ቅዱስ ሩፋኤል

ከውክፔዲያ
ቅዱስ ሩፋኤል
መንፈሳዊ ሐኪም

ቅዱስ ሩፋኤል ከጦቢት ጋር
ሊቀ መላዕክት
ሩፋኤል ማለት እግዚአብሔር ያድናል (ይፈውሳል) ፣ ደስታ ማለት ነው
የንግሥ ቀን ጳጉሜ ፫ ቀንስንክሳር
የሚከበረው በመላዕክት አማላጅነት በሚያምኑ በተለይ በኦርቶዶክስና ካቶሊክ ቤተክርስቲያኖች
የሚውልበት ቀን ወር በገባ በ፲፫ኛው ቀን ከአእግዚአብሔር አብ ጋር።


ቅዱስ ሩፋኤል (በዕብራይስጥ: רָפָאֵל) ሲነበብ ሩፋኤል ፣ ከ፯ቱ ሊቀመላእክት መዐረጉ ሦሥተኛ ነው ። ሩፋኤል መላእከ ኃይል በግዕዝ :

  • ፈታሔ መኀፀን ወሰፋድል ።
  • መወለድ መንፈሳዊ ።
  • ወሐኪም ሰማያዊ ይባላል ።

የወላድ ማኀፀን እንዲፈታ ስለተሾመ ከጌታ አዋላጅ ብትኖርም ባትኖርም ሩፋኤል አይታጣም ፣ በምጥ ጊዜ ሴቶች ሁሉ በባላገር ያሉ መልኩን ያነግታሉ ማየ ጸሎቱንም ይጠጣሉ ቶሎም በፍጥነት ይወልዳሉ ።

ድርሳነ ሩፋኤል ክፍል ፩[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

፩ ፤ በአብ ስም አምነን አብ ወላዲ ብለን በወልድ ስም አምነን ወልድን ተወላዲ ብለን በመንፈስ ቅዱስ ስም አምነን መንፈስ ቅዱስን ሠራፂ ብለን ምንም ለአጠይቆ አካላት ሦስት ብለን በባሕርይ በሕልውና በመለኮት አንድ አምላክ ብለን አምነን አስቀድሞ በኅዳር ፲፪ ቀን እንደተናገርነው ክቡራን የሚሆኑ ከሰማያውያን ሊቃነ መላእክት ሦስተኛ የሚሆን የቅዱስ ሩፋኤል በዓለ ንግሥ በጳጉሜ ሦስት ቀን የሚከበርና የሚታሰብ መሆኑን እንናገራለን ።

፪ ፤ ይህም ዕለት በሊቀ ጳጳሱ በአባ ቴዎፍሎስ ዘመን እስክንድርያ በምትባል አገር ዳርቻ ባለች ደሴት በውስጧ ብዙ ተአምራት የተፈፀመባት በቅዱስ ሩፋኤል ስም የታነፀች ቤተ ክርስቲያን የተባረከችበትና የተቀደሰችበት ዕለት ነው ።

፫ ፤ ይህም የሆነው አንዲት በጣም ሀብታም የሆነች ሮማዊት የሮም ሀገር ሴት ንዑድ ክቡር የሚሆን የቅዱስ ሩፋኤልን ሥዕልና ልጆችዋን እንዲሁም ከባልዋ በውርስ ያገኘችውን ብዙ ገንዘብ ይዛ ወደ ሊቀ ጳጳሱ ወደ ቴዎፍሎስ ዘንድ በመጣችበት ጊዜ ነበር ።

፬ ፤ ከመጣችም በኋላ በሊቀ ጳጳሱ ቤት ፊት ለፊት ያለውን ኮረብታ አስቆፈረችና ከመሬት ውስጥ ወርቅ የተከማቸበት ሣጥን ተገኘ ።

፭ ፤ ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሱ አባ ቴዎፍሎስ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን አሣነፀ ከነዚህም ውስጥ እስክንድርያ በምትባል አገር ዳርቻ ባለች ደሴት ላይ ክቡር በሚሆን በቅዱስ ሩፋኤል ስም የተሠራች ቤተክርስቲያን ትገኝበት ነበር ሥራዋንም ሠርቶ በፈፀመ ጊዜ በዚችው ዕለት በታላቅ ክብር አክብሮ ባረካት ቀደሳትም ።

