ደብረ ታቦር (ዓመት በዓል)

ከውክፔዲያ

ደብረ ታቦር ወይንም ቡሄ! በመላው ሀገራችን በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን የሚከበር በዓል ሲሆን፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከምታከብራቸው ዐቢይ (ዋና) በዓላት አንዱ ይሄ 'ደብረ ታቦር' (የቡሄ በዓል ነው።)

የበዓሉ መሠረት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የዚህ በዓል መሠረት የክርስቲያን እምነት ሲሆን፣ ደብረ ታቦር በግዕዝ የታቦር ተራራ ማለት ነው፡፡ የታቦር ተራራ የሚገኘው አሁን ፍልስጥኤም ታሪክ ማዛባት ነውር ነው ታቦር ተራራ(ሃር ታቦር) ተወደደም ተጠላ እስራኤል በምትባል ጥንታዊትና ዘመናዊት ሀገር በሰሜኑ የእስራኤል አገር ይገኛል:፡ ደብረ ታቦር ወይንም የታቦር ተራራ ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስት ደቀመዛሙርቱን ይዞ ወደ ተራራው የወጣበትና ፊቱ እንደፀሐይ የበራበት ልብሱም እንደብርሃን ነጭ የሆነበት ቦታ ነው፡፡ ይህ ቦታ ጌታ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ተራራ ነው።

የማቴዎስ ወንገል ምዕራፍ ፲፯፦ ቁጥር ፩ እስከ ፭ " ከስድስት ቀንም በኋላ ኢየሱስ ጴጥሮስንና ያዕቆብን ወንድሙንም ዮሐንስን ይዞ ወደ ረጅም ተራራ ብቻቸውን አወጣቸው። በፊታቸውም ተለወጠ፥ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ፥ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ። እነሆም፥ ሙሴኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው። ጴጥሮስም መልሶ ኢየሱስን ጌታ ሆይ፥ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው፤ ብትወድስ፥ በዚህ ሦስት ዳስ አንዱን ለአንተ አንዱንም ለሙሴ አንዱንም ለኤልያስ እንሥራ አለ። እርሱም ገና ሲናገር፥ እነሆ፥ ብሩህ ደመና ጋረዳቸው፥ እነሆም፥ ከደመናው። በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት የሚል ድምፅ መጣ።"

ዓቢይ መሠረቱ ይሄ ሲሆን፣ በአገራችን የክረምቱ አፈና ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታየውም በዚህ በዓል አካባቢ ስለሆነ ይቺ ዕለት 'ቡሄ' የሚለውን ስያሜ አገኘች። ቡሄ ማለት ገላጣ፣ የተገለጠ ማለት ነው፡፡

በገጠርም ሆነ በየከተማው ልጆች ጅራፋቸውን ገምደው ሲያጮሁ (ሲያኖጉ) ይሰነብታሉ። እናቶችም ለበዓሉ ዝግጅት ስንዴ ሲለቅሙ፣ ሲፈትጉ፣ ሲፈጩ ይሰነብታሉ። ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ዕለት ጊዜው ምሽት ነበር፡፡ እረኞችም ከብርሃኑ የተነሣ እየተገረሙና እየተደነቁ ወደ ቤት አልተመለሱም ነበር፡፡ የልጆቹን መዘግየት ያዩ ወላጆች ችቦ አብርተውና ዳቦ ይዘው ፍለጋ ወጡ፡፡ ታዲያ ያንን ማስታወሻ «ቡሄ» ለሚሉ ልጆች ሙልሙል ዳቦ የሚሰጠውና ችቦ በማብራት በዓሉን የምናከብረውም ከዚህ በመነሣት ነው፡፡

የቡሄ ዜማ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በዋዜማው የሠፈር ልጆች በየቤቱ እየዞሩ ሆያ ! አሲዮ ቤሌማ እያሉ ይጨፍራሉ።

ቡሔ በሉ

ቡሔ በሉ |2| ሆ ልጆች ሁሉ ሆ

የኛማ ጌታ ሆ የአለም ፈጣሪ ሆ

የሰላም አምላክ ሆ ትሁት መሀሪ ሆ

በደብረታቦር ሆ የተገለፀው ሆ

ፊቱ እንደፀሀይ ሆ በርቶ የታየው ሆ

ልብሱ እንደ ብርሃን ሆ ያንፀባረቀው ሆ

......................

