ጨረራ

ከውክፔዲያ
ቁስን ሰንጥቀው ለማለፍ የተለያየ ችሎታ ያላቸው ሶስት የአዮን ፈጣሪ ጨረራ አይነቶችአልፋ እኑሶች (α) በወረቀት ሊቆሙ ይችላሉ። ቤታ እኑሶች (β) በአሉሚኒየም ይገደባሉ። ጋማ ጨረራ (γ) ምንም እንኳ ሃይሉ ቢዳከምም ማናቸውንም ቁስ ሰንጥቆ ማለፍ ይችላል

ጨረራ ወይም ‘radiation’ የሚለው ቃል በቀላሉ ሲገለፅ አቅምን (ኢነርጂን) ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ በሞገድ (wave) ወይም በእኑስ (ቅንጣጢት) መልክ ሲጓጓዝ ማለት ነው። ‘radiation’ የሚለውን የእንግሊዝኛ ቃል የተለያዩ የሳይንስና የኢንጂኔሪንግ መስኮች ጨረራ እና ጨረር በማለት የተለያየ ትርጓሜ ይሰጡታል። ሆኖም በህብረተሰባችን ዘንድ በተለይም በሒሳብ ትምህርት ውስጥ ከትምህርት ቤት ጀምሮ ‘ray’ ለሚለው ቃል ጨረር በሚል የተተረጎመ በመሆኑና የእንግሊዝኛውን ‘radiation’ ከሚለው ቃል ትርጓሜው የሚለይ በመሆኑ ጨረራ የሚለውን ቃል መጠቀም ይሻላል። ሆኖም ግን አሁንም ድረስ ‘alpha ray’ እና ‘beta ray’ እየተባለ በእንግሊዝኛውም ቋንቋ ቢሆን ‘ray’ የሚለው ቃል ጥቅም ላይ ይውላል፡ ፡

የጨረራ ዓይነት[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የጨረራ ዓይነት በዋናነት በሁለት ይከፈላሉ። እነዚህም አዮን ፈጣሪ ጨረራ (Ionizing Radiation) እና አዮን የማይፈጥር ጨረራ ዓይነቶች (Non-Ionizing Radiation) በማለት ይታወቃሉ።

አዮን ፈጣሪ ጨረራ (Ionizing Radiation)[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በሰውነታችን ወይም በቁስ ውስጥ ሲያልፍ በሰውነታችን ወይም በቁሱ ውስጥ በሚገኘው አቶም ውስጥ የሚገኘውን ኤሌክትሮን በማስፈንጠር/በማውጣት የቻርጅ ልዩነት እንዲፈጠር በማድረግ አዮን ይፈጠራል። ለአዮን ፈጣሪ ጨረራ (Ionizing Radiation) አለአግባብ መጋለጥ በሰዎች ጤና፣ በንብረት እና በአካባቢ ላይ ከፍ ያለ ጉዳት ሊያደርስ እንደሚችል በመስኩ የተደረጉ ጥናቶች የሚያመለክቱ ሲሆን፤ ለአዮን ፈጣሪ ጨረራ አይነተኛ ባህርይ በስሜት ህዋሳቶቻችን በአካባቢያችን መኖሩን ማወቅ የማንችል፣ በተለይ በጨረራ አመንጪዎች (Radiation Sources) የተበከሉ የምግብና የፍጆታ ዕቃዎች ወደ ህብረተሰቡ ከተሰራጩ ጉዳቱ አስከፊ እንደሚሆን የተረጋገጠና ለዚህም ቁጥጥር ያመች ዘንድ ወሰን የወጣለት ነው።

ለከፍተኛ አዮን ፈጣሪ ጨረራ መጋለጥ ለህልፈተ ህይወት፣ ለዘላቂ የአካል ጉዳት፣ ለደምና ሌሎች የካንሰር ደዌ፣ ለመካንነት እንዲሁም ለአእምሮ ዘገምተኝነት የሚዳርግና በትውልድ የሚተላለፍ የበራሄ ye-zer-wurs /Genetic/ ለውጥ የሚያመጣ ነው።

አዮን ፈጣሪ ያልሆኑ የጨረራ ዓይነቶች (Non-Ionizing Radiation)[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