፮ ፤ ምእመናኑ ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ እየጸለዩ ሳሉ እንሆ ቤተ ክርስቲያኒቱ ተንቀጠቀጠች ተናወጠች ታወከች። በመረመሩ ጊዜም ከባሕር አንበሪዎች በአንዱ ታላቃ ዓሣ አንበሪ ላይ ተሰርታ አገኙዋት ከቦታው ሳይንቀሳቀስ ኑሮ ነበር ።

፯ ፤ በላዩ የሰው ሁሉ እግር በበዛና በከበደው ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አወከው። ምእምናኑና ሊቀ ጳጳሳቱ አንድ ሆነው ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ጮሁ ። ወደ ከበረ መልአክ ወደ ሩፋኤልም ለመኑ ።

፰ ፤ ያን ጊዜ ልዑል እግዚአብሔር የከበረ መልአክ ሩፋኤልን ላከው ሰዎችንም ይቅር አላቸው ። በእግዚአብሔር ትእዛዝ ጸንተህ ቁም ከቦታህም አትንቀሳቀስ ብሎ ዓሣውን በጦር ወጋ ።

ቅዱስ ሩፋኤል ዓሳአንበሪውን እንደወጋው

ያን ጊዜም ዓሣ አንበሪ በቦታው ጸንቶ ቆመ አልተቀንቀሳቀሰም ። በዚችም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙ ድንቅ ተአምራት ተደረገ ። ለታመሙትም ታላቅ ድኅነት ሆነ ። ይህችም ቤተ ክርስቲያን እስላሞች እስከ ነገሡ ደረስ እንደዚህ ኖረች ።

፱ ፤ እስላሞች በነገሡ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈረሰች ዓሣ አንበሪውም ተንቀሳቀሰ ዳግመኛም ባሕሩ ተናወጸ በዚያ ቦታ ላይ የነበሩትን ብዙ ሰዎችም አሰጠማቸው ።

፲ ፤ የከበረ የመላእክት አለቃ የሩፋኤል ይቅርታ ልመናውና በረከቱ ከኛ ጋር ይኑር ። ለዘለዓለሙ አሜን ።

፲፩ ፤ የሰውን ልብ ደስ የሚያሰኛት ልዩ ስጦታ ላለው ለሩፋኤል ሰላም እላለሁ ደዌ ኃጢያትን ይፈውሳል ቁስለ ነፍስንም ያክማልና ። ስለዚህም እውነትን የሚከተሉ ይቅርታን ያገኛሉ ። በተንኮል ጎዳና የሚግዋዙ ግን በነፍሳቸውም በሥጋቸውም ጥፋትን ያስከትላሉ ሲል ለጦቢት አስረዳው አስገነዘበው ።

ድርሳነ ሩፋኤል ክፍል ፪[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

፲፪ ፤ አባ ዮሐንስ የተናገረው የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤል የክብሩ ዜና ዳግምኛም የቁስጥንጥንያው አገር ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስ ይህን የገናናነቱን ነገር ተናገረ፣ ደገኛውን ንጉሥ አኖሬዎስን አንዲህ አለው ንጉሥ ሆይ ዕወቅ እኛ ወደ አንተ ልንመጣ በመረከብ ተሳፍረን ነበርና ስንሔድ ሳለን በከበረች በቀዳሚት ቀን በደሴት ላይ የተሰራች አንዲት ቤተ ክርስቲያን አየን። ከወደቡ ደረስን በዕለተ እሑድም ሥጋውን ደሙን እንቀበል ዘንድ ከዚያ አደርን ። በዚች ቤተ ክርስቲያን አጠገብም ትንሽ ገዳም አገኘን ። በውስጧም መነኮሳት አሉ ። ክብር ይግባውና በእግዚአብሔር ትእዛዝ ወደ እነሱ ደረስን ። መነኮሳቱንም ከቀደሙት ሰዎች ዘመን የተላለፈ ብሉይ መጽሐፍ ከእናንተ ዘንድ እንደ አለ እመከርበት ዘንድ ስጡኝ አልኳቸው ። አንሆ በቤተ ክርስቲያን ብዙ መጻሕፍት አሉ ትርጓሜያቸውን ግን እኛ አናውቅም ብለው መለሱልኝ ።

