ምናኔ

ከውክፔዲያ


በአፍሪቃ ቀንድ ላይ ባለችው በዚህች ኢትዮጵያችን ውስጥ ምግባር ባህል ሃይማኖት ልዮ ትኩረት ተሰጥቷቸው ረጅም ከሚባል ዘመን በላይ የተሻገሩ የማንነት እሴቶች ናቸው::

እነዚህ ከብዙ ሃገራት የሚለዩዋት እሴቶች ናቸው እንግዲህ ከባህሉ ከቋንቋው ከኪነ ጥበቡ ከአስተዳደሩ ከዘመን ቀመሩ ከፍልስፍናው… ወ.ዘ.ተ ጋር ተዳምረው ራሷን የቻለች ነፃ ሃገር እና ጥንታዊት የአለም ቅርስ የሚያሰኛት እነዚህ ከላይ የጠቀስናቸው እሴቶቿ እንዲህ ባለ ረዥም ጊዜ ባስቆጠረ ድህነት እና ውስጣዊ የእርስ በእርስ ጦርነት (ሃይማኖታዊ እና የአስተዳደራዊውን ፍጭት አጠቃሎ) እንዲሁም የውጭ ወረራ እና ዝርፊያ አልፎ በቃልም ይሁን በፅሁፍ ወይም በሌላ በማንኛውም አይነት መንገድ ተጠብቀው ቆይተው ከተሻገሩባቸው እና አሁንም ከተጠለሉባቸው ታዛዎቹ ውስጥ የመሪነቱን ቦታ የሚይዙት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ (ቀደም ሲል ከግብፅ በተሻገረው መንበረ ማርቆስ እህት ቤተ ክርስቲያን ከጊዜ በሁዋላ ደግሞ ራሱን ችሎ መንበረ ተክለ ሃይማኖት ) ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ የተጠቃለሉት ገዳማት በዋነኝነት ይመደባሉ::

ታዲያ በእነዚህ ገዳማት ውስጥ በህርመት የሚኖሩ ባህታዊያን እና ካህን መነኮሳት ረዥም ጊዜ በቆየው እና የቀደመ የግብፃዊያንን አስቸጋሪ እና በእጅጉ ፈታኝ የሆነ የምናኔ ህይወት አሁንም ጠብቀውት እና ከእለት እለት ህይወታቸው በፍቃደኝነት እና በፍቅር ይኖሩታል:: በመንፈሳዊው አስተሳሰብ የሚታመንበትን የአጋንንት ውጊያ ከሰው ልጅ የህልውና አቅም በላይ የሆነውን የበረሃውን ንዳድ የአራዊትን ፀብ ሁሉ ስጋዊ ህፀፆችን ከራስ ላይ እየጣሉ ወደ ፍፁም መለኮታዊ አኗኗር መለወጥ በሚል መለኮታዊ ፍልስፍና ተጠምደው ይኖራሉ ይህ አለም ሁሉ በቅጡ ያላጤነው እፁብ የሆነውን ይህ የህይወት ፍሰት በአለም ውስጥ የተደበቀ ሌላ አለም ነው::