የጥንቱ ኢትዮጵያ ገዢ መደብ

ከውክፔዲያ

የጥንቱ የኢትዮጵያ ገዢ መደብ የምንላቸው በዘውድ ስርዓቱ ውስጥ ስልጣን ኑሮዓቸው አገሪቱን የሚያስተዳድሩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ነው። እኒህ ክፍሎች በአራት ዋና ክፍሎች ይከፈላሉ፦-

፩- ንጉሠ ነገሥት ወይንም ዐፄ -- በድሮው ስርዓት፣ ንጉሠ ነገሥት ወይም ዐፄ የስልጣን ፍጽምና ነበረው። ስልዚህም በሁሉ ላይ ሙሉ፣ ይግባኝ የማይባልበት ስልጣን ነበረው።

፪- መሳፍንት -- ከሌሎች መሳፍንት ወይም ከንጉስ ቤተሰብ በመወለዳቸው ምክያት ስልጣን የነበራቸው ናቸው። የኒህ ስልጣን ከሁሉ በላይ ግን ከንጉሡ በታች ነበር።

፫- መኳንንት -- እሊህ በንጉሱ ጉልት ተሰጥቷቸው ስልጣናቸው የታወቀላቸው ናቸው። ንጉሱ ፍጽም ስልጣን ስላለው የስልጣናቸው ዋስትና የንጉሱ መልካም ፈቃድ ነበር። ሲሻው ሊሽራቸው ሲሻው ሊሾማቸው ይችላል።

፬- ባላባት -- ከመኳንንት ስር ባላባት ይገኛሉ። እኒህ በጦር ስራ ወይም በንግድ ወይም በመሳሰሉት ስራቸው የጎጥ አስተዳደር ደረጃ የደረሱ ናቸው። ስልጣናቸው ውሱንና ከመኳንንት በታች ነበር።


መኳንንቶች (መሳፍንቶችንም ይጨምራል) ጉልታቸው ላይ ባላቸው መብት ምክንያት ከለተ ተለት የእጅ ስራ ተላቀው ኑሯቸውን ከሌላው ህብረተሰብ በበለጠ በተመቻቸ መልኩ ይመሩ ነበር። ስራ ቢሰሩም እንደ ፍርድ መስጠት፣ ጦርነት መሄድ የመሳሰሉ ነበሩ እንጂ እርሻና ሌሎች የእጅ ስራወችን አይሰሩም ነበር። ገበሬ መደብ ርስት ሲኖረው፣ ይህ ርስት በጉልት ስር ነበር። በሃሳብ ደረጃ፣ መኳንንት በንጉሱ መልካም ፈቃድ የሚተዳደሩ የነበሩ ይሁን እንጅ በተግባር ግን ጉልታቸውን እንደፈለጉ በመሸጥና ለልጅ ልጆቻቸው በማውረስ የራሳቸው የሆነ፣ ከንጉሱ መልካም ፈቃድ የማይመነጭ ሃይል ነበራቸው። ስለሆነም ከሞላ ጎደል የአውሮጳውያንን ፊውዳል ስርዓት የሚያንጸባርቅ ስርዓት ነበር የሚካሄደው።

መኳንንቶች በንጉሱ ፍጽም ስልጣን ላይ ሁለት ጊዜ ተነስተዋል። አንደኛው አጼ ዘድንግልን ከገደሉ በኋላ ሙሉ በሙሉ በዘር የሚመጣ የንጉስ ስልጣንን በመሻር በነርሱ የተመረጠ ንጉስ እንዲነግስ የተወያዩበት ሁኔታ ነበር። ነገር ግን ሱሰኒዮስ በመንገሱ አልተሳካላቸውም። ሁለተኛ ጊዜ ዘመነ መሳፍንትን ያስነሱበት ሁኔታ ተጠቃሽነት አለው።

ዋቢ ጽሑፍ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

  • Donald Crummey: Land and Society in the Christian Kingdom of Ethiopia from the Thirteenth to the Twentieth Century, (Urbana 2000)