከፍተኛ የሆነ ችግር አለባቸው ። የዚህን ኡማ ታላላቅ መሪዎች በማነወርም ይታወቃሉ ። ሁሉንም ሙስሊሞች ከነኚህ ጠማማ እና የተንሸራተተ ጀመዓ እንዲሁም ወጣ ካለ አመለካከታቸው እንዲጠነቀቁ እንመክራለን ።’ ብለዋል ። v ታላቁ የሀዲስ ሰው ሼኽ ሙሀመድ ናስረዲን አል አልባኒም ‘ አህባሾች የዐብደላህ አልሀረሪ ተከታዮች ናቸው ። አመለካከታቸው በአጉል ፍልስፍና ላይ የተመሠረተ ሲሆን ቁርኣንና ሀዲስን በዐቅላቸው በመመራመር እንጂ በሰለፎች ግንዛቤ ላይ አይረዱም ። ተጠቃሽ ምንጮች ﺑﻐﻴﺔ ﺍﻟﻄﺎﻟﺐ ﻟﻠﺸﺒﺦ ﻋﺒﺪ ﺍﻟﻠﻪ ﺍﻟﻬﺮﺭﻱ ﺍﻟﺤﺒﺸﻲ ﺃﺧﻄﺎﺀﻩ ﻭﺷﺬﻭﺫﻩ ﻋﺒﺪ ﺍﻟﺮﺣﻤﻦ ﺍﻟﺪﻣﺸﻘﻴﻪ ﺻﺮﺑﺢ ﺍﻟﺒﻴﺎﻥ ﻟﻠﺸﺒﺦ ﻋﺒﺪ ﺍﻟﻠﻪ ﺍﻟﻬﺮﺭﻱ ﻓﺮﻗﺔ ﺍﻷﺣﺒﺎﺵ ﺩ ﻋﻠﻲ ﺍﻟﺸﻬﺮﺍﻧﻲ Antihabashis.com, alsunnah. org qaradawi.net Bouti.com