ስለ ያ ትውልድ ተቋም

ከውክፔዲያ

«ያ ትውልድ ተቋም»ን እናስተዋውቃችሁ ያ ትውልድ ያስመዘገበውን አኩሪ የፍትህ ተጋድሎና የከፈለውንም መስዋዕትነት ለማስታወስና ተተኪው ትውልድ ካለፈው ትውልድ ታሪክ በመቅሰም ለሀገሩና ለሕዝቡ ተሟጋች ብቁ ዜጋ ይሆን ዘንድ መሠረት የሚጥል፡ በያ ትውልድ ስም የሚንቀሳቀስ «ያ ትውልድ ተቋም» በመባል የሚታወቅ የትውልድ መታሰቢያ ተቋም በሰሜን አሜሪካ ተመሥርቷል። የ«ያ ትውልድ ተቋም» ከማንኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ነፃ ሆኖ በትግሉ ላለፈው ትውልድ መታሰቢያ ይሆን ዘንድ የትግሉን ታሪክ እውነተኛ መረጃ በማሰባሰብ፣ የተጎዱ ወገኖችን በመርዳትና ለትውልዱ የስም መጠሪያ ይሆን ዘንድ መታሰቢያዎችን በማቆም ላይ ትኩረት አድርጎ በውጭው ዓለም ይንቀሳቀሳል፤ በሀገር ቤትም ሕጋዊነቱን ለማግኘት በጥረት ላይ ነው። «ያ ትውልድ ተቋም» በኅዳር 2005 ዓ.ም. ለንባብ ያበቃውንና በሰኔ 29 ቀን 2005 ዓ.ም. በህትመት መልክ ያቀረበውን “ያ ትውልድ ስንል” በጥያቄና መልስ በቀረበው መጣጥፍ መሠረት “ያ ትውልድን” በዚህ መልክ ያስቀምጠዋል። “ያ ትውልድ” ስንል ዋናውን የ1966 እንቅስቃሴ አንኳር ኃይል ይይዛል። ሆኖም ለዚህ እንቅስቃሴ የጀርባ አጥንት የነበረውና ዋነኛው ከዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን በተለይ የተማሪዎች እንቅስቃሴ (ዋለልኝ መኮንን፡ ማርታ መብራቱ፡ ጥላሁን ግዛው ዘመን)፡ የሠራተኛ ማኅበራት (አበራ ገሙ)፡ የሠራዊቱ እንቅስቃሴና መሰል ውጤት በመሆኑ: ያ ትውልድ ስንል ከ1953 የእነ ግርማሜና መንግሥቱ ነዋይ ዘመን ጀምሮ እስከ 1983 ዓ.ም. ያለውን የ30 ዓመት ጊዜ ለማየት ቢሞከርም ትኩረቱ ግን የ1966 ዓ.ም. የየካቲትን የለውጥ ማዕበል ያንቀሳቀሰውን ኃይል ጨምሮና በኢሕአፓ ጥላ ሥር ተሰልፎ ለዴሞክራሲና ለሕዝብ መንግሥት ምሥረታ መሥዋዕትነት የከፈለውንና እየከፈለ ያለውን ትውልድ ይመለከታል። ይህን ዋነኛው የያ ትውልድ አካል አድርገን ብንወስድም ይዘን የተነሳነው ተልዕኮ ያ ትውልድ ብለን ካስቀመጥነው የጊዜ ገደብ በፊትም ሆነ በኋላ ያለውን አይመለከትም ማለት አይደለም። ወደ ተማሪዎች እንቅስቃሴ ታሪክ ስንመለከት ወደ 1930ዎቹ በጣት የሚቆጠሩ የተማሪዎች እንቅስቃሴ የእነ ዶር መላኩ በያን ዘመንን መዳሰስ ግድ ይላል። በሌላ በኩልም ለኢትዮጵያ የግዛት አንድነትና ሉዓላዊነት ከባዕዳን ወራሪዎች ሲፋለሙ ክቡር ሕይወታቸውን የከፈሉና አኩሪ ታሪክ አስመዝግበው ያለፉ ጀግኖች ኢትዮጵያውያንን እንመለከታለን፦ ለአብነት ያህል እነ አብርሃ ደቦጭና ሞገስ አስገዶም፣ ዘረዓይ ደረስ፣ አቡነ ጴጥሮስ፣ ወዘተ ዓይነት ክቡር ጀግኖች ታሪክ መዘገብ አለበት እንላለን። በያ ትውልድ ስም የኢትዮጵያን የትግል ታሪክ ማሰባሰብ አንዱ ተልዕኮአችን በመሆኑ የአሁኑንም ትውልድ የትግል ታሪክ እንዳስሳለን። አዲሱ ትውልድ የያ ትውልድን ታሪክ አውቆ በቀጣይነት ሀገሩንና ሕዝቡን አፍቃሪ ብቁ ዜጋ ይሆን ዘንድ ከተፈለገ ያለፈውንና ያሁኑን ታሪክ አጣምሮ፤ ያለውን ክፍተት ማጥበብ አስፈላጊ መሆኑን እናምናለን። በመሆኑም በተለያዩ የጭቆና አገዛዝ መረቦች ውስጥ ተቀፍድዶ የተያዘውን ሕዝባችንን ለዜግነት መብቱ መከበርና ለዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ግንባታ ሲፋለሙ የአምባገነን አገዛዞች ሰለባ የሆኑትን ወገኖች ከያ ትውልድ ዘመን በፊትም ሆነ በኋላ ያሉትን ይመለከታል። በሰኔ 28-29, 2004 ዓ.