ዘውዱ ጌታቸው

ከWikipedia

ዘልለው ለመሐድ፦ የማውጫ ቁልፎች, ፍለጋ
ዘውዱ ጌታቸው

ዘዉዱ ጌታቸው (አዲስ አበባ 1952 -አዲስ አበባ ታህሳስ 18 ቀን 1997 ዓ.ም)፣ ኤች.አይ.ቪ|ኤድስን በሚመለከት ፀጥታና ዝምታ በሰፈነበት ወቅት ራሱ ከቫይረሱ ጋር እንደሚኖር ይፋ በማዉጣት «ትዉልድ ይዳን በእኛ ይብቃ» ! ብሎ ኤች.አይ.ቪ|ኤድስን ለመዋጋት የተነሳ ኢትዮጵያዊ ጀግና ነበረ። ዘዉዱ ጌታቸው የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን በመስፍን ሀረር ትምህርት ቤት ፤የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ በተፈሪ መኰንን ትምህርት ቤት ተምሮ ካጠናቀቀ በኋላ በአዲስ አበባ ዮኒቨርሲቲ ቴክኖሎጂ ፋክልቲ በመግባት የከፍተኛ ደረጃ ትምህርቱንም አጠናቋል። በአሰላ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በመምህርነት እንዲሁም በዚላ፥በበርታ፥በሱርና፥በሶጀት ኮንስትራክሽን ድርጅቶች በመካኒክነት ሠርቷል።

«እኔ ከቫይረሱ ጋር የምኖር ነኝ።» በማለት የኢትዮጵያ ሕዝብን በአደባባይ ለማስተማር መዉጣት እጅግ በጣም ጥቂት ቆራጦች ብቻ የሚደፍሩት ተግባር በነበረበት ጊዜ ብቅ ብሎ ለአገር የሚጠቅም ታላቅ ተግባር ሲያከናዉን የቆየ ሰዉ ነበረ። ዘዉዱ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነዉን ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ሰዎች ማህበር «ተስፋ ጎህ ኢትዮጵያን» በ1990 ዓ.ም ከአሥር ጓደኞቹ ጋር በመመስረት ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ወገኖች መብታቸዉን ለማስከበር እንዲታገሉ ከማሰባሰቡም በላይ ኤች.አይ.ቪ|ኤድስን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በሚደረገዉ ትግል ዉስጥ ጉልህ አስተዋፅኦ አድርጓል። ራሱ ከቫይረሱ ጋር እንደሚኖር ይፋ አዉጥቶ በማሳወቁ ምክንያት ይደርስበት የነበረዉን አድልኦና ማግለል በቆራጥነት በመፋለም ዛሬ ኤች.አይ.ቪ|ኤድስን በሚመለከት ኢትዮጵያ ዉስጥ ለተገኙ አዎንታዊ ለዉጦች ከፍ ያለ ድርሻ አበርክቷል። ዘዉዱ ጌታቸው በአገርና በአለም አቀፍ ደረጃ ተስፋ ጎህን በመወከል የኤች.አይ.ቪ|ኤድስ ችግር በአገራችን እያደረሰ ያለዉን እዉነታ በመናገርና ለበሽታዉ መንግስት ትኩረት እንዲሰጥ ጥሯል። በተጨማሪም «ተስፋ ብርሃን በኤድስ ወላጅ አልባ ሕፃናትና ወጣቶች ማህበር»ንም በመመስረት ኤች.አይ.ቪ|ኤድስን የሚያስከትለዉን ሰብዓዊና ማህበራዊ ቀዉስ በመታገል አያሌ ታዳጊዎችን ከመበተን አድኗል። ከ1996 ዓ.ም ጀምሮ በኤች.አይ.ቪ ምክንያት በስራ ቦታ የሚደርሰዉን አድልኦና ማግለል ይበልጥ ለመታገል ወደ ማህበር ለመምጣት ያልደፈሩትን ወገኖች በስልክና በሌሎች የመገናኛ አዉታሮች የምክር አገልግሎት ለመስጠትና ከኤች.አይ.ቪ|ኤድስ ጋር የሚኖሩ ወገኖች ሰብአዊ መብት እንዲከበር ይበልጥ ለመታገል «አዲስ ምዕራፍ» የተባለ ድርጅት አቋቁሟል። እስከ ሕልፈተ ሕይወቱ ድረስ ሠርቷል። ዘውዱ ጌታቸው ባደረበት ሕመም ምክንያት በተለያዩ ሆስፒታሎች በሕክምና ሲረዳ ቆይቶ በተወለደ በ45 ዓመቱ ታህሣሥ 18 ቀን 1997 ዓ.ም ከዚህ አለም በሞት ተለይቱዋል።

የኔ መሣርያዎች