ኮሶ በሽታ

ከውክፔዲያ

የኮሶ በሽታ ከተለያዩ የሰውና እንስሳት የትል በሽታዎች ኣንዱ ነው። ከሰው ኮሶ በሽታዎች ኢትዮጵያ ውስጥ በሰፊው የታወቀው ሕዋስ ቲንያ ሳጂናታ ይባላል። በሽታው ሰውን የሚይዘው ያልተመረመር ጥሬ የከብት ሥጋ በመብላት ሲሆን በሽታውን የሚያስከትለው እንቁላል ጥሬ ሥጋ ውስጥ ያለማጉሊያ መሣሪያ በዓይን ይታያል።

ኣንድ ሰው የኮሶ እንቁላል ያለበትን ጥሬ ስጋ ከበላ በኋላ እንቁላሉ ይፈለፈልና ኣንጀት ላይ በመንጠልጠል ከኣንገቱ ማደግ ይጀምራል። የኮሶ ትል ርዝመት ከሰው ይበልጣል። በቂ እድሜ ከኣገኘ በኋላ ብዙ እንቁላሎች ያሉት እየተቀነጠሱ ሹጥ ሆነው ከሰገራ ጋር ወይም ለብቻቸው ይወጣሉ። የኮሶ መድኃኒት ተወስዶ ከእንጀት ተነቅሎ ወይም ከኣንገቱ ተበጥሶ ሲወጣ ኣሻረኝ ይባላል። የኮሶው መድኃኒት ኮሶውን ከኣንጀት ፈንቅሎ ካላወጣው ግን እንደገና ከኣንገቱ በመጀመር ያድግና ሌላ የሹጥ ዙር መታየት ሲጀምር ኮሶ ታየኝ ይባላል። ስለዚህ ኣንድ ሰው ኮሶ ከታየው ትሉን ከኣንገቱ ፈንቅሎ የሚያወጣ መድኃኒት መውሰድ ኣለበት። ኣንድ ሹጥ ውስጥ ብዙ የኮሶ እንቁላሎች ስለኣሉት ኣንድ ኮሶም ብዙ ዓመታት ስለሚኖር ብዙ ሺህ እንቁላሎች ይኖራሉ። ኣንድ ሰው ሰገራውን ሜዳ ላይ ሲወጣ ሹጡ ፀሓይ ሲሞቀው ይፈነዳና ብዙ ሺህ እንቁላሎቹ ሳር ላይ ይረጫሉ። ከብቶች እንቁላሎቹን ከሳሩ ጋር ሲበሉ ተፈልፍለው ሆድ ዕቃቸውን ስርስረው የከብት ስጋ ውስጥ ተቀምጠው ጥሬ ስጋ የሚበላ ሰው እስኪመጣ ይጠብቃሉ። የግዴታ ሰገራ ሜዳ ውስጥ መውጣት ካስፈለገ ትንሽ ጉድጓድ ቆፍሮ ከእዚያ ሰገራውን በኣፈር መሸፈን እንቁላሎቹ እንዳይበተኑ ይጠቅማል። [1]

ኮሶ የሰው እንጂ የእንስሳት በሽታ ኣይደለም። የጥንት ሰዎች የዱር እንስሳትን ሲበሉ የያዛቸውን የኮሶ በሽታ በየኣካቢያቸው በመጸዳዳት ለለማዳ እንስሳት ኣስተላለፉ እየተባሉ ይታማሉ። ሥጋን ማብሰል የኮሶውን እንቁላል ይገድላል። የኮሶ እንቁላል ያለበትን የከብት ሥጋ ለሁለት ሳምንታት ፍሪዝ ማድረግም ይገድላቸዋል።

የውጭ መያያዣዎች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]