ም. በሰሜን አሜሪካ ዳላስ በተካሄደው መሥራች ጉባኤ እንደተመሠረተ የሚታወቀው «ያ ትውልድ ተቋም» ቀደም ሲልም በተለይ በ1969 ዓ.ም. የዓለም ሠራተኞች ቀን ክብረ በዓል በሰላማዊ ሰልፍ ለማክበር በወጡ ወጣቶችና ሕፃናት ላይ በደርግ አገዛዝ የደረሰውን ፍጅት በማሰብ፤ በሜይ ዴይ ማለትም ሚያዝያ 23 ቀን 2004 ዓ.ም የዚሁ ተቋም ድረ ገጽ www.yatewlid.org or www.yatewlid.com ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ይፋ መደረጉ ይታወቃል። ይህ ድረ ገጽ በተለይ 1969/71 በደርግ ነፃ ዕርምጃና ቀይ ሽብር ሰለባ የሆኑትን ሰማዕታት ስምና ምስል ከማካተቱም በተጨማሪ በወቅቱ ይወጡ የነበሩ ድርጅታዊ ልሳኖችን (ለምሳሌ በኢሕአፓ በኩል “ዴሞክራሲያ”፣ በመኢሶን በኩል “የሰፊው ሕዝብ ድምጽ” ) እና ሌሎችንም መጣጥፎችን ያካተተ የመረጃ ጎተራ (ዳታ ቤዝ) ነው። ያ ትውልድ ድረ ገጽ የ«ያ ትውልድ ተቋም» ዋና ቤተ መረጃና ወቅታዊ መልዕክቶችን ማስተላለፊያ ነው። ያ ትውልድ ድረ ገጽ ከሌሎች የሚለየው ማንኛውንም የፖለቲካ ወገንተኝነት ሳይዝ መረጃዎችን በማሰባሰብ ላይ የተመረኮዘ መሆኑ ነው። በድረ ገጹ የተካተቱትን መረጃዎች ለማየት፣ ለማንበብ፣ ለዋቢነት ወዘተ ለመጠቀም ለሚፈልጉ ወገኖችና ተጠቃሚዎች በፍጥነትና በቀላሉ ያገኙት ዘንድ ታስቦ የተዘጋጀ ነው። በጥቅሉ የያ ትውልድ ድረ ገጽ ቤተ መረጃ፤ በዘመኑ ሥልጣኔ ደረጃ የኢንተርኔት ግልጋሎት ባለበት በየትም ቦታና በማንኛውም ጊዜ ሊያገኙትና ለማንበብም ሆነ ለሌላ ጠቀሜታ እንዲያውሉት ሆኖ የተደረደረና የሚፈልጉትን መረጃ ሙሉ በሙሉ በነፃ ከአሉበት ቦታ ሆነው እንዲያገኙት በሚያስችል ሁኔታ የተዘጋጀ የዲጂታል መረጃና መታሰቢያ ድረ ገጽ ነው። በ “ያ ትውልድ ስንል” መጣጥፍ በግልጽ እንደተቀመጠው “ያ ትውልድ ተቋም”ን በቀዳሚነት የመሠረትን በኢሕአፓ ውስጥ በተለያየ ጊዜ የነበርንና በአሁኑ ወቅት በተለያዩ መስኮች ላይ የተሳተፍን የቀድሞ የኢሕአፓ አባላት ነን። ጅምር ማሰባሰቡን በቀዳሚነት እንውሰድ እንጂ «ያ ትውልድ ተቋም» በአባልነት የኢሕአፓ አባል ያልነበሩትንና ከአሁኑም ትውልድ ያሉ ወገኖችን ያካትታል። «ያ ትውልድ ተቋም» ሦስት መሠረታዊ ዓላማዎችን ይዞ የተነሳ ተቋም ነው፤ እነሱም ፦ 1. የኢትዮጵያን በተለይ የያ ትውልድን የዴሞክራሲና የፍትህ ትግል ታሪክ ማሰባሰብ 2. ለያ ትውልድ ሰማዕታት መታሰቢያ ሐውልት ማቆምና 3. በትግሉ የተጐዱ ወገኖችንና ቤተሰቦችን መርዳት ናቸው። የያን ትውልድ ታሪክ መረጃ ማሰባሰብና ለትውልድ ማሰተላለፍ ጠቀሜታው ከትምህርት ሰጪነቱ በተጨማሪ በሀገራችን በደርግ አገዛዝ የደረሰው አንድ ትውልድ የመመተር እርምጃ ዳግም እንዳይደገም ልብ! እንድንል “ያ ትውልድ” ቃሉ ይጋብዘናል። ይህ በኢትዮጵያ የታሪክ መረጃ አያያዝ ደረጅ ቀዳሚነትን የያዘው ድረ ገጽ ሊጎበኝና ሊታገዝ የሚገባው ሲሆን የያ ትውልድ የትግል ታሪክ በማሰባሰብ ከትውልድ ትውልድ ይተላለፍ ዘንድ መሠረቱን የጣለው «ያ ትውልድ ተቋም» ዕንቁ/Noble ዓላማ ይበልጥ ለመረዳትና ግንዛቤ ለማግኘት www.yatewlid.org or www.yatewlid.com ድረ ገጽን ይጎብኙ፤ “ያ ትውልድ ስንል” መጣጥፍን ያንብቡ። ያ ትውልድ ድረ ገጽ በቅርብ ጊዜ ሙሉ በሙሉ የእንግሊዘኛ ክፍል እንደሚኖረው በዚህ አጋጣሚ መግለጽ እንወዳለን።

ያ ትውልድ ተቋም ለማንኛውም ጥያቄና አስተያየት የኢሜል አድራሻችን፡ yatewlid@yahoo.com, yatewlid@gmail.com, yatewlid@hotmail.com