ሚሌሲያን

ከውክፔዲያ

ሚሌሲያንአይርላንድ አፈ ታሪክ ዘንድ፣ አይርላንድን በጥንት ከወረሩት ነገዶች መጨረሻዎች ነበሩ።

ከሚሌሲያን አስቀድሞ አይርላንድን የሠፈሩት ፬ ሕዝቦች - የፓርጦሎን ሕዝብ፣ የነመድ ሕዝብ፣ ፊር ቦልግ፣ እና ቱአጣ ዴ ዳናን - ሁላቸው የማጎግ ዘር ይባላሉ። በተቀራኒ የኚህ ሚሌሲያን ሃረገ ትውልድ ግን ከማጎግ ሳይሆን ከጋሜርና ከፌኒየስ ፋርሳ እንደ ደረሰ ይጻፋል።

ሌቦር ጋባላ ኤረን[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሌቦር ጋባላ ኤረን ዘንድ የሚሌሲያን ወላጆች አለቆች ከጋሜር እንዲህ ነው፦

  • ጋሜር - የያፌት ልጅ
  • ኢባጥ (ሪፋት)
  • በዓጥ
  • ፌኒየስ ፋርሳ - ለ፵ ዓመታት የእስኩቴስ ንጉሥ
  • ኔል - ወንድሙን ነኑዋልን ገድሎ ወደ ግብጽ ሸሸ፤ የፈርዖንን ሴት ልጅ ስኮታ አገባት። ይህ በኒኑስ ዘመን እንደ ሆነ ይባላል።
  • ጋይድል ግላስ - ጎይደልኛ ፈጠረ (የአይርላንድኛየስኮትላንድ ጋይሊክኛ ወላጅ)።
  • ኤስሩ
  • ስሩ - ሕዝቡ ከግብጽ ወደ እስኩቴስ ተመለሱ (204 ሰዎች)። ይህ ሚሌሲያን ወደ አይርላንድ ሳይገቡ 440 ዓመታት በፊት እንደ ሆነ ይባላል።
  • ኤበር ስኮት - እስኩቴስን ከኑኑዋል ልጆች ያዘ።
  • ቧማይን - በነኑዋል ልጅ ኖሚየስ ዕጅ ተገደለ።
  • አግኖማይን - ኖሚየስን ገድሎ እስኩቴስን ገዛ።
  • ታት - የኖሚየስ ልጅ ሬፊልን ገድሎ እስኩቴስን ገዛ፤ በሬፊል ልጅ ሬፍሎይር ዕጅ ተገደለ።
  • ፪ አግሞናይን - ሬፍሎይርን ገድሎ ሕዝቡ ወደ ጥቁር ባሕር አጠገብ ሸሹ (180 ሰዎች)፣ ብሔሩም በዚያ ፫ መቶ ዓመታት ቀሩ።
  • ላምፊንድ
  • ኤበር ግሉንፊንድ
  • አግኒ
  • ፌብሪ ግላስ
  • ነኑዋል
  • ኑዋዱ
  • አሎት
  • ኤርቃ
  • ዴጥ
  • ብራጥ - ከጥቁር ባሕር አጠገብ ተነስተው በክሬታና በሲኪልያ በኩል ወደ እስፓንያ ደረሱ። (140 ሰዎች)
  • ብሬውጋን - ብሪጋንቲያ ከተማ በእስፓንያ ሠራ።
  • ኢጥ - አይርላንድን ከእስፓንያ አይቶ ወደዚያ ተጓዘ፤ ይህም በቱዋጣ ዴ ዳናን ነገሥታት ማክ ኲልማክ ኬክትማክ ግሬን ዘመን ነበር፤ ኢጥ በአይርላንድ ሲጎበኝ ስለ ተገደለ፣ ቂሙን ለማብቀል የብሬውጋን ልጆች (አሁን 1,500 ሰዎች) አይርላንድን ወረሩ።

«ሚሌሲያን» የሚለው ስያሜ ከብሬውጋን ሌላ ልጅ ቢሌ ልጅ ጋላም መጠሪያ «ሚል ኤስፓኝ» ነው። በሮማይስጥ የተጻፈው ሂስቶሪያ ብሪቶኑም (የብሪታንያውያን ታሪክ) «ሚሌስ ሂስፓኒያይ» (የእስፓንያ ወታደር) ስላለው ነው። እንዲያውም የብሔሩ ስም በትክክል «ጋይደሎች» ተባለ፤ ከዚያ አይርላንድን ከገዙት ከፍተኛ ነገሥታት አብዛኖቹ ከዚያው ሚል (ጋላም) ዘር ስለ ተወለዱ «ሚሌሲያን» ይባላሉ። የጋይደሎች አለቃ የ«ሚል» (ጋላም) ልጅ አመርጊን ሲሆን ቱዋጣ ዴ ከተሸነፉ በኋላ ከፍተኛ ንጉሥነቱን ለወንድሞቹ ለኤቤር ፊን (በደቡብ) እና ለኤሪሞን (በስሜን) አካፈለ።

የሚሌሲያን ወረራ ጊዜ በልዩ ልዩ አቆጣጠሮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሌቦር ጋባላ አቆጣጠር ዘንድ (በኋለኞቹ ቅጂዎች) ጋይደሎች አይርላንድን የወረሩት በታላቁ አሌክሳንድር ዘመን በ336 ዓክልበ. ሆነ። ከዚህ ጋር በሚሔደው ነገሥታት ዝርዝር መሠረት ግን፣ ጋይደሎች አይርላንድን የገቡ በእስራእል ንጉሥ ዳዊት ዘመን ወይም 1000 ዓክልበ. ግድም ሆነ። የአራት ሊቃውንት ዜና መዋዕሎች በተባለው ታሪክ መሠረት ግን አይርላንድን ከቱዋጣ ዴ ዳናን የያዙት በ1708 ዓክልበ. ሆነ። የአይርላንድ ታሪክ ባለው አቆጣጠር ደግሞ ይህ ወረራ በ1295 ዓክልበ. ሆነ። ከሁሉ ጥንታዊ የሆነውም ምንጭ ሂስቶሪያ ብሪቶኑም እንዳለው ወረራው በሮሜ መጀመርያ ቆንስላ ሉክዩስ ዩንዩስ ብሩቱስ ዓመት (517 ዓክልበ.) ሆነ።

በአይርላንድ ዝርዝሮች መካከል ከሁሉ ቀድሞ የተቀነባበረው የላውድ አቆጣጠሮች (1012 ዓም) ሲሆን በዚህ በኩል የሚሌሲያን ወረራ በዳዊት ልጅ ሰሎሞን ዘመን ነበር (950 ዓክልበ.) ሲል፣ በውስጡ ያሉት የነገስታት ዘመናት በጥንቃቄ ሲደመሩ ወረራው በ1305 ዓክልበ. ያሕል እንደ ሆነ ይመስላል።

በተጨማሪ የእስፓንያ ነገሥታት ዝርዝር 773-744 ዓክልበ. ግድም «ሚሌሲያን» በኢቤሪያ እንደ ገዙ ይላል።