መሬት ነክ ምህንድስና (ጂኦቴክኒካል ምህንድስና)

ከውክፔዲያ

መሬት ነክ ምህንድስናግንባታ አካላትን የሚሸከሙ አለቶችና አፈሮችን የምህንድስና ጠባይ የሚያጠና የሲቪል ምህንድስና ዘርፍ ነው። ይህ ዘርፍ ከአፈር ሳይንስ፣ ከቁስ ሳይንስ ፣ ከሜካኒክስ እንዲሁም የፍሰት ሳይንስ (hydraulics) እውቀቶችን በመጠቀም ደህንነታቸው የተጠበቀና የገንዘብ አቅምን ያገናዘቡ የግንባታ መሰረቶችን፣ የመጠበቂያ ግድግዳዎችን፣ ግድቦችን፣ ዋሻዎችን የመሳሰሉ የግንባታ አካላትን መንደፍና መገንባት ላይ ትኩረት ያደርጋል ።

የከርሰ ምድር ውሃን በተለያዮ ምክንያቶች ከመበከል የመጠበቅ እንዲሁም የቆሻሻ ክምችትን በአግባቡ ለመቆለልና ክምችቱ የአፈርና የከርሰ ምድር ውሃን እንዳይበክል የማድረግ ስራዎችም በዚሁ የምህንድስና ዘርፍ የሚተገበሩ ናቸው።

የአፈርን የምህንድስና ጸባይ የማወቅ ተግባር ለመሬት ነክ መሃንዲሶች ፈታኝ ነው። በሌሎች የሲቪል ምህንድስና ዘርፎች የግንባታ ቁሶች ጸባይ (ለምሳሌ እንደ ብረት እና ኮንክሪት) በሚገባ የሚታወቅ ሲሆን፤ በግንባታ አካባቢ የሚገኝን የአፈር ጸባይ ማወቅ ግን ከተለዋዋጭነቱና በናሙና በሚደረጉ ሙከራዎች መፈተሽ የሚቻለው ከጠቅላላውን የተወሰነውን ብቻ በመሆኑ በጣም አዳጋች ነው።

ከዚህም በተጨማሪ አፈር በጭነት ምክንያት የሚያደርገው የቅርጽ ለውጥ ከጫናው ጋር ቀጥተኛ ያልሆነ (nonlinear) ተዛምዶ ስላለው፤ ማለትም አነስተኛ እና ከፍተኛ ለሆኑ ጫናዎች የተለያየ ጥንካሬ(strength)፤ ጠጣርነት(stiffness)፤ የቅርጽ ለውጥ ስለሚኖረው፤ የአፈርን የምህንድስና ጸባይ በተሟላ ሁኔታ ለማወቅ የዳግታል።

መሬት ነክ መሃንዲሶች አብዛኛውን ጊዜ ከከርሰ ምድር ባለሙያዎችና የአፈር ሳይንቲስቶች ጋር በትብብር ይሰራሉ።