ድረ ገጽ መረብ

ከውክፔዲያ
ደንበኛ አገልጋይ

ድረ ገጽ መረብ (ወይም ኢንተርኔት) በጣም ብዙ የኮምፒዩተር አውታሮችን ያያየዘ የመገናኛ መረብ ነው። በመረቡ ውስጥ ብዙ ድረ ገጽ ይገኛሉ። ከዚያ በላይ በርካታ የመነጋገርና መገናኘት መንገዶች አሉ።

ከሁሉ አስቀድሞ የተፈጠረ ክፍለ-ኢንተርኔት «USENET» የሚባለው አገልግሎት ነው። ይህ በ1973 ዓ.ም. (1980 እ.ኤ.አ.) አካባቢ ሲጀመር በተለይ ለዩኒቨርሲቴዎችና ኮሌጆች ብቻ የታወቀ መገናኛ ሆኖ ቆየ። ይህ ጽሑፍ በተገናኙት ኮምፒውተሮች ላይ መልጠፍ የሚፈቅድ ሥርዓት ብቻ እንጂ ስዕል ወይም ሌላ ነገር አልነበረም። መጀመርያው e-mail አድራሳዎች የተሰጡት ከዚያ ዘመን ነው። ዛሬም ብዙዎች ተጠቃሚዎቹ ግን ስንኳ ስለ USENET መኖሩን አያውቁም።

መጀመርያው ድረ ገጽ የተፈጠረው በ1983 ዓ.ም. (1990 እ.ኤ.አ.) ሆነ።

ኢንተርኔት እንዴት እንደሚሰራ ለመረዳት በመጀመሪያ አገልጋይና (server) ደንበኛ (client) ምን እንደሆኑ ለይተን እንረዳ። አንድ የምግብ ቤት አስተናጋጅ ምግብ ለብዙ ተስተናጋጆች እንደሚያቀርበው፣ ሁሉ ኢንተርኔት ላይ ያለ አገልጋይ (server) የተለያዩ ነገሮችን ደንበኞቹ (clients) ይሰጣል። የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ደንበኞች ይባላሉ ማለት ነው።

ደንበኞች የተለያየ ነገር ከአገልጋዩ ሊቀበሉ ይችላሉ። ለምሳሌ፤ እርስዎ ይህንን ድረ ገጽ ሲመለከቱ የቻሉት አገልጋዩን ድረ ገጹን እንዲልክልዎ በመጠየቅዎ ነው። በመሆኑም ይሄ አገልጋይ «ድረ ገጽ አገልጋይ» (web server) ይባላል። ሌላ አገልጋይ ደሞ መልአክት (email) ሊያቀብል ይችላል። ስለዚህም «መልአክት አገልጋይ» ይባላል።

ኢንተርኔት የአገልጋይና የደንበኞች መረብ ነው። በአብዛኛው የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ድረ ገጽ (WWW or World Wide Web) ይጠቀማሉ። ስለዚህም ደረ ገጽ የኢንተርኔት ትልቁ ጥቅም ነው። ብዙ ጊዘም ኢንተርኔትና ድረ ገጽ በስህተት አንድ መስለው ይታያሉ። ነገር ግን መረቡ፤ ማለትም ኢንተርኔት፤ ለሌላ ጥቅም ላይ ሊውል ይችላል። ለምሳሌ ከላይ የተጠቀሰው (USENET) የኢንተርኔት ሌላው ጥቅም ነው።

ከአንድ አገልጋይ የሚፈልጉትን ነገር ለመጠያቅ በመጀመሪያ የአገልጋዩን መጥራት ያስፈልጋል። እያንዳንዱ አገልጋይ ልዩ የሰነድ አድራሻ (URL) አለው። ይሄን የሰነድ አድራሻ በመጠቀም ከየትኛውም ቦታ አገልጋዩን መጥራት ይቻላል። ለምሳሌ www.wikipedia.org የውክፔድያ አገልጋይ የሰነድ አድራሻ ነው። አንዳንዴ አንድ ነገር ፈልገን የትኛው የሰነድ አድራሻ ላይ አንደምናገኘው ላናውቅ እንችላለን። በዚህ ጊዘ ፈላጊዎችን (search engines) እንጠቀማለን። ለምሳሌ www.google.com ጉግል ላይ የሰነድ አድራሻዎችን መፈለግ ይችላሉ።