የአካባቢ ጥበቃ ምህንድስና

ከውክፔዲያ

የአካባቢ ጥበቃ ምህንድስና ከጤና ጥበቃ ምህንስና ጋር ተጓዳኝ የሆነ የምህንድስና ዘርፍ ሲሆን፣ የጤና ጥበቃ ምህንድስና በአመዛኙ የንጹህ ውሃ መጠጥ አቅርቦትና የአካባቢ ቆሻሻ ፍሳሽ አወጋገድ ላይ ሲያተኩር፤ የአካባቢ ጥበቃ ምህንድስና ሰፋ ባለ መልኩ የአካባቢ ብክለት የሚያስከትሉና ለጤና ጠንቅ የሆኑ ጎጂ ኬሚካሎችን እና ቆሻሻዎችን መቆጣጠርና ማስወገድ ይጨምራል። የአካባቢ ጥበቃ ምህንድስና፤ የማህበረሰብ ጤና ምህንድስና እና የአካባቢ ጤና ምህንድስና በሚል አጠራርም ይታወቃል።

የአካባቢ ጥበቃ ምህንድስና በኬሚካል ውህደቶች፣ በባዮሎጂካል ሂደቶች እንዲሁም በሙቀት ለውጥ አማካኝነት የሚፈጠሩ ቆሻሻዎችን የማጥራትና የማስወገድ፣ አየርንና ውሃን የማጣራት፣ እንዲሁም በአደጋ ወይም በቆሻሻ ክምችት የተበከለን የመሬት አካል ወደ ተፈጥሮዋዊ ይዘቱ የመመለስ ስራዎች የሚያከናወኑበት የምህንድስና ዘርፍ ነው። በአካባቢ ጥበቃ ምህንድስና ትኩረት ከሚደረግባቸው ዋና ነጥቦች ውስጥ የመርዝ ወይም የኬሚካል እንቅስቃሴ ወይም ጉዞ (ከመሬት ላይና ከመሬት በታች)፣ የውሃ ማጣራት፣ የቆሻሻ ፍሳሽ ማጣራት፣ የአየር ብክለት፣ የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድና የአደገኛ ቆሻሻዎች አያያዝ ይገኙበታል። የአካባቢ ጥበቃ መሃንዲሶች ብክለትን የመቀነስ፣ የአረንጓዴ ምህንድስና ዘርፍ ስራዎች (የአካባቢ ብክለትን የሚቀንሱ የግንባታ መንገዶችንና ቁሶችን የኢኮኖሚ አቅምን ባገናዘበ መልኩ የማጥናት ስራ)፤ እንዲሁም የኢንዱስትሪዎችን የቁሳቁስና የሃይል አጠቃቀም ፍሰት የማጥናት ስራዎችና (industrial ecology) የመሳሰሉት ላይ ይሳተፋሉ። ከዚህም በተጨማሪ የአካቢቢ ጥበቃ መሃንዲሶች ድርጊቶች (ለምሳሌ የአንድ የግንባታ አካል ትግበራ) በአካባቢው ላይ ሊያስከትሉ የሚችሉትን ተጽእኖ በመገምገም መረጃ ያዘጋጃሉ።