የሐዋርያት ሥራ ፰

ከውክፔዲያ
የሐዋርያት ሥራ ፰
ፊሊጶስ ኢትዮጵያዊውን ጃንደረባ ሲያጠምቀው ።
አጭር መግለጫ
ፀሐፊ ቅዱስ ሉቃስ
የመጽሐፍ ዐርስት የሐዋርያት ሥራ
የሚገኘው በአዲስ ኪዳን ፭ኛው መጽሐፍ
መደብ የቤተክርስቲያን ታሪክ
ኢየሱስ ክርስቶስና ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ሲጠመቁ የሚያሳይ የመስታውት ስዕልCathedral of Incarnation(Garden City,New York)


የሐዋርያት ሥራ ፰ በአዲስ ኪዳን ፭ኛ መጽሐፍ "የሐዋርያት ሥራ" ውስጥ የሚገኝ ሲሆን "ስምንተኛው ምዕራፍ" ነው ። የሚያተኩረውም በፊሊጶስ (አርድዕት) ሰባኪነት የተከናወኑ ሥራዎችና በተለይ በኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ማመንና መጠመቅ (ቁ፣፳፮) ምስክር ላይ ነው ። ይህም በ፵ ንዑስ ክፍሎች ይካተታል ።

የሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ ፰

ቁጥር ፩ - ፲[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

1፤በዚያን፡ቀንም፡በኢየሩሳሌም፡ባለች፡ቤተ፡ክርስቲያን፡ላይ፡ታላቅ፡ስደት፡ኾነ፤ዅሉም፡ከሐዋርያትም፡ በቀር፡ወደ፡ይሁዳና፡ወደሰማርያ፡አገሮች፡ተበተኑ። 2፤በጸሎትም፡የተጉ፡ሰዎች፡እስጢፋኖስን፡ቀበሩት፡ታላቅ፡ልቅሶም፡አለቀሱለት። 3፤ሳውል፡ግን፡ቤተ፡ክርስቲያንን፡ያፈርስ፡ነበር፤ወደዅሉም፡ቤት፡እየገባ፡ወንዶችንም፡ሴቶችንም፡እየጐተተ፡ ወደ፡ወህኒ፡አሳልፎ፡ይሰጥ፡ነበር። 4፤የተበተኑትም፡ቃሉን፡እየሰበኩ፡ዞሩ። 5፤ፊልጶስም፡ወደሰማርያ፡ከተማ፡ወርዶ፡ክርስቶስን፡ሰበከላቸው። 6፤ሕዝቡም፡የፊልጶስን፡ቃል፡በሰሙ፡ጊዜ፡ያደርጋት፡የነበረውንም፡ምልክት፡ባዩ፡ጊዜ፥የተናገረውን፡ባንድ፡ልብ፡አደመጡ። 7፤ርኩሳን፡መናፍስት፡በታላቅ፡ድምፅ፡እየጮኹ፡ከብዙ፡ሰዎች፡ይወጡ፡ነበርና፤ብዙም፡ሽባዎችና፡ ዐንካሳዎች፡ተፈወሱ፤ 8፤በዚያችም፡ከተማ፡ታላቅ፡ደስታ፡ኾነ። 9፤ሲሞን፡የሚሉት፡አንድ፡ሰው፡ግን፦እኔ፡ታላቅ፡ነኝ፡ብሎ፥እየጠነቈለ፡የሰማርያንም፡ወገን፡እያስገረመ፡ ቀድሞ፡በከተማ፡ነበረ። 10፤ከታናናሾችም፡ዠምሮ፡እስከ፡ታላላቆቹ፡ድረስ፦ታላቁ፡የእግዚአብሔር፡ኀይል፡ይህ፡ነው፡እያሉ፡ዅሉ፡ ያደምጡት፡ነበር።

