ሙት-አሽኩር

ከውክፔዲያ

ሙት-አሽኩር አሞራዊው የአሦር ንጉሥ 1 እሽመ-ዳጋን ልጅና ተከታይ ነበረ።

በእሽመ-ዳጋን ዘመን የሑራውያን ጎሣ የቱሩካውያን ንጉሥ ዛዚያ በስምምነት ሴት ልጁን ለሙት-አሽኩር አጋባት። ሙት-አሽኩር ደግሞ በማሪ ንጉሥ ዝምሪ-ሊም ዘመን በተጻፉት ደብዳቤዎች ይታወቃል። ከደብዳቤዎቹ እንደምንረዳ በ1674 ዓክልበ. ግ. ልዑል ሙት-አሽኩር በኤካላቱም እየገዛ ዛቻ በጎረቤቱ በካራን (ፓዳን-አራም) ላይ ለመጣል ሲያስብ ፪ ሺ የራሱን ወታደሮችና ፪ ሺ የባቢሎን ወታደሮች ነበሩት፣ ተጨማሪ ሥራዊት ከኤሽኑና ንጉሥ ይጠይቃል። ኤሽኑና ግን እምቢ አለው። ከዚያ በኋላ ግን የኤካላቱም ሰዎች ከአላሐድ ንጉሥ አታምሩም ጋር በመንፈቅለ መንግሥት ሐሙታር የተባለ ሰው በኤካላቱም ዙፋን ላይ አኖሩ። ስለዚህ አባቱ ንጉሥ እሽመ-ዳጋን በጣም ታምመው ወደ ባቢሎን ንጉሥ ሃሙራቢ ተጉዞ ቤዛ ለአላሐድ ጓደኛና ደጋፊ ለኤላም ይለምናል፤ ልጁን ለኤካላቱም እንዳስመለሰ ይሆናል።

እሽመ-ዳጋን ባረፈው ጊዜ ብዙ ሌሎች ሰዎች ለአሦር ንጉሥነት ተነስተው ብሐራዊ ጦርነት እንደ ሆነ ይመስላል። የሙት-አሽኩር ስም በአሦር ነገሥታት ዝርዝር አይገኝም፣ ዳሩ ግን በእርሱ ፈንታ ስለ አሹር-ዱጉል፦ «አሹር-ዱጉል ዲቃላ ልጅ ነበረ፣ የዙፋን ማዕረግ አልነበረውም። በአሹር-ዱጉል ዘመን መጀመርያ፣ 6 ሌሎች «ዲቃላ» የተባሉ ጣውንት ነገሥታት ተነሡ፦ አሹር-አፕላ-ኢዲ፣ ናሲር-ሲን፣ ሲን-ናሚር፣ ኢፕቂ-ኢሽታር፣ አዳድ-ሳሉሉ እና አዳሲ ናቸው።» በአንዳንድ ሊቃውንት ግምት አሹር-ዱጉል በአሹር ከተማ እየነገሠ ሙት-አሽኩር በኤካላቱም ብቻ ይገዛ ነበር።

ከዚህ በላይ በዚህ ወቅት የባቢሎን (የሃሙራቢ) አገረ ገዥ ፑዙር-ሲን ንጉሡን አሲኑም (የ1 ሻምሺ-አዳድ ልጅ-ልጅ) አሞራዊ ስለ ነበር ከዙፋኑ እንዳባረረው በማለት አስቀረጸ። አሲኑም ወይም ሙት-አሽኩር እራሱ ወይም ወንድሙ ሊሆን ይቻላል።

በመጨረሻ የአዳሲ ልጅ ቤሉ-ባኒ ኗሪ ሥርወ መንግሥት በአሦር መሠረተ።