በሰውነታችን ውስጥ በሚያልፉበት ጊዜ አዮን የመፍጠር አቅም የላቸውም ነገር ግን በተጋለጠው የሰውነታችን ህብረህዋስ (Tissue) ላይ ሙቀት እና መጠነኛ የሆነ የኤሌክትሪክ ጅረት እንዲፈጠር ያደርጋሉ። የሙቀቱ መጠን ከፍተኛ ከሆነ የሰውነታችንን ህዋስን (cell) የመግደል አቅም ይኖራቸዋል። በዚህም ምክንያት ሞት ሊከሰት እንደሚችል ጥናቶች ይጠቁማሉ። እነዚህ ጥናቶች በአብዛኛው ያተኮሩትና ያገኟቸው ውጤቶች በሙቀቱ አማካይነት እና በሚፈጠረው መጠነኛ የሆነ የኤሌክትሪክ ጅረት የሚመጣውን የጤና እክል በማየት ነው። ይህም የጤና ችግር ከሰው ሰው የሚለያይ ነው። በተጨማሪም ይህ የጨረራ ዓይነት ካንሰር ሊፈጥር ይችላል ወይም አይችልም በሚለው ላይ የተለያዩ ጥናቶች በተለያዩ ተመራማሪዎች እየተከናወነ እንደሆነ ከዓለም አቀፍ የአዮን ፈጣሪ ያልሆኑ የጨረራ መከላከያ ኮሚሽን (International Commission on Non-Ionizing Radiation Protection - ICNIRP) የሚወጡ ሪፖርቶች ይጠቁማሉ። ይህ ኮሚሽን ለዚህ የጨረራ ዓይነት ቁጥጥር እንዲያመች ዓለም አቀፍ ወሰን ያወጣ ሲሆን በብዙ ሀገራት ዘንድ ተቀባይነትን በማግኘት ተፈፃሚ እየሆኑ ይገኛል። እነዚህን አዮን ፈጣሪ ያልሆኑ የጨረራ ዓይነቶች (Non-Ionizing Radiation) በተለይም ካንሰር ያመጣሉ ወይም አያመጡም የሚሉት ጥናቶች ተረጋግጠው ተገቢው ውሳኔ ላይ እስኪደረስ ድረስ በሳይንሱ ዓለም እንደተለመደው ተገቢ የጥንቃቄ መንግድ (Precautionary Approach) እንድንከተል ሁሉም ወገኖች ያስገነዝባሉ።

አዮን ፈጣሪ ያልሆኑ የጨረራ ዓይነቶች (Non-Ionizing Radiation) ለመግለፅም፣ እንደ የራዲዮ ሞገድ /Radio wave/፣ ማይክሮ ዌቭ /Microwave/፣ ታህታይ ቀይ ጨረራ /Infrared/፣ ብርሃን /Visible Light/፣ ላዕላይ ወይነጸጅ ጨረራ /Ultra Violet/፣ የላዘር ጨረራ /laser/ የሚባሉት ሲሆኑ፤ በህክምናው፣ በኢንዱስትሪ፣ በሞባይል ቴሌኮምኒኬሽን ሥርዓት፣ በራዲዮቴሌቪዥን ሥርጭት፣ የራዳር ሥርዓት፣ ብሎም በመዝናኛ ቤቶችና ሲዲና ዲቪዲ ማጫወቻዎች ጨምሮ በስፋት የሚገኙ ናቸው።