፲፫ ፤ አምጡልኝ ልያቸው አልኳቸው አመጡልኝ ። መረመርኳቸው ። እግዚአብሔር በደቀ መዛሙርቱ ፊት ስለ አደረጋቸው ድንቅ ሥራዎችና ተአምራቶች ስለ ሰማያትና ስለ ምድር ተፈጥሮ ይህ ዓለም እስኪያልፍ ድረስ ያለውን የሚናገር ጽሑፍ አገኘሁ ።

፲፬ ፤ እኔ መጻሕፍትን ሁሉ ስመረምር ንጹሐን አባቶቻችን ሐዋርያት ስለ ሰባቱ የመላእክት አለቆች ሹመት የጻፉትን አንድ መጽሐፍ አገኙ። እንዲህ ይላል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በደብረ ዘይት ተቀምጦ የጌትነቱን ሚሥጢር ሲገልጥላቸው ሳለ ሐዋርያትም እንዲህ ብለው ለመኑት።

፲፭ ፤ ጌታችን ፈጣሪያችን እግዚአብሔር ሆይ የከበረ መልአክ የሩፋኤልን ክብር ታስረዳን ዘንድ አንለምንሃለን። በመቸ ወር በመቸ ቀን ሾምከው። ከባልንጀሮቹ ከመላእክት አለቆች ጋር የተተካከለ ነውን ። የሱን ነገር ለዓለም ሁሉ እናስተምር (እንናገር) ዘንድ ።

፲፮ ፤ በታናሹ ወር በሦስተኛው ቀን በዓሉን አድርጉለት ይኸውም ጳጉሜ ነው አላቸው ።

፲፯ ፤ ስለዚህም በዚህ መልአክ አማላጅነት ከእግዚአብሔር ይቅርታ ቸርነት ያገኙ ዘንድ በችግራቸውና ጭንቀታቸው ጊዜ በዚች ቀን ሰዎች ሁሉ ልመናቸውን ያቀርቡለታል ።

፲፰ ፤ ያን ጊዜም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስቱን የመላእክት አለቆች ሚካኤልን ገብርኤልን ሩፋኤልን ከሦስተኛዪቱ ሰማይ ይመጡ ዘንድ አዘዛቸው ። እነሱም ደስ እያላቸው መጥተው ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ፊት ሰገዱ ።

፲፱ ፤ በዚያም ጊዜ ጌታችንም ሩፋኤልን ጠቀሰውና ፣ የክብርህን ታላቅነት ያውቁ ዘንድ ስምህን ለሐዋርያት ንገራቸው አለው ።

፳ ፤ የመላእክት አለቃ ሩፋኤልም ሐዋርያትን እንዲህ አላቸው እኔ ሩፋኤል እባላለሁ የዋህ ነኝ ከመላእክት አለቆችም ሦስተኛ ነኝ ። የመላእክት አለቃ ሚካኤል ግን ከቀድሞ ጀምሮ የመላእክት ሁሉ አለቃ ነው ስሙም ዕፁብ ድንቅ ፣ ይቅር ባይ ማለት ነው።

፳፩ ፤ ገብርኤልም ሁለተኛ የመላእክት አለቃ ነው። ይኸውም አምላክ ሰው ሆነ (አምላክ ወሰብ) እየተባለ ይጠራል ። የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መወለድ ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም ይነግራት ዘንድ የተላከ ነው ።

፳፪ ፤ እኔም አንደ ነገርኳችሁ ስሜ ሩፋኤል እባላለሁ ልቡናን ደስ የሚሰኝ የዋህ ቸር ለኃጥአን የምራራ ነኝ። ሰዎችን ስለ ኃጢኣታቸው ወደ እግዚአብሔር አላሳጣቸውም ። ስለ ደግነቴ ሰውን ስለመውደዴ የሚራዱ መላእክትን ወደ ኃጥአን ነፍስ እልካለሁ አንጂ ። ከኃጢአታቸውም እስኪመለሱ ድረስ እታገሳቸዋለሁ በደላቸውንም ይቅር እላቸዋለሁ ።

