ሙሴ

ከውክፔዲያ
ዘልለው ለመሔድ፦ የማውጫ ቁልፎች, ፍለጋ
ሙሴ ጽላቱን ሲቀበል

ሙሴ (ዕብራይስጥ፡ מֹשֶׁה ) በብሉይ ኪዳን ከሚጠቀሱት ታላላቅ ነብያት አንዱ ነው። ሙሴ በተውለደበት ዘምን የእስራኤል ልጆች በግብጽ ውስጥ በባርነት ከ400 ዓመት በላይ ተገዝተው የነበርበት ሆኖም ግን ቁጥራቸው እየበዛና እየተጠናከሩ የነበርበት ጊዜ ነበር። በዚህ ዘመን ግብፅን ያስተዳድር የነበር፣ ስሙ በብሉይ ኪዳን ያልተጠቀሰው የግብፅ ፈርዖን፣ የእስራኤል ልጆች ከውጭ የግብፅ ጠላቶች አግዘው ሊወጉን ይችሉ ይሆናል በሚል ፍራቻ ማናቸው የእስራኤል ወገን የሆኑ ወንድ ልጆች በተወለዱ ጊዜ እንዲገደሉ አዘዘ። ሆኖም የሙሴ እናት፣ ዮካብድ፣ ልጇን ደብቃ ታኖር ነበር። ከሶስት ወር ድበቃ በኋላ ልጁን በደንገል ሳጥን አድርጋ በአባይ (ናይል) ወንዝ አጠገብ አስቀመጠችው። ሳጥኑ እየተንሳፈፈ የፈርዖን ልጅ እምትታጠብበት ስፍራ ደረሰ፣ የፍርዖንም ልጅ ለህጻኑ ስላዘነች በፈርዖን ቤት አደገ።

ካደገ በኋላ አንድ የግብፅ ባሪያ አሳዳሪ እስርኤላዊ አሽከሩን ሲደበድብ አይቶ ሙሴ ግብጻዊውን ገደለው። ሆኖም ይህ ጉዳይ በግብጽ ባለስልጣኖች ዘንድ እየተሰማ ስለሄደ ሙሴ ወደ ምድያም አገር ተሰደደ። በዚያ ለ40 አመት ያክል ሲቀመጥ የካህኑን ዮቶርን በጎች ይጠብቅ ነበር። በዚህ ጊዜ የድሮው ፈርዖን ሞቶ አዲስ ፈርዖን በግብፅ ነግሶ ነበር።

በአዲሱ ፈርዖን ዘመን የእስራኤላዊያኑ ጭቆና ባሰ እንጅ አልቀነሰም። ከኮሬብ ተራራ በሚገኝ ቁጥቋጦ ውስጥ በተገለጠለት መልዕክት መሰረት ሙሴ እድሜው 80 ከሞላ በኋላ ወደ ግብፅ ተመለሰ። የመመለሱም ዋና ዓላማ እስራኤላውያኑ ግብፅን ለቀው እንዲወጡ አዲሱን ፈርዖን ለማስፈቀድ ነበር። አዲሱ ፈርዖን እምቢ ስላለ ሙሴ 10 መቅሰፍቶችን በግብፅ ላይ ከፈፀመ በኋላ ንጉሱ ስለተስማማ እስራኤላውያንን እየመራ፣ ከ400 ዓመት በላይ ከተገዙበት ግብፅ አውጥቶ በሰናይ በርሃ መርቷል። በዚህ ወቅት እስራኤላውያኑ በኮሬብ ተራራ ተመስርተው የኤዶምን ደንበሮች ያስሱ ነበር። አሥርቱ ትዕዛዛትን ሙሴ የተቀበለው በዚህ ወቅት ነበር። በእንደዚህ አይነት ሁኔታ ሙሴና ህዝቡ ለ40 ዓመት በበርሃው ውስጥ ክዋተቱ በኋላ ሙሴም ወደተስፋይቱ ምድር ወደ ከነዓን ሳይገባ በዚሁ በስደት ወራት እድሜው 120 ሲሆን አልፏል።

በታሪክ አጥኝዎች ዘንድ፣ ሙሴ መቼ እንደኖረ በዕርግጥ አይታወቅም። አንድ አንድ አንድ ተመራማሪዎች የኖረበትን ዘመን ከክርስቶስ ልደት በፊት በ12ኛው ክፍለዘመን ሲያደርጉ ሌሎች ከዛ በፊት ነው ይላሉ።