ቁጥር ፲፩ - ፳[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

11፤ከብዙ፡ዘመንም፡ዠምሮ፡በጥንቈላ፡ስላስገረማቸው፡ያደምጡት፡ነበር። 12፤ነገር፡ግን፥ስለእግዚአብሔር፡መንግሥትና፡ስለኢየሱስ፡ክርስቶስ፡ስም፡እየሰበከላቸው፡ፊልጶስን፡ባመኑት፡ ጊዜ፥ወንዶችም፡ሴቶችም፡ተጠመቁ። 13፤ሲሞንም፡ደግሞ፡ራሱ፡አመነ፤ተጠምቆም፡ከፊልጶስ፡ጋራ፡ይተባበር፡ነበር፤የሚደረገውንም፡ምልክትና፡ ታላቅ፡ተኣምራት፡ባየ፡ጊዜ፡ተገረመ። 14፤በኢየሩሳሌምም፡የነበሩት፡ሐዋርያት፡የሰማርያ፡ሰዎች፡የእግዚአብሔርን፡ቃል፡እንደተቀበሉ፡ሰምተው፡ ጴጥሮስንና፡ዮሐንስን፡ሰደዱላቸው። 15፤እነርሱም፡በወረዱ፡ጊዜ፡መንፈስ፡ቅዱስን፡ይቀበሉ፡ዘንድ፡ጸለዩላቸው፤ 16፤በጌታ፡በኢየሱስ፡ስም፡ብቻ፡ተጠምቀው፡ነበር፡እንጂ፡ከነርሱ፡ባንዱ፡ላይ፡ስንኳ፡ገና፡አልወረደም፡ ነበርና። 17፤በዚያን፡ጊዜ፡እጃቸውን፡ጫኑባቸው፡መንፈስ፡ቅዱስንም፡ተቀበሉ። 18፤ሲሞንም፡በሐዋርያት፡እጅ፡መጫን፡መንፈስ፡ቅዱስ፡እንዲሰጥ፡ባየ፡ጊዜ፥ገንዘብ፡አመጣላቸውና፦ 19፤እጄን፡የምጭንበት፡ዅሉ፡መንፈስ፡ቅዱስን፡ይቀበል፡ዘንድ፡ለእኔ፡ደግሞ፡ይህን፡ሥልጣን፡ስጡኝ፡አለ። 20፤ጴጥሮስ፡ግን፡እንዲህ፡አለው፦የእግዚአብሔርን፡ስጦታ፡በገንዘብ፡እንድታገኝ፡ዐስበኻልና፥ብርኽ፡ ከአንተ፡ጋራ፡ይጥፋ።

ቁጥር ፳፩ - ፴[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

21፤ልብኽ፡በእግዚአብሔር፡ፊት፡የቀና፡አይደለምና፡ከዚህ፡ነገር፡ዕድል፡ወይም፡ፈንታ፡የለኽም። 22፤እንግዲህ፡ስለዚህ፡ክፋትኽ፡ንስሓ፡ግባ፥ምናልባትም፡የልብኽን፡ዐሳብ፡ይቅር፡ይልኽ፡እንደ፡ኾነ፡ወደ፡ እግዚአብሔር፡ለምን፤ 23፤በመራራ፡መርዝና፡በዐመፅ፡እስራት፡እንዳለኽ፡አይኻለኹና። 24፤ሲሞንም፡መልሶ፦ካላችኹት፡አንዳች፡እንዳይደርስብኝ፡እናንተው፡ወደ፡ጌታ፡ለምኑልኝ፡አላቸው። 25፤እነርሱም፡ከመሰከሩና፡የጌታን፡ቃል፡ከተናገሩ፡በዃላ፡ወደ፡ኢየሩሳሌም፡ ተመለሱ፤በሳምራውያን፡በብዙ፡መንደሮችም፡ወንጌልን፡ሰበኩ። 26፤የጌታም፡መልአክ፡ፊልጶስን፦ተነሥተኽ፡በደቡብ፡በኩል፡ከኢየሩሳሌም፡ወደ፡ጋዛ፡ወደሚያወርደው፡ ምድረ፡በዳ፡ወደ፡ኾነ፡መንገድ፡ኺድ፡አለው። 27፤ተነሥቶም፡ኼደ።እንሆም፥ህንደኬ፡የተባለች፡የኢትዮጵያ፡ንግሥት፡አዛዥና፡ጃን፡ደረባ፡የነበረ፡ በገንዘቧም፡ዅሉ፡የሠለጠነ፡አንድ፡የኢትዮጵያ፡ሰው፡ሊሰግድ፡ወደ፡ኢየሩሳሌም፡መጥቶ፡ነበር፤ 28፤ሲመለስም፡በሠረገላ፡ተቀምጦ፡የነቢዩን፡የኢሳይያስን፡መጽሐፍ፡ያነብ፡ነበር። 29፤መንፈስም፡ፊልጶስን፦ወደዚህ፡ሠረገላ፡ቅረብና፡ተገናኝ፡አለው። 30፤ፊልጶስም፡ሮጦ፡የነቢዩን፡የኢሳይያስን፡መጽሐፍ፡ሲያነብ፡ሰማና፦በእውኑ፡የምታነበውን፡ ታስተውለዋለኽን፧አለው።