የጨረራ ምንጮች[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

የጨረራ ምንጮችን ስናይ በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ መልክ የሚገኙ ናቸው። በሰውነታችን ውስጥ የካልስዩም ራዲዮኑክላይድ በተወሰነ መጠን ይገኛል፣ በሁሉም አፈር ውስጥ መጠኑ ይለያይ እንጂ ራዲዮአክቲቭ ፖታስዩም እንዲሁም በሙዝ፣ ቡና፣ ወዘተ ውስጥ ተለያዩ ራዲዮኖክላይዶች ይገኛሉ። ከከዋክብትና ከጋላክሲዎችም የተለያዩ የጨረራ ዓይነቶች (የኮስሚክ ጨረራ) ወደምድር በመምጣት በተወሰነ ደረጃ የጨረራ መጋለጥ በሰው ልጅ ላይ ይፈጥራሉ። እንደ አለንበት ቦታ መልካ ምድር ሁኔታም በተለይ ከዩራንዩምቶርይም ራዲዮኖክላይዶች (primordial sources) እና ከእነሱ በመፈራረስ (decay) ሂደት ተፈጥረው በምድር ላይ የሚገኙ በርካታ የጨረራ ምንጮች ይገኛሉ። ከነዚህ በተፈጥሮ የሚገኙ የጨረራ ምንጮች የሰው ልጅ ለጨረራ ይጋለጣል ይህም Background Radiation ይባላል። ምንም እንኳን ይህ የተፈጥሮ የመጋለጥ ሁኔታ ከቦታ ቦታ የሚለያይ ቢሆንም በዓለም ላይ አንድ ሰው በአማካይ ለ2.4 mSv በዓመት ይጋለጣል። ይህም በተለምዶ በደረት አካባቢ የሚታዘዝ አንድ ራጅ (chest radiography) ስንነሳ የሚኖረውን የጨረራ መጋለጥ ስድስት እጥፍ ይሆናል።

በሰው ሰራሽ መልክ የሚዘጋጁ የጨረራ አመንጪዎች ደግሞ የታሸጉና ያልታሸጉ የሬዲዮአክቲቭ ቁሶች (Sealed and Unsealed Radioactive Sources) በትላልቅ አክስላሬተሮች (Accelerators) ወይም በኑክሌር ማብላያ (Nuclear Reactor) ወይም ከፍተኛ የኑትሮን ምንጮችን በመጠቀም መፈብረክ የሚቻል ሲሆን፣ የተለያዩ የኤክስሬይ መሳሪያዎችም (X-rays) በፋብሪካ ይመረታሉ። በህክምና መስክ የሚገኙ የኤክስሬይ መሳሪያ (X-ray) በተለምዶ ራጅ ተብሎ የሚታወቅው ሲሆን፣ የተለያዩ የራጅ አገልግሎት ዓይነቶች ይገኛሉ፣ እነዚህም (መደበኛ ራጅ Conventional X-ray፣ የጥርስ-Dental Radiography፣ ሲቲ ስካን-CT-Scan፣ የማሞግራፊ-Mammography፣ ፍሎሮስኮፒ-Fluoroscopy፣ ኢንተርቬንሽናል ራዲዮሎጂ-Interventional Radiology፣ ወዘተ) ይባላሉ፤ የኤክስሬይ መሳሪያዎች በሌሎች ዘርፎች ለምሳሌም በኢንዱስትሪው የብረታ ብረት ምርቶች ጥራት ቁጥጥር (ለምሳሌምከፍተኛ ግፊት - pressure የሚያርፍባቸውን የአውሮፕላን አካላትና ሌሎች የብረት ምርቶችን ጥራት ለመቆጣጠር – Industrial radiography ሥራ) ይገኛል፤ በበርካታ ኤርፖርቶች፣ ሆቴሎችና ሌሎች ሕንፃዎች ለጥበቃ አገልግሎት ማለትም ዕቃዎችን ለመፈተሽ፤ በሲሚንቶ ኢንዱስትሪዎችና የትምህርትና ምርምር ተቋማት የምርቶችን ጥራትና የናሙናዎችን ተፈጥሯዊ የውስጥ ቅርፅ - internal structure - ለመለካት እንዲሁም ለጥናትና ምርምር (XRF)፤ በወደቦችና የጉምሩክ ኬላዎች የሚገኙ የከፍተኛ የካርጎ ስክሪኒንግ የሊኒየር አክስላሬተሮች ለዕቃዎች ቁጥጥር አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛሉ። ይህም የኤክስሬይ መሳሪያዎች በህክምናው ላይ በተለምዶ ራጅ ብለን ለምንጠራው ተግባር ላይ ብቻ የሚውሉ ሳይሆን በሌሎችም ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ውስጥ የሚገኙ መሆኑን ያሳይል፡፡

ደግሞ ይዩ[ለማስተካከል | ኮድ አርም]

ሲዲና ዲቪዲ ልዩነቱ