ጆሰፍ ስሚስ

ከውክፔዲያ
ጆሰፍ ስሚስ 1835 ዓም ፎቶ

ጆሰፍ ስሚስ (1798-1836 ዓም) አሜሪካዊ የሃይማኖት መሪና የሞርሞኒስም መስራች ነበረ።

ጆሰፍ ስሚስ በክርስቲያን ኅብረተሠብ የተወለደው ቢሆንም፣ በወጣትነቱ እንደ አስማተኛ ዝነኛ ሆኖ ነበር። በ«ንግርተኛ ድንጋዮች» እርዳታ የጠፉትን ቅርሶች ለማግኘት ችሎታው እንደ ነበረው ማሳመን ቢሞክር፣ በማናቸውም ፈተና ይህ ዘዴ ሐሣዌ መሆን ሲገለጽ፣ ከድፍረቱ ግን አልዞረም ነበር።

በ1820 ዓም «ሞሮናይ» የተባለ አንድ መልአክ «የወርቅ ጽላቶችን» እንዳሳዩት ብሎ እነኚህን ጽላቶች ወደ እንግሊዝኛ በ«ንግርተኛ ድንጋዮች» ለማስተርጐም ዋና እቅዱ ሆነ። ስሚስ እንደ ነገረው ጽላቶቹ የተቀረጹበት ቋንቋ «ተሐድሶ ግብጽኛ» እንደ ነበር አለ። ለመሆኑ በዚያ ዘመን ያሕል የታሪካዊ ግብጽኛ ማንበብ ችሎታ እየተፈታ ሲሆን፣ ስሚስ በእውነት ስለ ግብጽኛ ወይም ስለ ቋንቋ ጥናት ያወቀው ብዙ ነገር እንዳልነበረ ግልጽ ነው።

ጆሰፍ ስሚስ ድንጋዮቹን አይቶ የመጽሐፈ ሞርሞን ትርጉም ሲያወራ

የወርቅ ጽላቶቹ በሰዎች መቸም አልታዩም፤ ስሚስ እንዳለው እያስተረጎማቸው አንድላይ ከሱ ጋር መኖራቸው አስፈላጊ አልነበረም፣ በመላዕክት እርዳታ ነው ብሎ ድንጋዮቹን በመመልከት የጽሑፉን እንግሊዝኛ ትርጉም በቃል ያወራ ነበር፤ ጓደኞቹም ከዚያ ያወራውን ይጽፉ ነበር። እንዲህ መጽሐፈ ሞርሞን ተፈጠረ። በዚህ መጽሐፍ ዘንድ አይሁዶች በጥንት ከእስራኤል ወጥተው ወደ አሜሪካ ፈለሱ፤ በኋላም ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ ወደ እነርሱ በአሜሪካ መጣላቸው ይላል።

በስሚስ ኗሪ ክፍላገር በኒው ዮርክ የነበሩት ሕዝብ በአጠቃላይ ስለ ተቃወሙት፣ ከተከታዮቹ ጋር ወደ ምዕራብ ሸሹ። በአዲስ ሃይማኖቱ ከክርስትና ከሚለዩ ትምህርቶች መካከል፣ ሥላሴን አያስተምርም፣ ኢየሱስና እግዚአብሔር የተለያዩ ናቸው፣ ስሚስ ነቢዩ ነው፣ በተጨማሪ «አንድ ባንድ» ሳይሆን አንዱ ሰው አያሌ ሚስቶች ማግባት መልካም እንደ ሆነ ሁሉ የሚያስተምር ሃይማኖት ሆነ። ሌሎችም ስነ ሥርዐቶች በምስጢር ተጠበቁ።

አንድ ጊዜ የእውነተኛ ግብጽኛ ብራና ከነጋዴ ገዝቶ ይህን ደግሞ «አስተረጎመ»። በጆሰፍ ስሚስ ትርጉም ጽሑፉ የሞርሞኖች «መጽሐፈ አብርሃም» ሆነ። ይህም ብራና አሁን ለሊቃውንት ታውቆ ግን ምንም ስለ አብርሃም የሚል ነገር ሳይሆን፣ በውኑ የግብጻውያን «መጽሐፈ ሙታን» ቅጂ መሆኑን ገለጹ። ሆኖም ሞርሞኖች እስካሁን የስሚስ ብልሃትና ቅንነት ደጋፊዎች ናቸው።

ስሚስ ደግሞ ደብረ ጽዮን እና አዲስ ኢየሩሳሌም በውነት በጣም ለጥ ባለ ቦታ በሚዙሪ ክፍላገር እንደ ተገኙ አስተማረ። በዚህ ስፍራ ግን እጅግ ለጥ ብሎ ምንም ተራራ በፍጹም አይታይም። ያም ሆነ ይህ እስካሁን ድረስ በብዙ ሞርሞኖች እንደ ተቀደሰ ቦታ ይቆጠራል።

ስሚስ በመጨረሻ በቁጡ ሕዝብ በእስር ቤት እያለ ተገደለ። ዳሩ ግን ብዙ ሺህ ተከታዮች ስላገኘ አሁንም ሞርሞኒስም በሰፊ ይገኛል።