ድምፅህን ሰማና በብሩ ደመና |2|

የቡሔው ብርሃን ለኛ በራልን |2|

…………………....

ያዕቆብ ዩሃንስ ሆእንዲሁም ጴጥሮስ ሆ

አምላክን አዩት ሆ ሙሴ ኤልያስ ሆ

አባትም አለ ሆ ልጄን ስሙት ሆ

ቃሌ ነውና ሆ የወለድኩት ሆ

..........................

ታቦር አርሞንኤም ሆ ብርሃን የታየባቸው ሆ

ከቅዱስ ተራራ ሆ ስምህ ደስ አላቸው ሆ

ሰላም ሰላም ሆየታቦር ተራራ ሆ

ብርሃነ መለኮት ሆ ባንቺ ላይ አበራሆ

..........................

በተዋህዶ ሆ ወልድ የከበረው ሆ

የእግዚአብሔር አብ ልጅ ወልደ ማርያም ነው

.....................

ቡሔ በሉ ሆ ቡሔ በሉ ሆ

የአዳም ልጆች ብርሃንን ተቀበሉ

አባቴ ቤት ሆ አለኝ ለከት ሆ

እናቴም ቤት ሆ አለኝ ለከት ሆ

አጎቴም ቤት ሆ አለኝ ለከት ሆ

አክስቴም ቤት አለኝ ለከት ሆ

ተከምራል ሆ እንደ ኩበት ሆ

.......................

የአመት ልምዳችን ሆ ከጥንት የመጣ ሆ

የተከመረው ሆ ከመሶብ ይውጣ ሆ

ከደብረ ታቦር ሆ ጌታ ስለመጣ ሆ

የተጋገረው ሆ ሙልሙሉ ይውጣ ሆ

.......................

ኢትዮጲያውያን ሆ ታሪክ አላችሁ ሆ

ባህላችሁን ይዙ አጥብቃችሁ ሆ

ችቦውን አብሩት ሆ እንደ አባቶቻችሁ ሆ

ሚስጢር ስላለው ሆ ደስ ይበልስችሁ ሆ

....................

አባቶቶቻችን ሆ ያወረሱን ሆ

የቡሔን ትርጉም ሆ ያስተማሩን ሆ

እንድንጠብቀው ሆ ለኛ የሰጡን ሆ

ይህን ነውና ሆ ይስድረከቡን ሆ

........................

ለድንግል ማርያም ሆ አስራት የሆንሽ ሆ

ቅዱሳን ጻድቃን ሆ የሙሉብሽ ሆ

ሁሌም እንግዶች ሆ የሚያርፉብሽ ሆ

..................

ለሐዋርያት ሆ የላከው መንፈስሆ

ዛሬም ለኢትዮጵያ ሆ ፀጋውን ያፍስ ሆ

በበጎ ምግባር ሆ እንድንታነፅ ሆ

በቅን ልቦና ሆ በጥሩ መንፈስ ሆ

በረከት ረድኤት ሆበሁላችን ይንፈስ

በዚህ ጊዜ እናቶች ካዘጋጁት ዳቦ ይሰጧቸውና እየገመጡ ጅራፋቸውን ሲያጮሁ ያመሻሉ። የቡሄ ዕለት ለእያንዳንዱ የቤተሰብ፣ ዘመድ አዝማድ ልጅ አንዳንድ ሙልሙል ዳቦ በልጆቹ ልክ ይሰጣል። በቆሎ ተማሪዎች ዘንድ ደግሞ ደብረ ታቦር ‘የተማሪዎች በዓል’ ነው። ተማሪዎቹ ቀደም ብለው “ስለ ደብረ ታቦር" እያሉ እህሉንም፣ ብቅሉንም፣ ጌሾውንም ይለምኑና ጠላውን ጠምቀው፣ ዳቦውን ጋግረው፣ ቆሎውን ቆልተው ለደብረ ታቦር ዕለት ሊያስቀድሱ የመጡትን ምዕመናን ሁሉ ይጋብዛሉ።

በአሁኑ ጊዜ፣ በተለይ በአዲስ አበባ ይሄንን መንፈሳዊና ባህላዊ መሠረት በመልቀቅ ለሕሙማን፣ አዛውንት እንዲሁም ለእንስሳት ድንጋጤ የሚፈጥረውንና ለእሳት አደጋ የሚያጋልጠውን ባእዳዊ ርችት በመተኮስ ሆኗል የሚከበረው።

ዋቢ ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]