፳፫ ፤ እግዚአብሔር በሐያ ሦስቱ ነገደ መላእክት ላይ የሾመኝ እኔ ሩፋኤል ነኝ ። እግዚአብሔር አብን ይቅር ባይ ልጁን ደስ የሚያሰኝ መንፈስ ቅዱስን አመሰግነዋለሁ ።

፳፬ ፤ በደብረ ጸዮን በሺው ዓመት ሠርግ ለወዳጆቹ በጎ ነገርን እሰጣቸው ዘንድ እግዚአብሔር ያዘዘኝ እኔ ሩፋኤል ነኝ ። በንጹሕ ዙፋኑ ላይ ተቀምጦ ከእርሱ ጋር ለተቀመጡ የዕውነተኛ ክብርን ከተመላ ጽዋ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚያጠጣቸው ጊዜ ።

፳፭ ፤ በዚያች በድኅነትና በደስታ ቀን ለክርስቲያን ከዕፀ ሕይወት እሰጣቸው ዘንደ እግዚአብሔር የአዘዘኝ እኔ ሩፋኤል ነኝ።

፳፮ ፤ ሰማያውያን መዛግብት በእጄ የሚጠበቁ እኔ ሩፋኤል ነኝ። እግዚአብሔር እንደ አዘዘኝ ልከፍታቸውና ልዘጋቸው የምችል አኔ ነኝ ።

፳፯ ፤ አንድ ሰው በእኔ ስም በዚህ ዓለም መከራ ለአገኘው ሰው በጎ ቢያደርግ ። የሹመቴን መጽሐፍ የሚጽፍ በእኔ ስምም ከድኆቹ አንዱን የሚያስብ ሰው ቢኖር ጳጉሜን ሦስት ቀን በምትሆነው እግዚአብሔር እኔን ከሾመባት በመላእክት ሹመት ባከበረባት በመታሰቢያዬ ቀን ፍሬ ግብር ዕጣን ጧፍ የሚሰጥ ቢኖር እኔ ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም አስኪገቡ ድረስ በብርሃን ሠረገላ አወጣቸዋለሁ።

፳፰ ፤ በዚህ ዓለም ፈጽሞ እንደሱ ያለ የማይገኝ ሽታው እጅግ የተወደደ የሽቱ አበባ በእጃቸው እንዲይዙ አደርጋለሁ።

፳፱ ፤ እግዚአብሔር የመረጣቸው ሐዋርያት ሆይ በእግዚአብሔር ፊት እስክትቆሙ ድረስ ሁል ጊዜ እጠብቃችሁ እረዳችሁ ዘንድ ከእኔ ረድኤትን እሹ ። በመላው ዓለም ላሉ ሰዎችም መታሰቢያዬን ያደርጉ ዘንድ ንገሩ አስተምሩ ። አኔ ስለነሱ ወደ እግዚአብሔር እማልዳለሁ ከመከራችውም አድናቸዋለሁ ቅጣትንም ፈጽሞ አያዩም ። ይህን ብሎ ቅዱስ ሩፋኤል በእግዚአብሔር ፊት ሰገደ ወደ ሰማያትም ዐረገ ።

፴ ፤ ሐዋርያትም ጌታችን እንደአዘዛቸው በዓሉን አከበሩ ዜናውን አስተማሩ። ስለዚህም ሰዎች በኃዘናቸውና በመከራቸው ጊዜ ይጠሩታል። በዚህ መልአክ አማላጅነት ከእግዚአብሔር ዘንድ ጸጋንና ይቅርታን ያገኙ ዘንድ። የመላእክት አለቃ በዚህ የከበረ መልአክ የሩፋኤል ተአምራት ብዙ ነው። እኛም ሁል ጊዜ መታሰቢያውን እናደርግ ዘንድ ይገባናል ። እሱ ስለእኛ ወደ እግዚአብሔር ይማልደናል። አማላጅነቱ ጸሎቱ በረከቱ ከእኛ ጋር ይኑረ ለዘለዓለሙ አሜን።

ዘአቅረብኩ ማኅሌተ በል።

ማጣቀሻ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

መጽሐፈ ጦቢት ስለ ቅዱስ ሩፋኤል በሰፊው ያስተምራል በተለይ ጦቢት ፥ ፲፪-፲፭ ።

በተጨማሪም መጽሐፈ ሄኖክ ይመልከቱ ።