አባል:Hinstein

ከውክፔዲያ

ሀገሬልመርቅሽ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሀገሬ
ውሃ ወደላይ አይፈስ ግን ይፈሳል ካሰቡበት፣
በቀጭን ቧንቧ ከላኩት ግፊት ጉልበት ከጫኑበት::
እንግዲያውስ እኔም ወደላይ ልመርቅሻ ሀገሬ፣
የበረከት ውሃን ላፍስስ ላርስሽ በንግግሬ::

ሀገሬ
የሞቱ ልጆችሽ ይደሰቱ በውድቀታቸው ስላሰቡን፣
በብርታታቸው አርግዘው በድካም ስለወለዱን::
እንኪያስ ደግነታቸው መልካሙ ስራ ይነገር፣
ጥፋቱ ለትምህርት ሆኖ ልማቱ ለትውልድ ይቅር ::

ሀገሬ
አፈርሽ ሲያዩት ይመር መሬትሽ ለዘር ይታረስ፣
ወንዝሽ ህይወት አፍስሶ ደረቁን ምድር ያረስርስ::
አዕዋፍ ሰላምን ፍቅርን ይዘምሩ፣
በየብስ በባህር ያሉት እንደዚሁ ይናገሩ::
እፅዋት ዛፍ ሳር ቅጠሉ በደስታ አየር ይወዝወዙ፣
ዝናብ ፀሃይ ነፋሳቱ ለልጆችሽ ይታዘዙ::

ሀገሬ
መረከብ አየር ቢሰጡት አገሩን ጥሎ የማይበር፣
በጅመንሻ ማባበያ ማንነቱን የማይቀይር::
አባት እናቱ ያስይዙትን ቋንቋ በመናገሩ፣
የቆሽሽ የማይመስለው ጠቁሮ በመፈጠሩ::
ባልተሳካው ባለሆነለት አምርሮ የማይናገር፣
ባወጣሽለት ስሙ በመጠሪያው የማያፍር፣
ልጅ ይስጥሽ እናቱን አንቺን ከልቡ የሚያፈቅር::
ሀገሬ
ሚጠሉሽ ሚንቁሽን ግድ የለም ዝምበያቸው፣
ግዜው ስለደረሰ ግዜው ሊበቀላቸው::
ስለዚህ
የሚጠላውን የሚወድ የሚንቅን የሚያከብር፣
የወጋ፟ውን የሚረሳ የበደለውን የሚምር፣
ለጨከነበት የሚራራ ባላንጣውን የሚመክር፣
ደመኛውን ይቅር ብሎ ቁጣውን አብርዶ ሚያድር::
ልብን

ደግሞ በችግሩ የታመነ ቃሉን ፍፁም አክባሪ፣
ፆሙን ሰንብቶ ሚሞት ለተናገረው ነዋሪ::
“ኢትዮጵያዊ ነኝ” ለማለት ሁለት ሶስቴ ማያስብ፣
ቋንቋ ታሪኩን ከመውደድ ጧት ማታ ሚንገበገብ::
ስራን ፈጣሪ መፍጠርን ካምላኩ የተማረ፣
ለራሱ ተስቆንቁኖ ከጓደኛው ታልሰወረ::
መፍትሄን የሚሻ ብርቱ ተፈትኖ የነጠረ፣
በፈጣሪው መና፟ እንጂ በምፅዋት ያልወፈረ::
ህሊናን

“እህ᎗ህ?” አትይኝም ሀገሬ? ሀገሬ ልመርቅሽ፣
ሰላምታን ለሚሰጥሽ “እግዜር ይመስገን” እንዳልሽ፣
እንዲህ ያለውን ህሊና እንዲህ ያለውን ልብ ይስጥሽ::
አሜን