ቁጥር ፴፩ - ፵[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

31፤ርሱም፦የሚመራኝ፡ሳይኖር፡ይህ፡እንዴት፡ይቻለኛል፧አለው።ወጥቶም፡ከርሱ፡ጋራ፡ይቀመጥ፡ዘንድ፡ ፊልጶስን፡ለመነው። 32፤ያነበውም፡የነበረ፡የመጽሐፉ፡ክፍል፡ይህ፡ነበረ፤እንደ፡በግ፡ወደ፡መታረድ፡ተነዳ፥የበግ፡ጠቦትም፡ በሸላቹ፡ፊት፡ዝም፡እንደሚል፥እንዲሁ፡አፉን፡አልከፈተም። 33፤በውርደቱ፡ፍርዱ፡ተወገደ፤ሕይወቱ፡ከምድር፡ተወግዳለችና፡ትውልዱንስ፡ማን፡ይናገራል፧ 34፤ጃን፡ደረባውም፡ለፊልጶስ፡መልሶ፦እባክኽ፥ነቢዩ፡ይህን፡ስለ፡ማን፡ይናገራል፧ስለ፡ራሱ፡ነውን፡ ወይስ፡ስለ፡ሌላ፧አለው። 35፤ፊልጶስም፡አፉን፡ከፈተ፥ከዚህም፡መጽሐፍ፡ዠምሮ፡ስለ፡ኢየሱስ፡ወንጌልን፡ሰበከለት። 36፤በመንገድም፡ሲኼዱ፡ወደ፡ውሃ፡ደረሱ፤ጃን፡ደረባውም፦እንሆ፥ውሃ፤እንዳልጠመቅ፡የሚከለክለኝ፡ምንድር፡ነው፧አለው። 37፤ፊልጶስም፦በፍጹም፡ልብኽ፡ብታምን፥ተፈቅዷል፡አለው።መልሶም፦ኢየሱስ፡ክርስቶስ፡የእግዚአብሔር፡ ልጅ፡እንደ፡ኾነ፡አምናለኹ፡አለ። 38፤ሠረገላውም፡ይቆም፡ዘንድ፡አዘዘ፥ፊልጶስና፡ጃን፡ደረባው፡ኹለቱም፡ወደ፡ውሃ፡ወረዱ፥አጠመቀውም። 39፤ከውሃውም፡ከወጡ፡በዃላ፡የጌታ፡መንፈስ፡ፊልጶስን፡ነጠቀው፤ጃን፡ደረባውም፡ኹለተኛ፡ አላየውም፥ደስ፡ብሎት፡መንገዱን፡ይኼድ፡ነበርና። 40፤ፊልጶስ፡ግን፡በአዛጦን፡ተገኘ፥ወደ፡ቂሳርያም፡እስኪመጣ፡ድረስ፡እየዞረ፡በከተማዎች፡ዅሉ፡ወንጌልን፡ ይሰብክ፡ነበር።