ሳዳም ሁሴን
ሳዳም ሁሴን ኢራቅን ለረጅም ዓመታት የመራ አምባገነን ነበረ። የመጨረሻዎቹ የሳዳም ቀናቶች ጥቅምት 27,2006 ኩዌትን ወርረው የነበሩት የቀድሞው የኢራቅ መሪ ሳዳም ሁሴን በአገሪቱ ላይ መጠነ ሰፊ ጉዳት ማድረሳቸው ይነገራል፡፡ከ600 በላይ የነዳጅ ጉድጓዶች ላይ በለቀቁት እሳት ያስነሱትን ቃጠሎ ማስቆም የተቻለው የዛሬ 22 ዓመት በዛሬዋ እለት ነበር፡፡ ኢራቅ ኩዌትን እስከወረረችበት ጊዜ ድረስ በነበሩት 10 ዓመታት ከኢራን ጋር ንብረት ደምሳሽና ሕዝብ ጨራሽ ጦርነቶችን አካሄደች፡፡ የዘመኑ የኢራቅ ፕሬዝዳንት ሳዳም ሁሴን በነዳጅ ዘይት የምርት መጠንና ኮታ የተነሳ ከትንሿ ጐረቤታቸው ኩዌት ጋር አተካሮ ውስጥ የገቡት ወዲያውኑ ነበር፡፡ ኩዌት ከተቀመጠላት ኮታ በላይ ነዳጅ ለዓለም ገበያ እያቀረበች ነው ብለው በንዴት ጦፉ፡፡ ሳዳም ሌላም ሰበብ ፈጠሩ፡፡ በድምበር አካባቢ ከሩማይላ ጉድጓዳችን ነዳጃችንን እየዘረፈች ነው ሲሉ ነገር ፍለጋው ከፍ አደረጉት፡፡ ኩዌትን በነብር አየኝ ዛቱባት፡፡ ጦር ሠበቁባት፡፡ እንዳዛቱትም አልቀሩም ኩዌትን አጭር በሚባል ጊዜ ወርረው ያዟት፡፡ ሳዳም በዚህ ብቻ ሳይወሰኑ ኩዌትን 19ኛ ክፍለ ሃገሬ ነች ብለው ከኢራቅ መቀላቀላቸውን አወጁ፡፡ አብዛኛው ዓለም የሳዳምን ወረራ አወገዘው፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በፀጥታው ምክር ቤት በኩል ኢራቅ ያለ አንዳች ማንገራገር ኩዌትን ለቃ እንድትወጣ ወሰነ፡፡ አስጠነቀቀ፡፡ ሳዳም ሁሴን ክንዴን ሳልንተራስ እንዲህ አይነቱ ነገር በፍፁም የማይሞከር ነው ሲሉ ፎከሩ፡፡ ዲፕሎማሲያዊ ተማፅኞውን ከቁብ አልጣፉትም፡፡ ከዓለም ዙሪያ ይደርስባቸው የነበረውን ውግዘት ከምንም አልቆጥር አሉ፡፡ አሜሪካ በተባበሩት መንግስታት ውሳኔ ታግዛና የበረከቱ የዓለማችንን አገሮች በአጋርነት አሠልፋ በበረሃው ማዕበል ዘመቻ ኩዌትን ነፃ ወደማውጣቱ ዘመቻ ገባች፡፡ የበረሃው ማዕበል ዘመቻ ኩዌትን ወርሮ ይዞ በነበረው የኢራቅ ጦር ላይ ማዕበል ሆነበት፡፡ የኢራቅ ጦር ማዕበሉን መቋቋም ተሳነው፡፡ ሳይወድ በግዱ ኩዌትን ለቆ የሚወጣ መሆኑን በተረዳ ጊዜ ከ600 በላይ በሆኑት የነዳጅ ጉድጓዶቿ ላይ እሳት ለቀቀባቸው፡፡ ከቁጥጥር ውጭ ሆኖ የከረመው የድፍድፍ ነዳጅ ቃጠሎ ኩዌትን ብቻ ሳይሆን መላ ቀጣናውን በከባድ ጥቁር ጭስ ጭጋግ ሸፈነ፡፡ በተፈጥሮ አካባቢ ላይ ያደረሰው ብክለትም እጅግ ከፍተኛ ነበር ይባላል፡፡ ብዙዎችን ለመተንፈሻ አካል የጤና እክል ዳርጓል፡፡ ቃጠሎው ተጀምሮ እስኪያልቅ በየቀኑ 6 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ በላ፡፡ በገንዘብ ረገድ ኩዌትን 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ አደረሰባት፡፡ ቃጠሎው ለ1 ወር ሲዘልቅ የመጨረሻውን ጉድጓድ እሳተ ማጥፋት የተቻለው የዛሬ 22 ዓመት በዛሬዋ እለት ነበር፡፡ uhannes taye