ቦሌ ዓለም አቀፍ ጥያራ ጣቢያ

ከውክፔዲያ
የቀድሞው የበረራ ቁጥጥር እና መንገደኛ ማስተናገጂያ ሕንፃዎች
ቦሌ ዓለም አቀፍ የጥያራ ጣቢያ (አውሮፕላን ማረፊያ)
ቦሌ ዓለም አቀፍ የጥያራ ጣቢያ

ቦሌ ዓለም አቀፍ የጥያራ ጣቢያ (አውሮፕላን ማረፊያ)አዲስ አበባ ከተማ በደቡብ-ምሥራቅ አቅጣጫ ከአራዳ በስምንት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ የአገሪቱ ዋና አድማሳዊ የንግድና የግንኙነት በር ነው።

ፕሮፌሶር (ዲባቶ) መስፍን አረጋ፣ ቦሌ በኦሮምኛ ቋንቋ ትርጉሙ የሚፈረፈር ወይም የሚሰነጣጠቅ መሬት እንደሆነ ይነግሩናል። እውነትም የአካባቢው ገጸ-ምድር ለአየር ማረፊያ አመቺ ሜዳማ ቢሆንም መሬቱ ግን ረግራጋ እና መረሬ ነው።

በፋሺስት ኢጣልያ ዘመናት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ጥያራዎች (አየር ዠበቦች) ወደአገሪቱ መግባት የጀመሩት በንግሥት ዘውዲቱ ዘመን ሲሆን በአዲስ አበባ ዙሪያ በጃን ሜዳ እና አቃቂ ያርፉ እንደነበር በታሪክ ተዘግቧል። የመጀመሪያው ቋሚ የጥያራ ጣቢያ ግን የተሠራው በአምሥቱ የፋሺስት ዘመናት ሲሆን የካቲት ፳፬ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ/ም አክሱም አካባቢ ላይ ከነጥያራው ተከስክሶ በሞተው አብራሪያቸው፣ “ኢቮ ኦሊቬቲ” “Ivo Olivetti” ስም ሠይመውት የነበረው የልደታ የጥያራ ጣቢያ ነው።

በዚሁ በፋሺስት ወረራ ዘመን ‘አላ ሊቶሪያ’ (ALA LITTORIA S.A., R.) የተሰኘው ኩባንያ በአገር ውስጥ ከአዲስ አበባ ተነስቶ ነገሌን፤ ሞቃዲሾን፤ ድሬ ዳዋን፤ ጎራኄን፤ ጂቡቲን፤ አሰብን፤ ጂማን፣ ጋምቤላደምቢ ዶሎን፤ ጎንደርአስመራን፤ ደሴን፤ ለቀምትን እና አሶሳን የሚያገለግሉ የበረራ መሥመሮች ሲኖረው ከአድማስ ባሻገር ደግሞ ከተማዋን በካርቱም፣ ዋዲ ሃይፋ፤ ካይሮቤንጋዚ እና ሲራኩሳ አድርጎ ከሮማ ጋር የሚያገናኝ የበረራ መሥመርም ነበረው።

ከድል በኋላ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ከድል ወዲህ ልደታ ጥያራ ጣቢያ፤ የብሪታኒያ ጦር ኃይሎች ሲገለገሉበት ከቆየ በኋላ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ታኅሣሥ ፳፩ ቀን ፲፱፻፴፰ ዓ/ም ሲመሠረት ዋና ጣቢያው እዚያው ነበር። ዳሩ ግን የአየር መንገዱ አገልግሎት እየተስፋፋ ሲመጣና ትላልቅ ጄት አውሮፕላኖች እንደሚያስፈልጉት ግልጽ ሲሆን፣ የልደታ አየር ጣቢያ ብቃት እንደሌለው እና ለጄት አየር ዠበቦችም ማሳረፊያ የማይስማማ መሆኑ ታምኖበት የአማራጭ ሥፍራ ፍለጋ ተጀመረ። የአዲሱንም አየር ጣቢያ ዝርዝር ጥናት እንዲያዘጋጅ ውሉ ለአሜሪካዊው ‘አማን እና ዊትኒ’ (Amman, and Whitney) ኩባንያ ተሰጥቶ፤ ጥናቱ በ፲፱፻፶ ዓ/ም ተገባዶ አማራጩ ሥፍራ ቦሌ እንዲሆን ተወሰነ።

አዲሱ የጥያራ ጣቢያ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ቦሌ ሜዳማ አካባቢ ሲሆን፣ ለመነሳትም ሆነ ለማረፍ ከሚከለክሉ ተራራዎችና ጋራዎች የራቀ ሥፍራ ነው። የከተማዋም ወሰን በወቅቱ ከመስቀል አደባባይ እና ከኡራኤል በማያልፈት ጊዜ ለአየር ጣቢያው ቋሚነት የታጨው አካባቢ ከከተማ ውጭ እና ራቅ ያለ ድንግል ልማት ነበር። የአየር ጣቢያውን የግንባታ ወጪ ከአሜሪካዊው ‘ኤክስፖርት-ኢምፖርት’ ባንክ በተገኘ ብድር ተሸፍኖ ሥራው ተጀመረ።

የግንባታው ሥራ ጨርሶ ባይጠናቀቅም እንኳ፤ የማኮቦቢያው እና የበረራ ቁጥጥሩ ሕንፃ ሥራ እንደተገባደደ አየር መንገዱ የገዛቸውን ሁለት የጄት ዠበቦች (‘ቦይንግ ፯፻፯) ሲረከብ እዚሁ ቦሌ ጥያራ ጣቢያ ነበር ያረፉት። ጠቅላላ ግንባታው ተጠናቆ ሲያልቅ ኅዳር ፲፩ ቀን ፲፱፻፶፮ ዓ/ም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተብሎ፣ በንጉሠ ነገሥቱ ተመርቆ ተከፈተ።

እድሳት እና መስፋፋት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የአዲሶቹ ጄት ጥያራዎች ክብደት፤ የአየር መንገዱ በረራ መሥመሮች መባዛት እና የማኮብኮቢያው መሠረት ግንባታ ጥንካሬ ወትሮውንም አስተማማኝ አለመሆን፤ የተነጠፈውም መረሬ እና የመሸርሸር ጠባይ ባለው አፈር ላይ በመሆኑ ከአምሥት እና ስድስት ዓመታት አገልግሎት በኋላ የመሰነጣጠቅ ባህሪ ይታይበት ዠመር። ስለዚህ ማኮብኮቢያውን የማጠንከር እና ርዝመቱን በ ሰባት መቶ ሜትር የማራዘም ሥራ አዲስ በተገኘ ብድር ተጠናቋል።

የአገሪቱ የአየር ግልጋሎት እያደገ ሲሄድ መንገደኛ ማስተናገጃ ሕንፃዎቹም የግድ መስፋፋት እንደነበረባቸው ግልጽ ሲሆን ከጃፓን መንግሥት በተገኘ ብድር ተስፋፍቶ ኅዳር ፳፩ ቀን ፲፱፻፸ ዓ/ም ተመርቆ ተከፈተ።

ዋቢ ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  • (እንግሊዝኛ) FO 371/178551 Annual Review of 1963

From Mr J W Russell – Addis Abeba to Mr Rab Butler (1st January, 1964) [1015/64]

Bole International Airport (ADD/HAAB), Addis Ababa, Ethiopia