እሣቱ ተሰማ

ከውክፔዲያ
እሣቱ ተሰማ

እሣቱ ተሰማ ታዋቂ ኢትዮጵያዊ ዘፋኝ ነው።

እሣቱ ተሰማ በ፲፱፻፴፩ ዓ.ም. በሲዳሞ ክፍለ ሀገር ተወለደ። በ፲፱፻፴፬ ዓ.ም. ወደ አዲስ አበባ መጥቶ ዘመድና ረዳት ስላልነበረው በስድስት ኪሎ አካባቢ ጫማ እየጠረገ እራሱን ማስተዳደር ጀመረ። በልጅነት ጊዜው በበዓላትና በሠርግ ላይ በድምፁ ይጫወት ነበር። በ፲፱፻፵፮ ዓ.ም. መባቻ ላይ በቀድሞው የክብር ዘበኛ የሙዚቃ ክፍል ውስጥ የመጀመሪያ ድምፃዊ ሆኖ ለመቀጠር የበቃውና ከኢትዮጵያ ቀደምት የሙዚቃ ሰዎች መካከል አንዱ ሊሆን ችሏል።

በ፲፱፻፵፰ ዓ.ም. በኢትዮጵያ የሬዲዮ አገልግሎት ሲጀምር «እንኩ እንኩ ፅጌሬዳ፣ አጥቻት ሳልጎዳ» በሚለው ዘፈኑ የመጀመሪያው ድምፃዊና የሬዲዮ ጣቢያው መራቂ ለመሆን በቅቷል። አንጋፋው ከያኒና ለሀገር ባህል ዜማ ከፍ ያለ ፍቅር የነበረው እሣቱ ከ፪፻ በላይ ዘፈኖችን የተጫወተ ሲሆን በራሱ ዜማና ድርሰት ተጫውቷቸው በሕዝብ ዘንድ ከተወደዱለት መካከል «ድማሜ»፣ «ትዳር ስመኝ»፣ እና «ምነው መንገብገቤ» ድንቅ የሥራ ውጤቶቹ ናቸው።

እሣቱ በሙያው ኩሩ የነበረና ነባር ድምፃዊ የነበረ ሲሆን በጤናው መታወክ ምክንያት ከሚወደውና ከሚያፈቅረው አሳድጎም እዚህ ካደረሰው የሙዚቃ ክፍል በ፲፱፻፸ ዓ.ም. በሐኪም ፈቃድ ተሰናበተ።

ማጣቀሻ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]